Tuesday, August 19, 2014

ያገር ፍቅር ልክፍት – በዶክተር ኃይሉ አርአያ


dr hailu areaya

ከእናቴ ማህፀን ነው ስፈጠር ከጥንቱ
ከህይወት መስመሩ ካገኘን ከእትብቱ ፡፡
ወይስ ከእናቴ ጡት ካይኖቿ እይታ
ከየት ነው ያገኘኝ ከቶ ከምን ቦታ
ያገር ፍቅር ልክፍት ያገር ፈቅርበሽታ፡፡
ከረገጥኩት መሬት በውስጥ እግሬ ገባ
ወይስ በጠዋት ፀሀይ ተወጋሁ ከጀርባ፡፡
ከበላሁት ቆሎ ጠረሾ አምባሻ
ከእንጀራ ከሽሮው ጥልቅ የእናት ጉርሻ፡፡
ከጠጣሁት ወተት ከጠጣሁት ውሃ
ከእረኝነት ውሎ ከዱር ከበረሀ፡፡
በነሀሴ ምሽት በቡሄ ጨለማ
ሁያሁዬ ስንል አሲዮ ቤሌማ፡፡
እደጉ ልጆቼ ብለው ሲያቀብሉን
የቡሄ በረከት የዳቦ ሙልሙሉን፡፡
ከሙልሙሉ ይሆን ከቃናው ከጣዕሙ
ወይስ ከምረቃው ከቃል ከትርጉሙ፡፡
ከቶ ከየት ይሆን ከምኑ ከስንቱ
ሳላውቀው የነካኝ ያገር ፍቅር ልክፍቱ፡፡
ቄስ ትምህርት ቤት ይሆን ከየንታ ቤት ታዛ
‹‹ሀ ሁ››ስል‹‹ለ ሉ››ስል ፊደልን ሳበዛ፡፡
በቀለም በፊደል በነጥብ ተመስሎ
በውስጤ የገባ ዓይነ ኩሌን ከፍሎ፡፡
ወይስ ውሎ አድሮ ነው ከፊደል በኋላ
የንታን‹‹ሄድኩኝ››ብዬ ስገባ ካአስኳላ፡፡
ገባ በጆሮዬ ተመስሎ ዜማ
‹‹ኢትዮጵያ ሆይ›› ብለው ሲጠሯት ስሰማ፡፡
‹‹ተጠማጅ አርበኛ ባገር መውደድ ቀንበር››
ለሶስቱ ቀለማት በሰልፍ ሲዘመር፡፡
አረንጓዴ ቦጫ ቀይ ቀለም ባንዲራ
ስትወጣና ስትወርድ ስንዘምር በጋራ፡፡
በክፍል ውስጥ ይሆን በእውቀቱ ገበታ
ሳላውቀው ሳላስበው ልቤ የተመታ ፡፡
ከመፅሀፉ ይሆን ከታሪክ ፀሀፊ
ወይስ ከመምህሩ ከዚያ ዕውቀት አስፋፊ
ባገር ፍቅር ልክፍት ተለክፎ አስለካፊ፡፡


No comments:

Post a Comment