Wednesday, March 12, 2014

ጃዋር መሐመድ In My Mind!

ከአብርሃ ደስታ

ጎበዝ ሰው አያስፈራኝም (ጉረኝነቴ) ምክንያቱም ጎበዝ ሰው ብቃት አለው። ብቃት ያለው ሰው በሐሳብ (በምክንያታዊነት) ያምናል። በምክንያት የሚያምን ሰው ደግሞ አያስፈራም። ምክንያቱም በሐሳብ (በምክንያት) ከሚያምን ሰው ጋር ስትገናኝ ምክንያታዊነት እንደ መስፈርት በመጠቀም በሐሳብ ትከራከራለህ እንጂ ወደ ሌላ የሐይል መንገድ አትሯራጥም። በሐሳብ መከራከር ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም። ምክንያቱም በምክንያት ስትከራከር አንድም ሰውየው ያሳምነሃል አልያም ደግሞ አንተ ታሳምነዋለህ። አንዳቹ ካሳመናቹ ሁለታችሁ ትስማማላቹ። ካልተስማማችሁ ደግሞ በሐሳብ ትለያያላቹ። በሐሳብ መለያየት በራሱ ችግር የለውም።

ጃዋር መሐመድ በፖለቲካ ብቃታቸው ከማደንቃቸው ኢትዮጵያውያን ፖለቲከኞች አንዱ ነው። እስከ ቅርብ ግዜ ጃዋር በሚሰጣቸው ትንታኔዎች እደነቅ ነበር። አንድ ግዜ ዕድል አግኝቼም አድናቆቴን ገልጨለታለሁ።
 

ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን የሐሳብ ልዩነት እየፈጠርን ነን (እኔና ጃዋር) አሁንም ቢሆን የሐሳብ ልዩነት ስለተፈጠረ ብቻ ጃዋርን አልጠላዉም። የራሱ ሐሳብ የመያዝና የማራመድ ሙሉ መብት አለው። በሱ ምርጫ ጣልቃ አልገባም። ግን የፖለቲካ ብቃቱ ግምት ዉስጥ በማስገባት ጃዋርን በአካል አግኝቼ በፖለቲካ ጉዳዮች ዙርያ መነጋገር (መከራከር) አማረኝ።

የጃዋር የፖለቲካ ብቃት ለኢትዮጵያ ሀገራችን የወደፊት እጣፈንታ እሴት ነው (ነበር) ብዬ አስባለሁ። ጃዋር ከሌሎች ቆራጥ ኢትዮጵያውያን ፖለቲከኞች ጋር በመሆን መሰረታዊ የፖለቲካ ለውጥ ማምጣት ይችል ነበር። አሁንም ተስፋ አልቆርጥም። 

ከጃዋር ጋር መከራከር (መነጋገር) የምፈልገው ነጥብ ምንድነው? የተለያየንበት ነጥብ ላይ ነው። ከጃዋር ጋር የተለያየንበት ነጥብ 'የኢትዮጵያዊነት ደፍኒሽን' ላይ ነው። የድሮ ስርዓቶች (የአሁንም ጭምር) በህዝቦች ላይ በደል ፈፅመዋል። የበደሉ መጠን ይለያይ እንጂ በሁሉም የኢትዮጵያ ህዝቦች ላይ ደርሷል። በደሉ (ጭቆናው) በህዝቦች ላይ መድረሱ አልደግፍም። በዚህ ነጥብ ከጃዋር ጋር እስማማለሁ። 

አዎ! በህዝቦች ላይ የደረሰው (እየደረሰ ያለው) ጭቆና መቃወም አለብን። ግን የምንቃወመው ጭቆናው እንጂ ህዝብን አይደለም። ጭቆናው ማነው ያመጣው? ገዥዎች ናቸው። ህዝብ አይደለም ህዝብን የበደለ (የጨቆነ) ነገስታት (መንግስታት) ናቸው ህዝቦችን የጨቆኑ (የሚጨቁኑ) ስለዚህ መቃወም ያለብን ጭቋኞችን (ገዥዎችን) እንጂ ህዝብን (ተገዥዎችን) አይደለም። 

አጤ ምኒሊክ በህዝቦች ላይ ግፍ ከፈፀሙ በደሉ የደረሰው በንጉሰ ነገስቱ እንጂ በሀገረ ኢትዮጵያ አይደለም። አጤ ምኒሊክን መውደድ እንደሚቻል ሁሉ መጥላትም ይቻላል። ጃዋር አጤ ምንሊክን መጥላት ይችላል። አጤ ምኒሊክ ስለ ጠላ ኢትዮጵያነቱን መጥላት ያለበት ግን አይመስለኝም። ምክንያቱም አጤ ምኒሊክ የኢትዮጵያ ንጉስ እንጂ ኢትዮጵያ አይደሉም። ይሄው አጤ ምኒሊክ ካረፉ መቶኛ ዓመታቸው ያዙ። ኢትዮጵያ ግን አለች፤ ለዘላለምም ትኖራለች። ስለዚህ ንጉስና ሀገር ማገናኘት አልታየኝም። ኢትይጵያና ምኒሊክ አንድ ያደረጋቸው ማነው?

የሀገር መሪዎችን እንደየተግባራቸው መጥላት ወይ መውደድ እንችላለን። እናት ሀገር ኢትዮጵያ ግን መውደድ ብቻ። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ሀገራችን የምትጠላበት ምንም ምክንያት የለም። ኢትዮጵያችን በማህፀኗ ይዛ፣ ወልዳ፣ አሳድጋ ይሄው ለዚህ በቃን። ኢትዮጵያ በደል (ጭቆና) አላደረሰችብንም። ህዝቦች የተጨቆኑ በኢትዮጵያ ንጉሶች እንጂ በኢትዮጵያ ሀገር አይደለም። በንጉስ ተግባር ምክንያት ሀገር ከጠላን ተሳስተናል። ጨቋኞች ካሉ እዋጋቸዋለሁ፤ እቃወማቸዋለሁ። ኢትዮጵያዬን ከጨቋኞች ነፃ አወጣታለሁ እንጂ ጨቋኝ መሪዎች ስላሏት (ስለነበሯት) አልጠላትም። ስለዚህ ሀገርና ገዢ ብንለያይ።

ጃዋር ሐሳብህ በስህተት ተረድቼህ ከሆነ አርመኝ። በዚህ ጉዳይ ተገናኝተን ብንነጋገር ግን ደስ ይለኛል (አጋጣሚ ሲፈጠር ማለቴ ነው) 

ሁላችን ኢትዮጵያዊ ማንነታችንን ለሌሎች አሳልፈን አንስጥ። ኢትዮጵያዊነታችን በራሳችን ለራሳችን።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

It is so!!!

No comments:

Post a Comment