Friday, January 2, 2015

የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች እንኳን አደረሰን !

ከምንም በላይ ግን ያኔ ከመነሻው ለአገር እና ለህዝብ የሚጠቅም ፓርቲ እንመስርት ብለን፣ገንዘባችን፣ ጊዜያችን፣ እውቀታችን ሳንሰስት በመስጠት፤በወቅቱ ፓርቲ እንመስርት ማለታችን ትክክል እንደነበር የዛሬ ውጤታችን ምስክር ነው ! 
-----------------------------
ሰማያዊ ፓርቲ ከተመሰረተ አሁን ሦስተኛ ዓመቱ ነው፣የአገራችን አሉታዊ እና አዎንታዊ ፖሊቲካ ድርጊቶችና ክስተቶችን በመመርመር የመፍትሔ አካል ለመሆን በአገር ወዳድ ኢትየጵያዊያን ታህሳስ 22/2004 ዓ.ም በይፋ ተመሰረተ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በእውነት እና በእውቀት ላይ የተመሠረተ ሰላማዊ ትግል በማድረግ ፣የዜጎች የሥልጣን ባለቤትነት ለማረጋገጥ አባላቱ እና ደጋፊዎችሁ እያሣየነው ያለው ቁርጠኝነት እና ታማኝነት ለፓርቲያችን ጥንካሪ ዋንኛ መሠረት ነው፡፡ 
ሰማያዊ ፓርቲ ከምስረታው ጀምሮ ያስመዘገባቸው አኩሪ ድሎች፣ በአገራችን እየተንቀሳቀሱ ከሚገኙ ቁጥራቸው ከበዛ ፓርቲዎች ተርታ፣ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠሩ አንዱ ለመሆነ ችሎአል፡፡ፓርቲያችን ከተመሠተር እና ወደ እንቅስቃሴ ከገባ አጭር ጊዜ ቢሆነውም ፣በኢትዮጵያዊያን ካለው ተቀባይነት እና በገዥው መንግስት ላይ እያሣደረ ያለው አስጨናቂ ተፅኖ በመመልከት አንዳንድ ታዛቢዎች ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ ? በማለት ይጠይቃሉ፣ መልሱ ግን አጭር ነው፡፡

እሱም ጠንከራ ጓዳዊ ትስስር ፣ጥልቅ የሆነ የአገር ፍቅር ስሜት፣ለዓላማ መሞት፣ በእውቀት እና በእውነት ላይ የተመሰረት ሰላማዊ ትግል ተግባሪዊ ማድረግ ፣ለፓርቲያችን ውጤት የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል፡፡
ይህ ማለት ግን ፓርቲያችን ሊደርስበት ካሰበው ደረጃ እጅግ በጣም ትንሽ መሆኑ ሁላችንም የምንረዳው ሃቅ ነው፡፡ የሁላችንም የጋራ ዓላማ፣ ህዝብ የአገሩና የሥልጣን ባለቤትነቱ እንዲረጋገጥ ማድረገግ ነው ! ይህን ለማሳካት አሁን ላይ ፓርቲያችን ያስመዘገበው ድል የዋናው ትግላችን ውጤት ማሣያ መለኪያ እንጂ ፍፃሜ አይደለም፡፡ እርግጥ ነው ከትግሉ ጅምሮ አንስቶ የጠልፎ መጣል የተለመደው አዙሪት ፓለቲካ፣ ፓርቲያችን ፈተና ውስጥ የከተተው ቢሆንም በአመራሩ ጠንካራ ውሳኔ ከገጠመው ፈተና በብቃት ለመወጣት የተቻለው ሲሆን፣ወደፊትም እንዲኸ ዓይነቱ ክስተት እንዴት መወጣት እንዳለበት ት/ት ያገኘበትም መልካም አጋጣሚ ጭምር ነው፡፡ 
ፓርቲያችን ከሌሎች በአገር ውስጥ ከሚንቀሣቀሱ የዲሞክራሲ ኃይሎች ጋር በመተባበር መጪው አገር አቀፍ ምርጫ 2007፣ ፍታሓዊ እና ዲሞክራሳዊ እንዲሆን ጠንክሮ እየሰራ የሚገኝ ሲሆን፣በ2005 ዓ.ም ሊካሄድ ታስቦ የነበረ የአካባቢ ምርጫ፣ ገዥው መንግስት በቻውን ተወዳድሮ ብቻውን ያሸነፈበት የይስሙላ ምርጫ መሆኑን የ33 ፓርቲዎች ጠንካራ ትብብር ያስገኘው ውጤት ነው ! የዚህም ውጤት ባለቤት ከሆኑ ፓርቲዎች ውስጥ ሰማያዊ ከዋናዎቹ አንዱ ነው፡፡አሁንም ወደፊትም ለአገር እና ለህዝብ ጥቅም ሲባል ፓርቲያችን በጥናት ላይ የተደገፈ ከእውነተኛ የዲሞክራሲ ኃይሎች ጋር የሚያደርጋቸው ማናቸውም ዓይነት ግንኙነት በፓርቲያችን ደንብ መሠረት ገደብ የተጣለበት አይደለም፡፡
ገዥው መንግስት የፓርቲያችንን ጥንካሪ በአግባቡ በመረዳት፣በምናደርጋቸው ሰላማዊ ትግል ምክንያት በመፍጠር በተደጋጋሚ ከሚወስዳቸው የእስራት እና ደብዳባ እርምጃ ባለፈ ፓርቲያችንን ለማፍረስ በግልፅ እና በስውር እየተነቀሣቀሰ ይገኛል፡፡ከዚህም በላይ የፓርቲያችን ሰላማዊ ተጋይ አቶ የሺዋስ አሰፋ ከአ/አ፣ አቶ በፍቃዱ አበበ ከአርባምንጭ እና አቶ አግባው ሰጠኝ ከሰሜን ጎንደር በሽብርተኝነት ከሱ እያሰቃያቸው ይገኛሉ፡፡ይሁን እንጂ የጀመረነው ሰላማዊ ትግል ከዚህም በላይ ዋጋ እንደሚያስከፍል ቀድመን የተረዳነው ስለሆነ ወደፊት እንጂ ወደ-ኋላ ማለት በእኛ ዘንድ ነውር መሆኑ ጠንቅቀን እናውቃለን ! 
ፓርቲያችን ባሣለፈው ሦስት ዓመታ ውስጥ የገጠመው ውስጣዊ እና ውጫዊ ችግሮች ማንኛወም ጠንካራ ፓርቲ ሊገጥመው ከሚችለው የተለይ ነገር አይደለም ፡፡ሆኖም ግን ያጋጠሙት ችግሮች ለመፍታት የተሄደበት መንግድ ማንኛውም ፓርቲ እና የፓርቲ አባላት ከሚሄዱበት በአንፃራዊ እጅግ በጣም የተሻለ ነበር ፡፡አሁንም ወደፊትም ችግሮች መኖራቸው የማይቀር መሆኑ ታሣቢ በማድረግ፣ የፓርቲው አባል የሆን ጥልቅና ዝርዝር ውይይት በግልፅ በማካሄድ ክፍተቶቻችን እንደምንሞላ ተስፋ አድርጋለው፡፡
ከምንም በላይ ግን ያኔ ገና ከመነሻው ለአገር እና ለህዝብ የሚጠቅም ፓርቲ እንመስርት ብለን፣ገንዘባችን፣ ጊዜያችን፣ እውቀታችን ሳንሰስት በመስጠት፤በወቅቱ ፓርቲ እንመስርት ማለታችን ትክክል እንደነበር የዛሬ ውጤታችን ምስክር ነው !ለዚህም በመብቃታችን መስራች አባላት ለሆን እንኳን ደስ አለን፣አላችሁ! ለማለት እወዳለው፡፡
የጀመራችሁት አገር የማዳን ትግል የእናተ የመስራቾች ብቻ ሳይሆን የእኛም ጭምር ነው !በማለት ከፓርቲው ምስረታ ጀምሮ እስካሁን ሰማያዊን በመቀላቀል በአመራርነት እና በአባልነት በማገልገል ፣አኩሪ የትግል መሰዋትነት እየከፈላችሁ ለምትገኙ ለገዥው ለወያኔ መንግስት የእግር እሳት ለሆናችሁ የእኔ ትውልድ ጓዶች እንኳን አደረሳችሁ !
ፓርቲያችን አሁን ላይ ያለበት ደረጃ እንዲደርስ በአሳብ እና በገንዘብ እየረዳችሁ ለምትገኙ በአገር ውስጥ እና በውጪ የምትገኙ ድጋፍ ሰጪዎቻችን ፣ድካማችሁ ፍሬ እያፈረ በመሆኑ የሚሰማችሁ ደስታ ለተጫማሪ ድጋፍ እንደሚነሳሳችሁ ተስፋዬ የበዛ ነው !ከምንም በላይ ግን ሁሌም ለማይለይን የሃሳብ እና የገንዘብ ድጋፋችሁ አገራዊ ግዴታችሁ ቢሆንም፣ በቀናነት እና በአገር ወዳድነት ለምታደርጉት ድጋፍ ምስጋና ተገቢ ነው፡፡ምስጋናውን ከአክብሮት ጋር እንድትቀበሉ በመጠየቅ ፣ለዚህ በመብቃታችን እንኳን አደረስን በማላት የ3ኛ ዓመት የእንኳን አደረስን የግል መልእክቴን በዚህ አጠቃልላለው፡፡
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !

No comments:

Post a Comment