Thursday, May 28, 2015

አሜሪካ ውስጥ ርካሽ እና ውድ የቤት ኪራይ ያለባቸው ከተሞች ተለይተው ታወቁ

(Admas Radio)
ካሊፎርኒያ፣ ዋሽንግተን ዲሲ፣ ሃዋይ፣ ኒውዮርክ እና ኒውጀርሲ ውድ ቤት ኪራይ ያለባቸው ከተሞች መሆናቸውን ሰሞኑን የወጣ ሪፖርት አሳይቷል።
new-york-city
አንድ በኒውጀርሲ ከተማ ለመኖር የፈለገ ተከራይ ባለሁለት መኝታ ቤት ተከራይቶ ለመኖር አንድ በሰዓት 25 ዶላር የሚከፈልበት የሙሉ ሰአት ሥራ መስራት ይኖርበታል። በኒውጀርሲ በአማካይ የሁለት መኝታ ቤት ዋጋ 1300 ዶላር በወር ነው። አንድ ሰው የቤት ክፍያው ከደሞዙ ከ 30 በመቶ መብለጥ አይኖርበትም – አቅም አለው ለመባል። በዚህ መሰረት 1300 በወር ከፍሎ ለመኖር ቢያንስ በወር አንድ ሰው 4ሺ 500 ዶላር ገቢ ሊኖረው ይገባል።

በኒውጀርሲ የቤቶችና ማህበረሰብ እድገት አጥኚ የሆኑት አርኖልድ ኮህን በርካታ የአሜሪካ ግዛቶች ነዋሪዎቻቸው ሁለት መኝታ ቤት አፓርትመንት የመከራየት አቅም እንዲኖራቸው የሚያስችል ክፍያ የላቸውም ይላሉ። በተለይ የኒውጀርሲን ሲያስረዱ “ልጆቻችንን የሚጠብቁልን፣ አዛውንቶቻችንን የሚንከባከቡልን፣ ግሮሰሪና ሌላም ቦታ የሚያስተናግዱን፣ ለየለት ለት ጉዳዮቻችን ተስፋ የምንጥልባቸው ሁሉ ፣ ለራሳቸው መኖሪያ ለመክፈል ግን አይችሉም” ሲሉ ይናገራሉ።
በኒውጀርሲ ግዛት መካከለኛ የሰአት ክፍያ 17 ዶላር ሲሆን፣ በሰአት 17 ዶላር የሚከፈለው ሰው ፣ ሁለት መኝታ ቤት አፓርትመንት መከራየት እንዲችል በሳምንት ቢያንስ 59 ሰአት መስራት ይኖርበታል። የግዛቱን ዝቅተኛ የሰአት ክፍያ ማለትም 8.38 ዶላር በሰ አት የሚከፈለው ሰው ሁለት መኝታ ቤት ካማረው ሶስት የሙሉ ሰአት ሥራ ያስፈልገዋል። ያ ማለት ደግሞ 24 ሰአት በቀን መስራት አለበት ማለት ነው።
በአንዳንድ የኒውጀርሲ አካባቢዎች ፣ ለምሳሌ በሃንተርደን፣ ሚድልሴክስ እና ሶመርሴት አካባቢዎች ሁለት መኝታ ቤት እስከ 1500 ዶላር ይደርሳል። በአንጻሩ በሱሴክስ፣ ኬፕ ሜይ እና ግላክስተር የሚባሉ ካውንቲዎች ኪራዩ የሚቀንስ ቢሆንም፣ በዚያ አካባቢ የሚኖሩ ደግሞ በአብዛኛው በሰአት 10 ዶላር አካባቢ የሚከፈላቸው ናቸው።
ለዚህም ነው ባሳለፍነው ሳምንት በኒውጀርሲ የሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ፣ እንደ ሰዉ አቅም የሚሆኑ ቤቶች እንዲሰሩ ግፊት የሚያደርግ ስብሰባ ያካሄዱት: በዚህ ስብሰባ የኒውጀርሲ ባለሥልጣናት ሁሉም እንዳቅሙ የሚኖርባቸው ቤቶች እንዲሰሩ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።
በኒው በርንስዊክ ከተማ ነዋሪ የሆነው ፖል ሜየርስ በወር 1500 ዶላር እየከፈለ በተከራየው ሁለት መኝታ ቤት አፓርታማ ከቤተሰቦቹ ጋር ይኖር ነበር። በመካከል ይስራ የነበረው የሽያጭ ሥራ ተቋረጠ። ለቤት ኪራይ የሚከፍለውም አጣ። በዚህ ጊዜ የቤት ዕቃዎቹን እያወጣ መሸጥ ነበረበት። “እንደዚያም ሆኖ መኖር አልቻልኩም፣ የምሸጠው አለቀ፣ የቤት ኪራይ ግን እየጠበቀኝ ነበር” ነው ያለው።
ከዚያ በኋላ ምርጫ አልነበረውም ከነቤተሰቡ ወጥቶ በመቆያ ጣቢያ (ሼልተር) መኖር ጀመረ። ስምንት ወር እዚያ ከቆየ በኋላ እሱ ሚስቱና አንድ ልጁ ከዚያ ወጥተው ኪልመር ሆምስ የተባለው ድርጅት በመንግስት ድጋፍ በሚገነባቸው አፓርታማዎች መኖር ጀመረዋል። እነዚህ አፓርታማዎች ሰዎች እንደገቢያቸው ልክ የሚከፍሉባቸው ናቸው። ሆነም ቀረ፣ ያቺንም ቢሆንም ለመክፈል ፖል ቀን ከሌሊት መስራት ነበረበት።
በሰሞኑ ጥናት መሰረት ውድ የአፓርታማ ኪራይ የተመዘገበባቸው ከተሞች መካከል ሃዋይ በቀዳሚነት ይጠቀሳል። በሃዋይ ሁለት መኝታ ቤት አፓርታማ 1700 ዶላር ሲደርስ፣ በዲሲ 1500 ዶላር አካባቢ፣ በካሊፎርኒያ 1389 ፣ በኒውርዮክ 1335፣ እንዲሁም ኒውጀርሲ 1309 ዶላር በአማካይ ናቸው።
በሌላ በኩል ርካሽ የሚባል ባለሁለት መኝታ ቤት አፓርታማ ከሚገኝባቸው ከተሞች መካከል ፖርቶሪኮ 547 ዶላር ፣ አርካንሳ 673 ዶላር ፣ ኬንታኪ 683 ዶላር፣ ዌስት ቨርጂኒያ 687 ዶላር እንዲሁም ሳውዝ ዳኮታ 698 ዶላር ይጠቀሳሉ።
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/41772#sthash.8gpRDeQb.dpuf

No comments:

Post a Comment