Friday, July 18, 2014

ችቦዉ ተለኩሷል የበለጠ ማቀጣጠሉ ወይም ማጥፋቱ የኛ ምርጫ ይሆናል !

አሁን በስልጣን ላይ ያለዉ የሕወሃት መንግስት ብቻ ሳይሆን ሌሎችም ሕዝብን በግፍ የሚገዙ አምባገነኖች ለስልጣናቸዉ ማራዘሚያ የሚጠቀሙበት ትላልቅ መሳሪያዎች ፍርሃትና ህዝብን መከፋፈል ነዉ።
ሕወሃት ስልጣን ከጨበጠ ከጅምሩ በኢትዮጵያ የዘረጋዉ ፖለቲካ በዘር ላይ የተመሰረተ ከፋፋይ ፖለቲካ ነዉ። ኢትዮጵያ የብዙ ብሄረሰብ አገር ናት። በታሪኳ የተሰሩ ብዙ ስህተቶችና በደሎች አሉ። በአንጻሩም ደግሞ ኢትዮጵያዉያን ከተለያዩ ቋንቋዎችና ክልሎች በሰላም በፍቅር ኖረዋል፣ ተዋደዋል፣ ተደባልቀዋል። በጋራ የዉጭ ወራሪ ኅይላትን መክተዋል።
የሕወሃት መንግስት ኢትዮጵያዉያን በጋራ የሰሩትን አጉልቶ አንድነትን ከማጠናከር ይልቅ ልዩነቶቻቸዉን አቻችለዉ ከዚህ በፊት በተሰሩት ስህተቶች ይቀር ተባብለዉና ካለፈዉ ትምህርት ቀስመዉ ፣ አንዱ የአንዱ ቋንቋ ባህል አክብሮና ተረዳድቶ እንዲኖር ከማድረግ ይልቅ እርስ በርስ ህዝቡን በመከፍፋፈል ወገን ከወገን ወንድም ከወንድም ማጣላቱን ስራቸዉ አድርገዋል። ጣሊያን አምስት አመት ኢትዮጵያን ወሮ በነበረ ጊዜ እንዳደረገዉ ትግሬ ፣ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ሱማሌ እያሉ ሕዝቡን በዘር ሸነሸኑት።

ይህንንም ያደረጉት ለቤሄረሰቦች ወይንም ለተለያዩ የቡድን መብቶች በማሰብ አልነበረም። ለምን ቢባል የቡድን መብቶች አገር ሳትከፋፈል የግልሰብ መብቶችን በማክበር ሊጠበቁ ስለሚችሉ። ነገር ግን ይህ በዘር ላይ የተመሰረተ ክፍፍል የተዘረጋዉ ሕዝብን በግፍ በአምባገነንነት ለመግዛት ስለተፈለገ ብቻ ነዉ።
ኢትዮጵያውያንን በዘር በመከፋፈል በትንሹም ቢሆን አንድ የሚያደርገን ላይ ከማተኮር ይልቅ የሚለያዩን ጎሳና ዘራችን ላይ እንድናተኩርና በጋራ ለሁላችንም እኩል የሆነች ኢትዮጵያን ከመመስረት ይልቅ ያለፈዉ ታሪካችንና ያለፈዉ በደላችን በማስታወስ አንዳችን በአንዳችን ላይ እንድንነሳ በማድረግ ሕዝቡን አፍኖ ለመግዛት እንዲያስችላቸዉ ነዉ ሕወሃት ይህን እኩይ የመከፋፈል ተግብራት ሲያደርግ የሰነበተዉ።
በምርጫ ዘጠና ሰባት ኢትዮጵያዉያን ቅንጅትን ሲመርጡ የመረጡት ኢትዮጵያዊነት ነበር። «እርግጥ ነዉ ኦሮሞ ነን፣ እርግጥ ነዉ ጉራጌ ነን፣ እርግጥ ነዉ አማራ ነን ፣ እርግጥ ነዉ ድብልቆች ነን … ነገር ግን ከሁሉም በላይ ኢትዮጵያዊ ነን» ብለዉ ነዉ፣ ኢትዮጵያዊነትን የፖለቲካዉ የማእዘን ድንጋይ አድርጎ የተነሳዉን ቅንጅትን የመረጡት።
ታዲያ ቅንጅት የተከፋፈልነዉን አንድ ለማድረግ ተንቀሳቅሶ ሲመጣ ገዥዉ ፓርቲ ሴራዉ እንደከሸፈበት አወቀ። የቅንጅት መሪዎችን እሥር ቤት ከተተ። ትግሬን ለማጥፋት እንደተነሱ አድርጎ የዉሸትና የረከሰ ፕሮፖጋንዳ መንዛት ጀመረ። የዘር ማጥፋት ወንጀል ክስ አቀረበ። ኢትዮጵያዉያን ሲከፋፈሉ ብቻ ስለሆነ ጥንካሪያቸዉ የሕወሃት ባለሥልጣናት የትግራይን ሕዝብ ከተቀረዉ ኢትዮጵያዊ የመለየትና የማቃቃር ሰይጣናዊ ሥራቸዉን አጧጧፉ። በትግራይና በተቀረዉ ኢትዮጵያ ክፍል መካከል የጥላቻ ግድግዳ ለመዘርጋት ሞከሩ።
የቴዎድሮስ አፍሮ ጉዳይ እንግዲህ የሚመጣዉ እዚህ ላይ ነዉ። የሕወሃት ከፋፋይ ቂም በቀልና እልህ ላይ የተመረኮዘ ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነን ፖለቲካን በዜማዉ መሸርሸሩ ሕወሃትን አስቆጣ። «ለዓለም ለዓለም እንዳይለያየን ዘለዓለም» እያለ መለያየታችን ትተን ለአንዲት ኢትዮጵያ በጋራ እንድንሰራ፣ ይቀር እንድንባባል አስተማረ። ከተተኮሰ ፈንጅና ከተወረወረ ቦምብ በበለጠ ሁኔታ የቴዲ አፍሮ የፍቅርንና የሰላም እንዲሁም የኢትዮጵያዊነት ዜማ በሕወሃት ኃላቀር ፖለቲካ ላይ ክስረትን አመጣ።
ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ከትግል አጋሮቻቸዉ ጋር ኢትዮጵያዊነትን አንግበዉ የፍቅርንና የሰላም ፖለቲካ ለማራመድ የቅንጅት ዓላማና ራዕይ ይዘዉ «አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ» በሚል ስም መንቀሳቀስ ጀመሩ። ወገን ከወገን ለመከፋፈል የተዘረጋዉን የመከፋፈልና የጥላቻ ግንብ ማፈራረሱ ላይ አተኮሩ።
«የአገዛዙ መሳሪያና ትጥቅ ከሕዝብ ጉልበት ጋር ሲነጻጸር ኢምንት ነዉ። አገዛዙ ወደደም ጠላም ለሕዝብ ጥያቄ እራሱን ያስገዛል» እያሉ ሕዝቡን ማስተማር ጀመሩ። ሕዝብ በራሱ እንዲተማመንና ከፍርሃት እንዲላቀቀ ራሳቸዉ ምሳሌ እየሆኑ ማሳየት ጀመሩ፡ ሕግን ያከብራሉ የተባሉት ሕግን ሲረግጡ አላይም በማለት ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ሰላማዊ እምቢተኝነትን አወጁ። የሚፈሩት አምላካቸዉንና ሕሊናቸዉን እንጂ በጉልበት ባርያ አድርገዉ ሊገዛቸዉ የሚፈልገዉን አምባገነን እንደማይፈሩና ለእዉነት ለሕግ የበላይነት እንደቆሙ አስመሰከሩ። ባርነትን «እምቢ»፣ ጭቆናን «እምቢ»፣ ፍርሃትን «እምቢ» ብለዉ ብቻቸዉን የታጠቀዉን ሕወሃትን ገጠሙ።
ይህ ትልቅ የፖለቲካ ድፍርት እጅግ የሚያስደንቅና የሚያስከበር እንደመሆኑ በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን ምሳሌ ሆነ። የወ/ት ብርቱካን ድፍረት ድምጽ አዉጥቶ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩትን በፉጨት ጠራ። ሕዝብን የሚያነቃቃና የሚያነሳሳ አኩሪና ታሪካ ድርጊት ነዉ።
ሕዝብ ከተነሳና ከተነቃቃ ድፍረት አግኘቶ ከፍርሃት ከተላቀቀ የአምባገነኖች ፍጻሜ እጅግ ቅርብ ይሆናል። ከተተኮሰ ፈንጂና ከተወረወረ ቦምብ በበለጠ ይህ የወ/ት ብርቱካን ሰላማዊ እምቢተኝነት ለሕወሃት ትልቅ የፖለቲካ ክስረትና ዉስጣዊ ነዉጥን ፈጥረ። የሕወሃት አመራር አባላት እርስ በርስ እንዲከፋፈሉና የሚያደርጉት ግራ እስኪገባቸዉ ድረስ ትርምስን በዉስጣቸዉ አመጣ። በአለም ሕብረተሰብ ዘንድ እንዲያፍሩ እንዲዋረዱ አደረገ። በርግጥ ጠመንጃ ሳይያዝ ጠመንጃ የያዘን ማብረክረክ እንደሚቻል በገሃድ ታየ።
የወ/ት ብርቱካንና ሌሎች የፖለቲካ እሥረኞች መታሰር በሰብዓዊነት ሲታይ የሚያስዝንና በጣም የሚያስቆጣ ነዉ። ነገር ግን መታሰራቸዉ በኢትዮጵያ ለዉጥ እንዲመጣ ለማድረግ ትልቅ መልካም አጋጣሚን ፈጠሯል። ሕወሃት ለመከፋፈል ሲሞክር የነበርቱካን መታሰር ሕዝቡ ተቆጥቶ እንዲነሳና በአንድ ላይ እንዲመጣ አድርጎታል። የኢትዮጵያዉያንን መተባበር እያየን ነዉ።
የሕዝብ ገንዘብን የዘረፈ እንደመሆኑ ሕወሃት ለእኩይ ተግርባራቱ የሚያሰማራቸዉ በርካታ ሕሊናቸዉ የሸጡ ግለሰቦች አሉ። እነዚህ ግለሰቦች አሁንም ያገኙትን ትንሽ ቀዳዳ በመጠቀም ኢትዮጵያዉያንን ለመከፋፈል ያለ የሌለ ጥረት ከማድረግ ወደ ኋላ አይሉም። በትግል ስልት ዙሪያ እንደንጨቃጨቅ ፣ ድሮ የተሰሩ ስራዎችን መልሰን እያመጣን እንድንካስስና በዘር በኃያማኖት እንድንለያይ ይሞክራሉ።
የሕወሃት መንግስት እስከአሁን በሥልጣን ላይ ያለዉ እኛ ደሞክራሲን በኢትዮጵያ እንዲመጣ የምንፈልግ ኃይሎችን መከፋፈልና ማዳከም በመቻሉ እንደሆነ ተገንዝበን የበለጠ አንድነታችንን በቅንነት ማጠናከሩ ላይ መበርታት አለብን።
በቅርቡ በውጭ አገር ያሉ በርካታ የፖለቲካና የሲቪክ ማህበራት የወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ተዲ አፍሮ፣ አቶ በቀለ ጂራታና ሌሎች የፖለቲካ እሥረኞች በግፍ መታሰርን በማወገዝ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ ባወጡት የጋራ መግለጫ ጠይቀዋል።
ይህ የድርጅቶች በጋራ መሰባሰብ በጣም የሚያበረታታና ትልቅ ድል ነዉ። እነዚህ ድርጅቶች በዉጭ አገር የሚኖረዉን ኢትዮጵያዉ ሁሉ በማስተባበር እየተመካከሩና ስራቸዉን እያቀናጁ ለአንዴን ለመጨረሻ ጊዜ ሕወሃት በዓለማቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ እዉነተኛ ገጽታዉ እንዲወጣ ማድረግ ይጠብቅባቸዋል። ሕወሃት የቆመዉ በምዕራባዉያን እርዳታ እንደመሆኑ በዉጭ አገር ያሉ ኢትዮጵያዉያን ትኩረታቸዉን ሙሉ ለሙሉ አገዛዙን ማጋለጡ ላይ ብቻ መሆን ይኖርበታል።
ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በዋሺንገትነ ዲሲ በተደረገዉ ታላቅ ሕዝባዊ ስብሰባ ንግግር ባደረጉበት ጊዜ ለዲሞክራሲ ለፍትህ ለነጻነት በሚደረገዉ ትግል እራስቸዉና ድርጅትቸዉ መከፈል ያለበትን መሥዋዕትነት ለመክፍለ እንደተዘጋጀ ተናግረዉ «እኛ ዝግጂን ነን፣ እናንተስ ተዘጋጅታቹሃል? » የሚል ጥያቄ በሺህ ለሚቆጠርዉ ተሰብሳቢዉ አቀርበዉ ነበር። ሕዝቡም መዘጋጀቱን በታላቅ ጭብጨባ መግለጹ ይታወሳል።
ወ/ት ብርቱካን ቃላቸዉን ጠብቀዉ ለሕገ ወጥ ሥራና ለአምባገነንነት ያላቸዉን እምቢተኝነት በጀግንነት አሳይተዋል። ተዳፍኖ የነበረዉን የዲሞክራሲ፣ የነጻነት የፍትህ የኢትዮጵያውነት ችቦ እንደገና ለኩሰዉታል።
እኛም ሁለት አማራጭ ነዉ ያለን። ከዚህ በፊት ከሰራናቸዉ ስህተቶች ተምረን ልዩነቶቻችን አቻችለን የገዢው ፓርቲ ካድሬዎች በኛ ላይ የሚዘረጉትን ወጥመዶች ሰባብረን፣ ይህ ችቦ የበለጠ እንዲቀጣጠል ማድረግ አንደኛዉ አምራጫችን ነዉ። ሁለተኛዉና ሌላዉ አማራጭ የሕወሃት መንግስትን እድሜ የሚያራዝም፣ የተለኮሰዉን ችቦ የሚያዳፍን፣ አገራችን ኢትዮጵያውም ከድጥ ወደ ማጡ እንድትሄድ የሚያደርግ የርስ በርስ የመከፋፈልና አብሮ ያለመሥራት አጉል ኀላ ቀር ልማዳን መቀጠል ነዉ።
ኢትዮጵያዉያን በአለም ዙሪያ በተደረጉ ሰላላምዊ ስለፎች ለማየት እንደተቻለዉ አብሮ የመሥራቱንና በጋራ የመንቀሳቀሱን አማራጭ የወሰዱ ይመስላል። ይህ መልካ ጅማሬ የበለጠ ተጠናክሮ ከገፋ ያለምንም ጥያቄ የሕወሃት ፍጻሜ እንደሚሆን መጠራጠር የለብንም። እንግዲህ ከአሁን በኋላ ወደኋላ መመልከት የለም። ወድፊት ብቻ እንጂ።

No comments:

Post a Comment