Friday, February 28, 2014

ጀግናውና ከሀዲው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራ

(ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)
hailemedhin
እነኝህ ሁለቱም አካላት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራን በየበኩላቸው ያሉትን ለመሆኑ የየራሳቸውን ማስረጃ የሚሏቸውን ነገሮች በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ የሕዝብ ወገን የሆነው ክፍል ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ጀግና ነው የሚሉበትን ምክንያት ሲጠቅሱ በአገዛዙ ተማሮ የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቁን፣ ይሄንን ድርጊት ከመፈጸሙ በፊትም ለወያኔ ባለመመቸቱ አሜን ወዴት ባለማለቱ እኅቱ በፌስ ቡክ (በመጽሐፈ ገጽ) በሰጠችው ገለጻ መሠረት ስልኬን ጠልፈውብኛል ይል እንደነበር፣ “መንግሥት” በተለያየ ዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች እየተከሰሰ እንዳለው የተለያዩ ግለሰቦችን በኮምፒውተራቸው (በመቀምራቸው) መሰለያ በመጫን እየሰለለ እንደሆነ እንደሚነገረው ሁሉ ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅንንም የግል ኮምፒውተሩን (መቀምሩን)  ካሜራ (በመቅረጸ ምስል) በመጠቀም እያንዳንዱን እንቅስቃሴየን ይከታተሉኛል ይል እንደነበር ኮንፒውተሩን (መቀምሩን) ሲጠቀም ካሜራውን (መቅረጸ ምስሉን) ለመሸፈን ይገደድ እንደነበር፣ መኖሪያ ቤቱንም በሌለሁበት እየገቡ ይፈትሹብኛል ይል እንደነበር፣ የሚያስፈራሩት አካላት እንደነበሩ፣ አልፎም ለቤተሰቦቹ እንደሚሠጋ ባጠቃላይ ደኅንነቱ በሚያሳዝን ሁኔታ አደጋ ላይ የወደቀ እንደነበር፣ ይህ ሁሉ ውክቢያና ማስፈራሪያ እየደረሰበትም ለእነሱ ቡድናዊ የፖለቲካ (እምነተ አሥተዳደር) ፍላጎት ባለመንበርከኩ ባለማደሩ ባለመገዛቱ እንደነበር ይህ ሁኔታ ደግሞ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ችግር መሆኑንና አዲስ ነገር አለመሆኑን በሁሉም ዜጎች ላይ እንደሚደርስ አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው የጋራ ችግር መሆኑን ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ግን እንደ ብዙዎቻችን ሁሉ በእነዚህ ግፎች ሁሉ ተንበርክኮ ባለመሸነፉና አሻፈረኝ ብሎ እራሱን ነጻ በማውጣቱ ለዚህ ለደረሰበት ሰላም ለሚነሳ ውክቢያ እጅ አለመስጠቱን በመጥቀስ ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ጀግና እንደሆነ ያረጋግጣሉ፡፡
“መንግሥት” እና ደጋፊዎቹ ደግሞ ምንም እንኳን እስከአሁን ከቦታው በተገኘው መረጃ መሠረት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን የፖለቲካ ጥገኝነት እንዳቀረበ በግልጽ የታወቀ ጉዳይ ሆኖ ያለ ጉዳይ ቢሆንም በማኅበራዊው የብዙኃን መገናኛው የ“መንግሥት” ደጋፊዎች የሆኑቱ የረዳት አብራሪውን የኃይለ መድኅንን ጉዳይ ኢሳትን በመሳሰሉ የብዙኃን መገናኛዎች ፖለቲካዊ ገጽታ ተሰጥቶት በማየታቸው ስሕተት መሆኑን በመኮነን ሲናገሩ ተስተውለዋል፡፡ ማስተዋል ካለመቻላቸው ይሁን የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቅ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ካለማወቃቸው ሊገባኝ አልቻለም፡፡
ጥቂቶት የመንግሥት ደጋፊዎች እና “መንግሥት” ግን ይህ ጉዳይ ምን ማለት እንደሆነ በሚገባ ገብቷቸዋል፡፡ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድም የሠጉት ትርጉም እንዳይወሰድና ስማቸው አሁን ካለበት ደረጃ ይብስ እንዳይጠፋ ያደረጉ መስሏቸው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ይህንን እርምጃ በወሰደበት ወቅት በደኅና በትክክለኛ (normal) የአእምሮ ጤና ላይ እንዳልነበረና ሱሰኛም እንደሆነ በዚህም ምክንያት ድርጊቱን እንደፈጸመ በማስረዳት ለመከላከል እየሞከሩ ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ድርጊታቸው ከድጡ ወደ ማጡ መሆኑን አልተረዱም አልተገነዘቡም፡፡ ድርጊታቸው ፈጽሞ ኃላፊነት የጎደለውና አርቆ ማሰብ የተሳነው፣ አየር መንገዱንም ለከፍተኛ ኪሳራ የሚዳርግ የደነቆረ ማስተባበያ ነው፡፡ ምክንያቱም ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን እንዲህ እንዳሉት ዓይነት ሱሰኛና ሥራውን በትክክል ለመሥራት በማያስችል የመንፈስ ጭንቀትም ሆነ የሥነ ልቡና መታወክ እንዳለበት እየታወቀ ሥራ ላይ በማሠማራት በመቶዎች የሚቆጠሩ ደንበኞቹን ደኅንነት ለአደጋ አጋልጧል የሚል ትርጉም እንደሚያሰጠውና አየር መንገዱ ለደንበኞቹ ደኅንነት የማያስብ የማይገደው የማይጠነቀቅ ኃላፊነት የማይሰማው እንደሆነ ተቆጥሮ ለዘመናት በብዙ ድካም የገነባውን መልካም ስም እንደሚያጠፋው ደንበኞቹንም እንዲያጣ እንደሚያደርገው ያልተረዱና መረዳት የማይችሉ ሰዎች የደነቆረ አርቆ ማሰብ የተሳነው ስም ማጥፋት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሥራየ ብለው ይህንን ስም ማጥፋት ያደረጉትና እያደረጉም ያሉት ደናቁርት አየር መንገዱ ለሚደርስበት ጉዳትና ኪሳራ ኃላፊነቱን የሚወስዱ ይሆናሉ፡፡
በሌላ በኩል በእርግጥም እንደተባለው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን የአውሮፕላኑን አቅጣጫ መቀየር ሳያስፈልገው በራሱ በግሉ በፈለገው ሀገር ላይ በሔደበት ጥገኝነት ጠይቆ መቅረት የሚችል ሰው ነበር፡፡ እንደኔ ግምት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ይህንን ያደረገበት ምክንያት ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉት፡፡ የአውሮፕላኑን አቅጣጫ ከሮም ወደ ስዊዘርላንድ ማድረጉና ጥገኝነቱን እዚያ መጠየቁ ሲጠይቅም አውሮፕላኑን መያዙ መውሰዱ ምክንያቱ አንደኛው ሽንት ቤት ሲገባ የቆለፈበት ዋናው አብራሪ ጣሊያናዊ በመሆኑ ለሚያቀርበው የፖለቲካ ጥገኝነት በቂም ምክንያት እንቅፋት እንዳይሆነው በመሥጋቱ ሲሆን ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን በሄደበት ቀርቶ ብቻውን መጠየቅ ሲችል ይሄንን ያላገረገበት ምክንያት ጉዳዩ የሱ የግሉ ጉዳይ ሆኖ እንዲቀር ስላልፈለገ፣ ይህ እሱን ያሰቀቀውና ያንገላታው ችግር የሱ ችግር ብቻ አይደለምና አውሮፕላኑን በመውሰድ የኢትዮጵያን ሕዝብ አቤቱታ በአደባባይ አጉልቶ በማሰማት እንዲያቀርብ አድርጎታል፡፡
ይህ ሰው እንደሌሎቻችን ሁሉ ሆዳም ቢሆን ኖሮ የያዘው የሙያና የኑሮ ደረጃ አይደለም በኢትዮጵያ በየትኛውም ሀገር ቢሆን ተንደላቆ ተንቀባሮ መኖር የሚያስችለው ደረጃ ነበረው፡፡ ነገር ግን ልጁ ሰው ነውና፣ ባለ ሕሊና ነውና፣ ጭንቅላት ያለው ዜጋ ነውና፣ አስተዋይ ነውና ሕዝቡ ወገኑ በችጋርና በሰብአዊ መብቶች እጦት እየተሰቃየ እያየ የሚበላውና የሚጠጣው ሊዋጥለት አልችል አለው፡፡ ምቾቱ ሊደላው አልቻለም፡፡ በአፍንጫየ ይውጣ አለ፡፡ አለና ድሎት ያለውን ሕይዎቱን መሥዋዕት አድርጎ በአስደናቂ ብቃትና አፈጻጸም የሕዝብን አቤቱታ በተገቢው ቦታና ሁኔታ ለዓለም ሕዝብ አቀረበ አሰማ፡፡
አዎ ይሄም እውነት ነው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራ ከሀዲ ነው፡፡ ግፈኛ አገዛዝን አላገለግልም ብሎ የግፍ አገዛዙን ክዷልና፡፡ ይህ አሁን እሱ ያደረገው ሥራ የሰላማዊ ትግል መሐንዲስ የሆነው ጋንዲ ለስኬት የበቃበት የሰላማዊ ትግል አንዱ ዓይነት እርምጃ ነው፡፡ ከተጠቀምንበትና ሁላችንም ከተባበርን የረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅንን አርአያነት ከወሰድን፡፡ ወያኔን በጣት በሚቆጠሩ ቀናት ውስጥ ብቻ እጅ እንዲሰጥ ማድረግ አቅሙን ጨካኝ ጉልበቱን ማሽመድመድ ይቻላል፡፡ እስከመቸ ነው እሽሩሩው? እስከመቸ ነው ትዕግሥቱ? እስከመቸ ነው መቻሉ? መጨረሻ የለውም እንዴ? ልክ የለውም እንዴ? በዚህ ሁኔታ ትውልድ እያለፈ ትውልድ መተካት አለበት እንዴ? ሁሉም ነገር ቢሆን እኮ ልክና መጨረሻ ገደብም አለው፡፡ ትዕግሥታችን እሽሩሩአችን መቻላችን መጨረሻ ገደብና ልክ ካለው ጊዜው አሁን ነው ጊዜው ዛሬ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የምንጨምራቸው ጊዜያት የሚባክኑ ብቻ ሳይሆኑ ህልውናችንን የሚያስከፍሉ የሚበሉ የሚያጠፉ የጥፋት የመዓት ቀናት ጊዜያት ዘመናት ናቸው፡፡
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
በተናጠል የሚወሰዱ እርምጃዎች የትም አያደርሱንም፡፡ የዚህን ጀግና እርምጃ ዐይተን አድንቀን መቀመጡ ምንም አይጠቅመንም እሱ ትልቁን እርምጃ ተራምዶ ጀምሮልናል የግድ መከተል ይኖርብና፡፡ ይሄኔ ሀገርን ሕዝብን እራሳችንን ነጻ እናወጣለን፡፡ ነጻ ነጻ ነጻ እንሆናለን እኛም ወግ ይደርሰንና ለሥልጣኔ ሽምጥ እንጋልባለን፡፡ የነጻነት ፍሬዎችን ልማትን፣ ሰላምን፣ አስተማማኝ ደኅንነትን፣ ምቾትን፣ ጤናን፣ ፍቅርን እናጣጥማለን እንኮመኩማለን፡፡ ሥጋትን፣ ፍርሐትን፣ ጭቆናን፣ እንግልትን፣ አፈናን፣ እረገጣን፣ መብት መነፈግን፣ ረሀብን፣ ችጋርን፣ ጉስቁልናን፣ አንገት አስደፊውን አዋራጁን ድህነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ቶሎ እናሰናብታለን እንቀብራለን፡፡ ይህች ሀገር ከራሷ አልፋ ለስንት የሚበቃ ሲሳይ በረከት አላት፡፡ ሕዝብ የተቸገረው የተራበው የሚጠማው ስለሌለን አይደለም፡፡ በጨካኝና አንባገነን አገዛዙ ተዘግቶብን፣ ተይዞብን፣ ተቆልፎብን፣ ተከልክለን፣ ተነፍገን ነው እንጂ፡፡ እውነት እንዳይመስላቹህ ድሆች አይደለንም በፍጹም ምንም የሚቸግረን ነገር አልነበረም፡፡
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
amsalugkidan@gmail.com (ፎቶ: ሪፖርተር)

No comments:

Post a Comment