Wednesday, November 7, 2012

ህዝብን በህትመት ነፃነት ማፈን አይቻልም !!!

                  በፍራቻ የሚነጥፍ ብዕርም ሆነ በአፈና የሚንበረከክ የትግል ማንነት የለንም!ኢህአዴግ ከአቶ መለስ ሞት በኋላ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስቴር አስቀምጧል፡፡ እንደ  አለመታደል ሆኖ ግን አዲሱም ሰው የሟቹን ጠቅላይ ሚኒስትር ዱካ የሚከተሉ፣ መለስ የጀመሩትን አፈና የሚያስቀጥሉ፣በመለስ የሙት መንፈስ የሚመሩ በመሆናቸው አሁንም በኢትዮጵያችን አንጻራዊ የሚባል እንኳ ለውጥ ለማየት አልቻልንም፡፡በተለይም “አዲሱ” መንግስት ስርዓቱን የሚተቹ ጋዜጦችን ከአደባባይ በማጥፋት የሀገሪቱን የፕሬስ ነፃነት ጉዞ ክፉኛ ወደኋላ መመለሱ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን የሚያስከትል መሆኑን ከግምት ያስገባ አይደለም፡፡

                  የአቶ መለስ ሞት ይፋ ከመሆኑ አስቀድሞ በውጪ መገናኛ ከተነገረ ቆይቷል የጠ/ሚኒስትሩ ሞት በመንግስት ይፋ ከተደረገ በኋላ ደግሞ ይህ እቀባ በሀገራችን ኢትዮጵያ የፕሬስ ነፃነት እና የመደራጀት መብት ቦታ እንዲኖራቸው አምባገነኑ የኢህአዴግ መንግስት እንደማይፈልግ በማያወላዳ ሁኔታ በተግባር የገለፀበት ነው፡፡ይህን አይነቱን ስርአት የሚሸከም ጫንቃ እንደሌለን በተግባር የመግለፅ ኃላፊነትም ሆነ ግዴታ እንዳለብን እንረዳለን፡፡ ስለሆነም ስርዓቱ ለሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ደንታቢስ መሆኑ የትግል መንፈስን የሚያጠናክር እንጂ ተስፋ አስቆራጭ ሊሆን እንደማይችል በተለያዩ ሰላማዊ የመብት ማስከበሪያ ትግሎች ለኢህአዴግ ልናረጋግጥለት ይገባል፡፡መለስ ዜናዊ የገነቡት አፋኝ ስርዓት ከሰውየውጋር ቢቀበር የነፃነት ናፋቂ የኢትዮጵያዊያን ሁሉ ምኞት ነበር፡፡ ሆኖም የመለስ ሞት የመንግስቱን ስልታዊ አምባገነንነት ቀመር በማሳጣቱ አሁን ያሉት አንባገነኖች ያፈጠጠና ያገጠጠ የአፈና ተግባር ውስጥ ገብተዋል፡፡በጋዜጦቻችን የሚንፀባረቁት የነፃነት ጥያቄዎች የህዝብ ናቸው፡፡ የህትመት  ጋዜጣን በማፈን የህዝብን የለውጥ ፍላጐት ማፈን እንደማይቻል ስርአቱ በሚገባው ቋንቋ ሊነገረው ይገባል የምንለውም ለዚሁ ነው፡፡ ራሱ የሚለውን እንደገደል ማሚቶ የሚያስተጋቡ አድርባይነትን ዋንኛ ተግባራቸው ያደረጉና ከስርአቱ በተለያየ ደረጃ የሚጠቀሙ ሆድ አደር የመገናኛ ብዙሃንን በመደገፍ፤ በአንፃሩ ለህዝብ አማራጭ በመሆን በስርዓቱ ላይ ትችት የሚያሰሙትን መርጦ ማፈንና ማዳከም ኢህአዴግ ለሚመራው መንግስት አደገኛ ውጤት እንደሚኖረው መገንዘብ ያስፈልጋል ፡፡በሀገራችን ለተረገጡት መብቶች እንዲከበሩ ሁነኛው መፍትሄ ኢትዮጵያን በአፈና ቀንበር ስር ያደረገውን አምባገነን ስርዓት ማስወገድ እንደሆነ እናምናለን፡፡ 

ለፍትህ  በሚያስተባብራቸው ሰላማዊ የትግል አቅጣጫዎች በመሳተፍ ሁሉን አቀፍ የመብት ማስከበር ትግል ማድረግ አማራጭ ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ መሆን አለበት፡፡  በህትመት ዙሪያ የሚፅፉትን የመንግስት የደህንነት አባላትና ማንነታቸው የማይታወቅ ግለሰቦች የተለያዩ ዛቻዎችና ማስፈራሪያዎችን ያለማቋረጥ ሲያደርሱባቸው ቆይተዋል፡፡ በተለይ የአቶ መለስ ሞት ውስጥ ውስጡን መሰማት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ጋዜጠኞቻችን ላይ የሚደርሱት ዛቻና ማስፈራሪያዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በጋዜጣ ላይ የሚፅፉትን እንዲሁም አዘጋጆች ላይ የግድያ ዛቻ የደረሰ ሲሆን የእገታ ሙከራም ተደርጓል፡፡ ይህ ድርጊት የሚያሳየው በኢትዮጵያ ጋዜጠኝነት ምን ያህል ፈታኝ እንደሆነ ነው፡፡በአሁን ሰዓትም ምንም ነፃ  ጋዜጣ  እንዳይታተም ተደርጓል።

    አምባገነኖቹ ባለስልጣናት ልብገዝተው ለህትመት ያላቸውን ነፃነት እንዲሰጡ አሁንም እንጠይቃለን ሆኖም መብታችንን ለማስከበር የተለያዩ ሰላማዊ ትግሎችን በማድረግ ህትመት ነፃ ሆኖ መንግስት ጣልቃ እንዳይገባ  እንተጋለን፡፡
አሁንም ለመንግስት የምንገልፀው በፍራቻ የሚነጥፍ ብዕርም ሆነ በአፈና የሚንበረከክ ማንነት እንደሌለን ነው። ነፃነት ለኢትዮጵያ ህዝብ !! ህዝብን በህትመት ነፃነት ማፈን አይቻልም !!!
 ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!
              ከዘካሪያስ



No comments:

Post a Comment