የግብፅ ህዝብ አምጦ የወለደው የተሂሪር አደባባይ ህዝባዊ አብዮት ውሉ የለየለት አይመስልም። በርካታ የፖለቲካ ተንታኞች አብዮቱ ጨንግፏል ሲሉ ቀላል የማይባሉት ደግሞ አብዮቱ በሙርሲና በዙሪያቸው ባሉ አክራሪ የእስልምና አማኞች ተነጥቋል ብለው ያምናሉ።
ግብፃውያን ዓመታት በላይ የተጫነባቸውን የሙባረክን አገዛዝ ከጣሉ በኋላ እፎይታን አላገኙም። በህዝቡ ምርጫ አብዛኛውን የፓርላማ መቀመጫ የያዘው የእስልምና ወንድማማቾች ፓርቲ ግብፅን ወደ አክራሪ የእስልምና አገዛዝ ይመልሳታል የሚል ስጋት በመኖሩ በፕሬዝዳንት ሙርሲ ላይ እምነት የሌላቸው በርካታ ግብፃውያን ተቃውሞ ሲያሰሙ ቆይተዋል።
በወናነት በሙርሲ መንግስት ላይ ተቃውሞ የሚያነሱ አክራሪ ያልሆኑ የእስልምና እምነት ተከታይ ግብፃውያንና የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ አማኝ ግብፃውያን ናቸው። ይሁንእንጂ ሙርሲ የእሳቸውን ስልጣን ከፍርድ ቤቶችና ከህግ በላይ የሚያጎነፅፈውን ፣ ለሴቶች እምብዛም የእኩልነት መብት የማያሰጠውንና በአመዛኙ ወደሸሪያ ህግ የሚያዘነብለው ሕገ-መንግስት ላይ ህዝበ ውሳኔ አሰጥተው ውሳኔው ላይ የተሳተፉ ጥቂት ግብፃውያን ህገ-መንግስቱን መደገፋቸው አይዘነጋም።
ይሁንና የሙርሲ ተቃዋሚዎች ከመጀመሪያው ህዝበ -ውሳኔውን ከመቃወማቸውም ባለፈ በህዝብ ውሳኔውም ላይ ወጥተው ድምፅ የሰቱ ጥቂት ግብፃውያን ናቸው በሚል በድጋሚ የህዝቡ ውሳኔውን ሳይቀበሉት ቀርተዋል።
ሀገሪቱ የሙባረክ አገዛዝ ከወደቀ በኋላ በአክራሪና ለዘብተኛ እንዲሁም ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ አማኞች የመክፈል አዝማሚያ አሳይታለች። በስልጣን ላይ ያለው የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ ሀገሪቱ በእስልምና አስተምሮሆቶች መመራት አለባት ወደሚል አቋም ያዘነበለ በመሆኑ በእስራኤል፣ በአሜሪካና በአውሮፓ ህብረት በጥርጣሬ አይን እንዲታይ አድርጎታል። ምዕራባውያን የግብፅ የታሂሪሪ አደባባይ አብዮት በእነ- ኢራንና በሌሎች አክራሪ የእስልምና መንግስታት እንዳይጠለፉም ስጋት አላቸው።