Wednesday, December 4, 2013

በአዲስ አበባ በሥጋ ውጤቶች ላይ ሊጣል የታሰበው ግብር እያወዛገበ ነው


·       የሥጋን ዋጋ እንዳያንረው አስግቷል

በፀጋው መላኩ

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከስጋ ነጋዴዎች ግብርን ለመሰብሰብ ቀደም ሲል ሲጠቀምት የነበረውን የቁርጥ ግብር አሰራር በመቀየር አንድ ነጋዴ በሬ በቄራ ካሳረዱ በኋላ ተጣርቶ በሚሸጠው የሥጋ መጠን ግብር ለመጣል እንቅስቃሴን በመጀመሩ አሰራሩ ውዝግብን አስነስቷል። ባለስልጣን መስሪያቤቱ ግብሩን ለመጣል አንድ በሬ ከእርድ በኋላ የሚወገደው ተወግዶ ምን ያህል ኪሎ የተጣራ ክብደት ይኖረዋል የሚለውን መረጃ ለመሰብሰብ ለአዲስ አበባ ቄራዎች ጥያቄ ማቅረቡን ተከትሎ በቄራዎች ድርጅት በኩል ለገቢዎች የተላከው የክብደት ግምት መጠን መጋነን ለውዝግቡን መነሻ መሆኑ ታውቋል።
በዚሁ ዙሪያ ማብራሪያ የሰጡን የአዲስ አበባ ሉካንዳ ነጋዴዎች ማህበር የህግ ክፍል ኃላፊ አቶ አየለ ሳህሌ፤ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከቄራዎች ድርጅት ያገኘውን የበሬ ስጋ የተጣራ ክብደት መሰረት በማድረግ የሰራው የግብር ሂሳብ በዘርፉ ያሉ ነጋዴዎችን ከገበያ የሚያስወጣ ብሎም በተጠቃሚው ላይም ተጨማሪ ዋጋን እንዲጠይቅ የሚያደርግ በመሆኑ አግባብነት የለውም ብለዋል። “የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት የእርድ አገልግሎት ከመስጠት ውጪ አንድም ቀን የደንበኞችን የእርድ በሬም ሆነ የስጋ ክብደት መዝኖ አያውቅም” ያሉት አቶ አየለ “ከምን መረጃ ተነስቶ የአንድ በሬ የተጣራ የስጋ ክብደት ይሄንን ያህል ኪሎ ነው በማለት የቄራዎች ድርጅት ለገቢዎችና ጉምሩክ መረጃ እንደሰጠ አይታወቅም ብለዋል”። የህግ ባለሙያው የባለስልጣን መስሪያቤቱ ራሱ መረጃውን ከነጋዴውም ሆነ ከማህበሩ ማግኘት እየቻለ ለምን በሌላ መንገድ መሄድ እንደፈለገ ግልፅ አይደለም በማለት ወቀሳቸውን በባለስልጣን መስሪያቤቱ ላይ አቅርበዋል።
እንደ አቶ አየለ ገለፃ ገቢዎችና ጉምሩክ ግብሩን ለመጣል በተነሳበት ወቅት የመነሻ የግምት መረጃውን ከየት እንዳገኘ ሲጠየቅ ከአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ከአንድ የስራ ሂደት ቢሮ የተፃፈ ደብዳቤን በማሳየት መረጃው ከትክክለኛ ምንጭ የተገኘ መሆኑን አስረድቷል። ደብዳቤውን የተመለከቱት የአዲስ አበባ ሉካንዳ ነጋዴዎች ማህበር አባላትም የደብዳቤውን ኮፒ ከአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ካገኙ በኋላ በኮፒ አባዝተው ለነጋዴዎቹ በትነዋል።
እንደ አቶ አየለ ገለፃ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ባገኘው የአንድ በሬ የተጣራ አማካኝ የስጋ ክብደት ከ450 እስከ 500 ኪሎ ግራም ነው በሚል ግምት ነው ግብሩን ወደ መሬት ለማውረድ የሞከረው። ይህምመረጃ ትክክል አለመሆኑን እንዲሁም ቄራዎች ድርጅትም ቢሆን ለደንበኞች የእርድ አገልግሎት ከመስጠት ውጪ የታረደ የከብት ስጋን የሚመዝንበት አሰራር የለም በሚል በማህበሩ አባላት ተቃውሞ ከተሰማ በኋላ ቄራዎች ድርጅቱ ቀደም ሲል ያስቀመጠውን የተጣራ የስጋ ክብደት መጠን በተወሰነ ደረጃ ዝቅ በማድረግ መልሶ ለባለስልጣን መስሪያቤቱ ደብዳቤ የፃፈ መሆኑ ታውቋል። እንደ አቶ አየለ ገለፃ ስጋ መዝኖ ለማያውቅ ድርጅት ሁለተኛው ግምት ቢሆን ትክክል አይደለም።
በዚሁ ዙሪያ በስልክ ማብራሪያ የሰጡት የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት የእርድ አገልግሎትና የስጋ ሽያጭ የሥራ ሂደት ዳይሬክተር አቶ ተኮላ ኃይሉ፤ የቄራዎች ድርጅት የተጣራ የስጋ ክብደትን በተመለከተ ለገቢዎችና ጉምሩክ መረጃን የሰጠው ለመነሻነት ብቻ እንዲጠቀምበት እንጂ በመረጃው ብቻ ተመርኩዞ ግብርን በነጋዴዎቹ ላይ እንዲጥል አልነበረም ብለዋል። ድርጅቱም የደንበኞቹን ሥጋ መዝኖ የማያውቅ በመሆኑ የተሰጠው መረጃ ከሙያና ከልምድ አንጻር በንድፈ ሀሳብ (theory) ላይ ብቻ የተመረኮዘ እንደነበር አቶ ተኮላ አረጋግጠዋል። መረጃውም ባለስልጣን መስሪያቤቱ በጠየቀው መሰረት ሲሰጠው የቄራዎች ድርጅትን መረጃ ብቻ በመነሻነት በመጠቀም ነጋዴው ላይ በቀጥታ ግብር እንዲጥል ሳይሆን የቄራዎች ድርጅት መረጃ እንደ አንድ ግብዓት ተወስዶ እንዲሁም ሌሎች ጥናቶችን በጥልቀት በማካሄድና ከነጋዴው ማህበረሰብ ጋርም የምክክርን መድረክ በመክፈት በሚወስደው ግብዓት መሰረት የግብሩ ሂሳብ ይሰራል በሚል ግምት እንደነበር ኃላፊው አመልክተዋል።
አቶ ተኮላ የሥጋ ምርት እንደበሬው ሁኔታና እንደሚሸጥበት አካባቢ የሚለያይ በመሆኑ ይህ ሁሉ ታሳቢ ሳይደረግ ግብርን መጣሉ የሥጋን ዋጋ በአጠቃላይ በማናር ተጠቃሚውን የሚጎዳ እንደዚሁም ነጋዴዎችን ከገበያ የሚያስወጣ መሆኑን ገልጸዋል። ከአፍሪካ ሀገራት ሳይቀር በዝቅተኛ ሥጋ ተመጋቢነቱ የሚታወቀውን ህዝብ የበለጠ የተመጋቢነቱን መጠን የሚቀንስበት ሁኔታም ይኖራል ብለዋል።
በዚሁ ዙሪያ ማብራሪያ የሰጡት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ በከር ሻሌ የአንድ የእርድ እንስሳ በመጨረሻ ተጣርቶ በኪሎ የሚሸጠውን የስጋ መጠንን በተመለከተ በባለስልጣን መሥሪያቤቱና በነጋዴዎች መካከል ልዩነት የተፈጠረ መሆኑን ገልጸው፤ ችግሩም ከነጋዴውጋር ተቀራርቦ በጋራ ለመፍታት መሥሪያቤታቸው ከሉኳንዳ ቤት ባለቤቶች ለመወያየት ያሰበ መሆኑን አመልክተዋል። ችግሩ ይህ ብቻም ሳይሆን ነጋዴዎች የቁም እንስሳትን ከገበሬው ሲገዙ ደረሰኝ የማያገኙበት ሁኔታም ስላለ በዚህም ዙሪያ መስሪያቤቱ መፍትሄ ለማፈላለግ እንቅስቃሴ የሚጀምር መሆኑን አቶ በከር ጨምረው ገልፀዋል።

No comments:

Post a Comment