Wednesday, November 12, 2014

የገቢዎችና ጉምሩክ ከፍተኛ ኦፊሰር ጉቦ ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ ተያዙ

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ቃሊቲ ጉምሩክ ጽሕፈት ቤት ከፍተኛ ኦፊሰር፣ አቶ ዘመን ይሰማው 40,000 ብር ጉቦ ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ ተይዘዋል በሚል ተጠርጥረው ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
cuffsየፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በተጠርጣሪው ላይ የመሠረተው ክስ እንደሚያስረዳው፣ የፈረንሣይ ኤምባሲ ሠራተኛ በነበሩት በሚስተር ሚሼል ሪቻርድ ስም የገባ ተሽከርካሪን፣ አቶ ተዋበ ዘለቀ የተባሉ ግለሰብ በ450,000 ብር ይገዛሉ፡፡
ግለሰቡ ተሽከርካሪውን ከገዙ በኋላ የመንግሥት ቀረጥና ታክስ ለመክፈል ወደ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ የባለሥልጣኑ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ይሄዳሉ፡፡ የሦስት ዓመታት ግብርና ታክስ 439,586 ብር እንዲከፍሉ ተጠርጣሪው እንደገለጹላቸው ክሱ ያስረዳል፡፡
ግለሰቡም በተጠየቁት መሠረት ክፍያውን ይፈጽማሉ፡፡ ተጠርጣሪው ኦፊሰር ተጨማሪ 146,000 ብር መክፈል እንዳለባቸው ይገልጹላቸውና 60,000 ብር ከሰጧቸው ግን እሳቸው እንደሚጨርሱላቸው ሲገልጹላቸው፣ በሐሳቡ በመስማማት ቅድሚያ ክፍያ 40,000 ብር ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ መያዛቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ ክስ ለመስማት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ለታህሳስ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ቀጠሮ ይዟል፡፡

No comments:

Post a Comment