ላለፉት አርባ ዓመታት ለኦሮሞ ህዝብ ነጻነት ሲታገል የቆየው ኦነግ አመራሮቹ ሲጣሉና ሲታረቁ መስማት የተለመደ ነው። የግለሰብ ጸብ የሚመስለው የድርጅት በሽታ ሲንጠው የቆየው ኦነግ በውል ባይታወቅም ተሰነጣጥቆ ለሰሚው ግራ የሚያጋባ ድርጅት ከሆነም ዓመታት ተቆጥረዋል። ስህተትን ገምግሞ የትግል አቅጣጫና ፕሮግራም ከመቀየር ይልቅ ጊዜው ባለፈበት አስተሳሰብ ባለበት ሲረግጥ እድሜውን የፈጀ ድርጅት እንደሆነ ተደርጎም ይወሰዳል።
ስለ ኦነግ ሲነሳ አብዛኞች በመገረም የሚናገሩትና ሚዛን የሚደፋው አስተያየት የሚሰነዘረው በድርጅቱ መከፋፈልና መበጣጠስ ሳይሆን ተለያይተውም አስመራን የሙጥኝ ያሉበት ምክንያት ነው። ኢህአዴግ ህጻን እያለ ሻዕቢያ እንዳሻው ይነዳው እንደነበር የሚያስታውሱ አስተያየት ሰጪዎች ከሽግግር መንግስት ምስረታ በኋላ ኦነግ አገር ለቆ እንዲወጣ መንገዱን የጠረገው ሻዕቢያ መሆኑንን በቁጭት ይናገራሉ።
ኢህአዴግ ለስልጣን አዲስ በሆነበት የጨቅላነት ዘመኑ፣ ኦነግ በታሪኩ ያልነበረውን ሰራዊት በመገንባት አስጨንቆት እንደነበር በመጠቆም በወቅቱ አስተያየት የሰጡ ኢህአዴግ በተለይም መለስ በሻዕቢያ በኩል ኦነግን ለመታረቅ አቅርበውት የነበረውን የሽምግልና ጥያቄ ኦነግ እንዳይቀበል ሰሚ ባያገኙም በአጽዕኖት ምክራቸውን ሰጥተው ነበር።
በኦነግ ታጣቂ ሃይሎችና በኢህአዴግ ሰራዊት መካከል እኩል ሊባል በሚችል ደረጃ የጡንቻ መፈታተን ነበር። ደርግ ሲበታተን ኦነግን የተቀላቀሉ የቀድሞው የኢትዮጵያ ሰራዊት አካላት ወያኔን የማዳፋት አቅሙ ነበራቸው። በወቅቱ የንስር ያህል ጉልበትና ሃይል ቢኖራቸውም ራሳቸውን ጫጩት አድርገው ተመለከቱ። አዲስ አበባ ሲገቡ የነበራቸውን የህዝብ ድጋፍ አራግፈው ጣሉት። በስሜት እየተነዱ ከሚወዷቸው ሁሉ ተቀያየሙ። ህወሃት አጋጣሚውን ለቅስቀሳና ለስም ማቆሸሻ ሰራበት። በስተመጨረሻ ኦነግ ሃይሉንና አቅሙን ዘንግቶ በአመራር ችግርና በአቋም ሸውራራነት ሃይሉን በሙሉ ወደ ካምፕ በማስገባት የኢህአዴግን የእርቅ ጥያቄ ተቀበለ። ሰራዊቱን እየነዳ በፈቃደኛት አሳሰራቸው።
በሻዕቢያ አደራዳሪነት ሁርሶ፣ ደዴሳና መስኖ የገባው ሰራዊት “በደባ” ተከቦ ትጥቁን እንዲፈታ ተደረገ። አብጦ የነበረው የኦነግ ጡንቻ በቅጽበት ከሰመ፤ ሰለለ። ኦነግ ሲቆጣጠራቸው የነበሩትን ቦታዎች ለማስተዳደርና በኦህዴድ ለመተካት ኢህአዴግ እንደ እባብ ተሹለክልኮ ዓላማውን አሳካ። ሻዕቢያም በዚሁ ውለታው ኢትዮጵያንና ኢኮኖሚዋን ብሎም የኢትዮጵያን ስነልቦና እንዳሻው እንዲጋልብ ተፈቀደለት። ብዙ አሻጥር ተፈጠረ፤ ተፈጸመም። ደንዳና ቆዳ ያላት ኢትዮጵያና ህዝቧ ተቦጠቦጡ። ተዘረፉ። አንድ እግር የቡና ተክል የሌላት ኤርትራ ቡና ላኪ ከሚባሉት ቀዳሚ አገራት ዝርዝር ውስጥ ተሰለፈች። አፈርን።