Thursday, September 4, 2014

መንግስትን ከምቃወምባቸው ምክንያቶች 2ኛው: * የግማሽ ሚሊዮን ኮንትራት ሰራተኞች አበሳ በሳዑዲ አረቢያ

Saudi arabia ethiopia 1
Saudi arabia ethiopia 2
Saudi arabia ethiopia 3
Saudi arabia ethiopia 4
ከነብዩ ሲራክ (ሳዑዲ አረቢያ)
* የግማሽ ሚሊዮን ኮንትራት ሰራተኞች አበሳ … !
ህገ ወጡ የስደት መንገድ ይቆም ዘንድ በሚል እሳቤ የኢትዮጵያ መንግስት የሳውዲ አረቢያ የኮንትራት ሰራተኛ ማቅረብን ተስማሙ ተባለ። ስለተደረገው ስምምነት ውል ግን የሚታወቅ ነገር ጠፋ ። ከሁለትዮሽ ስምምነት የወጣ ውል ነው ተብሎ በሚታወቀው የተሸፋፈነ ስምምነት ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የኮንትራት ስራተኞች ወደ ሳውዲ ገቡ።

ህጋዊ ፈቃድ ይዘው በህጋዊ መንገድ የሰሩ ባይጠፉም በ”ህጋዊ ” ፍቃድ ስር የኮንትራት ሰራተኞች ከማገናኘት ጀምሮ እስከ ሰራተኛ አቅርቦት ህገ ወጥ አካሄድ ተቀይጦበት ዜጎች በቂ መረጃ ወደ ሌላቸው ሳውዲ የገጠር ከተሞች ሳይቀር ማሰራጨቱ በርትቶ ቀጠለ ። ኤጀንሲዎች በየገጠሩ የደላላ ቡድን በማሰማራት ለአቅመ አዳም ያልደረሱ ፣ በቋንቋ ከራሳቸው ዜጋ እንኳን መግባባት የማይችሉ ፣ ፊደል ያልቆጠሩ የሚባሉትን ጨምሮ፣ ለቤት መብራት እና ለመኪና እንግዳ የሆኑትን እህቶች በቀቢጸ ተስፋ እያማለሉ በተጭበረበረ መንገድ እንደላኳቸው መረጃዎች በስፋት ተገኙ። በኮንትራት አጠቃላይ ወጩ በቀጣሪው የሚከወን ቢሆንም ጉዳዩን ማስጨረሻ፣ የቲኬት እና ሌላ ሌላ ወጭ እየተባለ አራጣ ብድር ሳይቀር ለከፍተኛ ተዳርገው ስደቱን እንደተቀላቀሉ በግንባር ያገኘኋቸው ተገፊዎች ቅስማቸው በሃዘን ተሰብሮ እያነቡ ምሬታቸውን ገልጸውኛል !
ይህ ሁሉ የሆነው በመንግስት በኩል ምንም አይነት ቅድመ ዝግጅት ፣ ስልጠናና የማስተባበር ስራ ሳይሰራ ነበርና ወደ ሳውዲ የመጡት ኮንትራት ሰራተኞች መዳረሻቸውን እንኳ በትክክል የሚከታተልና የሚመዘግብ ተወካይ አልተዘጋጀም። ይህም ብዙ ሳይቆይ አደጋ አስከተለ …ከዚያ በኋላ የሆነውን ማንሳት ይከብዳል ! “…ገደሉ ፣ ተገደሉ ፣ ሞተው ተገኙ ፣ ራሳቸውን ሰቀሉ ፣ ከፎቅ ተወረወሩ፣ ተደፈሩ ፣ አበዱ ፣ ሰው አሳበዱ ፣ በየአውራ ጎዳናው ተንከራተቱ ፣ ወድቀው ታዩ …” ወዘተረፈ ተብሎ …ሰቅጣጭ መርዶ ጆሯችን እየከበደው መስማት ግድ አለው !
ህጋዊ ሽፋን የያዙ የሃገር ቤት ደላሎች ፣ አሸጋጋሪዎች ብቻ ሳይሆን መንግስት መስሪያ ቤት ተቋማት ፣ ከቀበሌና ወረዳ እስከ ማህበራዊና የኢሚግሬሽንና ደህንነት መረጃን ሳያረጋግጡ በመስጠታቸው በአብዛኛው እህቶቻችን ለዚሀ የከፋ አደጋ ተጋለጡ ። ለሁሉም የሚያም የሚያሳዝነው ይህ ስህተት ተሰርቶ የተሰደዱ ወገኖች ባሉበት ሃገር የቅርብ ርቀት በጅዳ የኢትየጵያ መንግስት የቆንስል ፣ በሪያድ የኢንባሲ መ/ቤት ቢኖሩም ዜጎች ሰብአዊ መብታቸው ሲጣስ ለመብታቸው መከበር አይተጉላቸውም !
እናም መብታችን የሚያስከብር አጥተን ቀኑ እንደጨለመብን እየተገፋን አመታትን ገፍተናል !

መንግስት ሆይ ስማን !
ነቢዩ ሲራክ

No comments:

Post a Comment