Wednesday, May 13, 2015

ደርግን ያስናፈቀ አገዛዝ! – ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

እኔ ለደርግ ሥርዓት ጥሩ ስሜት የለኝም፡፡ በእርግጥ ደርግ ያደረገውን የቀይ ሽብር ፍጅት በወቅቱ ገና መወለዴ ስለነበር በዐይኔ ዐላየሁም፡፡ ይሁንና የሆነውን ሁሉ ግን አባቴም በኢሕአፓነቱ የደርግ ጥቃት ሰለባ ስለነበር እሱ ከነገረኝም ሆነ እኛ ዜጎች የደርግንም ሆነ የሌላውን ማንነት ከመረዳት አንጻር ከታሪክ ብዙ የምንረዳው ነገር አለና ለደርግ ጥሩ ስሜት የለኝም፡፡ ከፈጸማቸው የግድያ እርምጃዎች ጋር በተያያዘ አሁን ሀገራችን ላለችበት ዘንቀ ብዙ ችግሮች ተጠያቂ እንደሆነም አስባለሁ፡፡ በተለይም እነዚያ ብዙ የተማሩ ብዙ የሚያውቁ ብዙ የውጪ ግንኙነት ልምድ የነበራቸው የ62ቱ የቀዳማዊ ዐፄ ኃይሌ ሥላሴ መንግሥት ሚንስትሮችን ጉዳይ ሳስብ ዘወትር ይከነክነኛል፡፡ ኢትዮጵያ ከስር የተነቀለችው ዐይኖቿ የጠፋው ያኔ ነው፡፡
እነ ጠቅላይ ሚንስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድን የሚያህል እጅግ አስተዋይ፣ አርቆ አሳቢ፣ ደከመኝ ሰለቸኝን የማያውቅ ትጉ፣ ተናግሮ ሊያሳምነው የማይችለው ሰው የሌለው ብልህ፤ በእነዚህ ብቃቱም በመንግሥታቱ ድርጅት ታሪክ ኮከብና አንጸባራቂ ዲፕሎማት (አቅናኤ ግንኙነት) የነበረን ታላቅ ሰው የመሳሰሉ ብርቅየ የሀገራችን ፖለቲካ (እምነተ አሥተዳደር) ቁልፍና መዝገቦች ያለ አግባብነት ያለው ፍርድ በግፍ መግደሉ ነው ሀገሪቱ መስመር ስታ ወዳልሆነ አቅጣጫ መንጎድ የጀመረችው፡፡ ሰሞኑን የፕሬስ (የጥፈት) ነጻነት ቀን ሚያዚያ 25 (May 3) በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ታስቦ ነበር:: ታዲያላቹህ በሀገራችንም ይሄንን የጥፈት ነጻነትን ቀን በዓል ለማክበር ለማሰብ እነማን ተሰባሰቡላቹህ መሰላቹህ? ጥፈትን (ፕሬስን) የገባችበት እየገቡ የሚያሳድዷት ጭፍሮች ተሰባስበው ታደሙና “ይሄው በዓልሽን እያከበርንልሽ ነው” ብለው ጥፈትን (ፕሬስን) ሲያፌዙባት ሲቀልዱባት ሲሳለቁባት ሲያበግኗት ዋሉ፡፡ ጥፈት (ፕሬስ) በጣም አሳዘነችኝ እንደምን ታር! እንዴት ትበግን! እንዴት ትደብን! ብየም አሰብኩላት፡፡ ጨጓራዋ ተልጦ ቆሽቷ ደብኖ እየጨሰች ታየችኝ፡፡ መድረኩ ላይ ተሠይመው እየተንጎባለሉ በመደስኮር ሲያቃጥሏት ከነበሩት የጥፈት ጠላት የወያኔ ጭፍሮች አንዱና በሀገሪቱ የጥፈት (የፕሬስ) ነጻነት እንዳለ ተደርጎ እንዲታሰብ ብቻ ተቋቁመው ከሚሠሩ የኅትመት የብዙኃን መገናኛዎች ባለቤቶች አንዱ የሆነው ሰው ምን አለ መሰላቹህ? እኔ ማንን ለማለት እንደፈለገ ቢገባኝም እንዴት ሆኖ እንደሆነ ግን ሊገባኝ አልቻለም፡፡ እንዲህ ነበር ያለው “አትመጣም ወይ መንጌ አትመጣም ወይ? እያለ የደርግን መልሶ መምጣት በመናፈቅ የሚጨፍር የፖለቲካ ፓርቲ ስለ ፕሬስ ነጻነት ተሟጋች እንዴት ሊሆን ይችላል?” ነበር ያለው፡፡ ሌላኛው ደግሞ አሁን በዚህ ወቅት “ነጻ ጥፈት (ፕሬስ) አለ በሚገባም እየሠራ ነው…..” በማለት ሌሎችን አለመኖሩን በማስረጃ አስደግፈው የሚሟገቱትን እንደ ሲ.ፒ.ጀ. ያሉ የዓለም አቀፍ ድርጅቶችን አቋምና ክስ ለማጣጣል ጥረት አደረገ፡፡ የሚገርማቹህ ይህ ሰው አንድ ወቅት ላይ የዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅት ተሸላሚ የነበር ሰው ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ቀድሞውንም ቢሆን ሥውር ተልእኮ ስለነበራቸው በነጻው ጥፈት ተሰማሩ እንጅ አንጻራዊ በሆነ መልኩ ነጻው ጥፈት የተሻለ ይሠራ በነበረበት ወቅት አገዛዙ በነጻው ጥፈት (ፕሬስ) ላይ ያለውን አያያዝና አቋም ቀንደኛ ተችና ተቃዋሚ ሆነው ኖረው አሁን ላይ ጭራሽ አገዛዙ ነጻውን ጥፈት (ፕሬስ) ደብዛውን ባጠፋበትና የለየለት አንባገነን በሆነበት ወቅት ከወትሮው ይበልጥ መቃወምና መታገል ሲኖርባቸው ሲጠበቅባቸው እነኝህ የነጻው ጥፈት ውጤት ጋዜጣ ባለቤት ነኝ ባይና ነጻ ጋዜጠኛ ነኝ ባይ ግለሰቦች የአገዛዙ ደጋፊ ሆነው ከአገዛዙ ጋር ሊሠሩ ሊሰለፉ የሚችሉበት አንዳችም ምክንያት የለም፡፡ የስለላ ተልእኮ ነበራቸው ለመመሳሰል ተቃዋሚ ሆነው በሚገባ ተወኑ አንደኛው እንዲያውም እስከመሸለም ድረስ ደረሰ ወዲያው ግን ተነቃባቸው ስለተነቃባቸውና ስለተገለሉም “ከተነቃ አይገደድም” ብለው ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡ ያለው ነገር ይሄ ነው ሌላ ምንም ምሥጢር የለውም፡፡ አገዛዙ የፈጸመውን ግፍና ወንጀል ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዐይን ለመሠወር ሲል የውጭ ዜጎች ድርሽ እንዳይሉ ወደ ተከለከሉበት አገዛዙ መጠነ ሰፊ የሰብአዊ መብት ረገጣና የዘር ማጥፋት ወንጀሎችን በፈጸመባቸው የሀገራችን አካባቢዎች የተፈጸሙትን ኢሰብአዊ ድርጊቶቹን ለማጣራትና መረጃ ለመሰብሰብ ባለመቻላቸው ምክንያት የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ሠራተኞች በተለያየ ዘዴና መንገድ መረጃ ለመሰብሰብ መሞከራቸውን ይሄ ጋዜጠኛ ነኝ ባዩ ወያኔ በዚህ በዓል ዝግጅት ላይ ሲናገር እንደሰማቹህት ነጻ ጋዜጠኛ መስሎ ይሰልል በነበረበት ወቅት ካየውና ካጋጠመው ተነሥቶ በመኮነንና እንደ ወንጀል በመቁጠር በወቅቱ ሲሠራው ከነበረው የስለላ ሥራው እየጠቀሰ ይናገር ነበር፡፡ ይሄ ሰው ከመሰሎቹ ጋር ሆኖ ባለፈው የሕወሀት 40ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል በሚከበርበት ወቅት ወደ ስፍራው ተጉዘው ጉብኝት ካደረጉት ጋዜጠኞችና ከያኔያን ነን ባዮች ጋር በመሆን በጉብኝታቸው መጨረሻ ላይ ባለ 6 ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት በማንኛውም እረገድ ከሕወሀት ጎን እንደሚሰለፉ ለሕዝብ በብዙኃን መገናኛ ካረጋገጡ ምንደኞች አድርባዮች ባንዶች አንዱ ሆኖ እያለ ነው እንግዲህ ዛሬም ሳያፍር አጻ ጋዜጠኛ ነኝ ሊለን የሚሞክረው፡፡ እንደምታስታውሱት ሚያዝያ 14,2007ዓ.ም. ቀን ሊቢያ ውስጥ በአረማዊያን ለተሠው ወገኖቻችን የተሰማንን ሐዘን ለመግለጽና ለአረመኔው አይ.ኤስ ቡድን ደግሞ ያለንን ተቃዉሞ ለማሰማት በወጣንበት ቀን በብልሹ አሥተዳደሩና በግፍ አገዛዙ ወገኖቻችንን ለስደት እየዳረገ ለእርድ፣ ለስጥመተ ባሕርና ተቆጥሮ ለማያልቅ መከራ ያበቃቸው ይህ የአገዛዝ ሥርዓት እንደመሆኑ መጠን ምክንያቱም አገዛዙ ዜጎች በዜግነታቸው የዜግነት ኃላፊነታቸውን ግዴታቸውንና መብታቸውን ለመወጣት ጥረት በሚያደርጉበት ወቅት ለሱ ስላለተመቸው በኃይል ይዞ አልለቅም ላለው ሥልጣኑ ሥጋት ስለሆኑ “እኔ የምላቹህን ብቻ ተቀብላቹህ ሳትወዱ በግድ እየተገዛቹህ መኖር አንችልም ካላቹህ ተሰደዱ” ብሎ ዜጎችን ከገዛ ሀገራቸው እንዲሰደዱ መሰደድን ብቸኛ አማራጭ አድርጎ የሰጠ ካልሆነ ግን አስራለሁ እገላለሁ ብሎ በብዙኃን መገናኛ አስፈራርቶ የሚያውጅ አገዛዝ (በምርጫ 97ዓ.ም. ወቅት አቶ መለስ ለቅንጅት አመራሮችና ተከታዮቻቸው የተናገሩትን ያስታውሷል)፣ ተቃዋሚ እንዲሰደድ እንጅ በሀገር እንዳይኖርና ሚናውን እንዲጫወት ባለመፍቀድ አቋም የያዘና አሳዳጅ አገዛዝ እንደመሆኑ ለዜጎች ስደት በቀጥታ ተጠያቂ ነውና በዚህ ምክንያት በሰልፉ ላይ ሕዝቡ በተለያየ መንገድ ለዚህ የአገዛዝ ሥርዓት ያለውን ተቃዉሞ ያሳይ ይገልጽ ነበር፡፡ ከእነኝህ የሕዝቡ ተቃዉሞ መገለጫዎች ከነበሩት ነገሮች አንዱ የነበረው ከላይ የነጻ ጋዜጣ ባለቤት ነኝ ባዩ ሰው የጠቀሰው “አትመጣም ወይ መንጌ አትመጣም ወይ?” የምትለዋ ዜማ ነበረች፡፡ አገዛዙ በዕለቱ ለተነሡት ተቃዉሞዎች ሁሉ ተጠያቂ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲን ነው፡፡ እናም እነዚህ የውሸት የጥፈት (የፕሬስ) ሰዎች ነን ባዮች የወያኔ ጭፍሮች ታዲያ እንደ ወያኔነታቸው ይሄንን የወያኔን ሐሰተኛ ክስ ትክክለኛ እንደሆነ አድርገው በማውራት ለማሳመንም በማሰብ በዚህ የጥፈት ነጻነትን በዓል ቀን ለማክበር በተሰበሰቡበትም ቀን ጉዳዩን በማንሣት የወያኔነት ሥራቸውን ለመከወን ሙከራ አደረጉና ከላይ የጠቀስኩትን ንግግራቸውን ተናገሩ፡፡ እኔ ወያኔዎች ከሚገርሙኝ ነገራቸው አንዱ ምናልባትም ዋነኛው እራሳቸውን ከደርግ የተሻሉ እንደሆኑ አድርገው በማሰብ ደርግን እያነሡ “የጥፈት (የፕሬስ) ነጻነት ያልነበረበት፣ ወጣቱን ትውልድ እየረሸነ የፈጀ እንዲህ ዓይነት አረመኔ መንግሥት እኮ ነበር የነበረው!” በማለት ሕዝቡ እነሱን የተሸሉ እንደሆኑ አስቦ አሜን ብሎ እንዲቀበላቸው የሚያደርጉት ጥረት ነው፡፡ አንባቢያን እስኪ አንድ ጥያቄ ልጠይቃቹህ? የጥፈት ነጻነት አለ ሰጥቻለሁ በሕገ መንግሥት አረጋግጫለሁ ብሎ ሲያበቃ ሰው ሲናገር ሲጽፍ የሚናገሩትን የሚጽፉትን እየለቀመ በማፈን ከሚያጠፋው ከሚያስረው ከሚገለው እና ስለማጠፋህ አትናገር አትጻፍ ብሎ አስቀድሞ አስጠንቅቆ መጻፍ መናገርን ከከለከለው ማንኛው ይሻላል? እኩይነት መርዘኛነት ሸረኝነት አጥፊነትስ የትኛው ላይ ነው ያለው? እንዲያው ነገሩን አልኩ እንጅ ወያኔስ ቢሆን ለማስመሰል ምዕራባዊያኑን ለመደለል ወረቀት ላይ አሠፈረው እንጅ የትኛው የሰጠው ያረጋገጠው ያሰፈነው ነጻ ፕሬስ (ጥፈት) ነው አደረኩ ብሎ ሊያወራው የሚችለው? ለማስመሰልም ቢሆን በትንሽ በትንሹ እንዲጻፍ ማድረጉ እኮ ያለፈ ድሮ የቀረ ታሪክ ሆነ፡፡ አሁንማ እኮ ጋዜጠኝነት በአሸባሪነት የሚያስከስስና የሚያስቀጣ ሞያ እኮ ሆነ፡፡ አሁንማ እኮ ነጻ ጥፈት (ፕሬስ) ሕገ መንግሥታቸውን በቀጥታ በሚጻረሩ በሚሽሩ እንደ ፀረ ሽብርተኝነት በመሳሰሉ ፀረ ሕገ መንግሥት ፀረ ሰብአዊ መብት ሕግጋት እግር ከወርች ታስሮ እንዳይሠራ እንዳይንቀሳቀስ ከተደረገ ቆየ አይደል እንዴ? ቅድመ ምርመራው (ሴንሰር ሽፑ) ተመልሶ መጥቶ ጋዜጠኖችንና ጸሐፍትን ውስብስብ ችግርና ሥጋት ውስጥ በመክተት በራሳቸው ላይ ግለ ቅድመ ምርመራ (self censor) እያደረጉ እንዲጽፉ በማስገደድ ከዚህ ያለፈውን ደግሞ ማተሚያ ቤቶቹ አገዛዙን የሚተቹ ጽሑፎች ሲኖሩ እንዲህ ዓይነት ጽሑፍ አናትምም እያሉ ኅትመቶች እንዳይታተሙ መደረግ ከተጀመረ ዓመታት ተቆጠሩ አይደለም አይደል እንዴ? ሌላው ቀርቶ ወያኔ አሁን ደግሞ የማኅበራዊ የብዙኃን መገናኛውን (social media) ማለትም እንደ ፌስ ቡክ (መጽሐፈ ግጽ) ያሉትን የብዙኃን መገናኛ መንገዶችን ሊዘጋብን ሊያግድብን ወስኖ ቁልፍ መጫን ብቻ እንደቀረው ሰማን አይደለም አይደል እንዴ? እንግዲህ የወያኔ የአንባገነንነትና የፀረ ነጻ ፕሬስ (ጥፈት) ማንነት አፋኝነት እዚህ ድረስ ነው፡፡ ይሄ ማንነቱም ከአሜሪካ መንግሥት እስከ የመብት ተሟጋች ድርጅቶች ድረስ በሚገባ ታውቆ ቀንደኛ ፀረ ነጻ ጥፈትነቱና አፋኝነቱ ካሰራቸው ካሳደዳቸው ከሶ ከሚያንገላታቸው ጋዜጠኞች ቁጥር ጋር እየተጠቀሰ በየጊዜው እየተመሰከረበት ይገኛል፡፡ አሁን በዚህ ወቅት ወያኔ በዓለማችን ውስጥ ካሉ 10 አፋኝና ፀረ ነጻ ጥፈት አገዛዞች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት አንዱ ነው፡፡ ታዲያ ወያኔና ደጋፊዎቹ አሰፈንን ብለው የሚያወሩት የትኛውን ነጻ ፕሬስ (ጥፈት) መብት ነው? ሀቁ ይሄ ከሆነስ ከደርግ እንሻላለን የሚሉት እኮ እንዴት ሆኖ ነው? ቀይ ሽብር ቀይ ሽብር የሚሉትስ ወያኔስ ቢሆን የገደለበትን ዘመቻ ስም አውጥቶ አይንገረን እንጅ አደባባይ ላይ ብዙዎችን አልገደለም አልረሸነም ወይ? የደርግና የወያኔ የገዳይነት ተግባር በአንድ ቀን በተፈጁት ዜጎች ቁጥር የግድ ተሰልቶ መነጻጸር አለበት ወይ? ዋናው ጉዳይ ዜጎች ተቃወሙ መብታቸውን ጠየቁ ተብሎ ለጥያቄያቸው ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት ባለመፍቀድ ባለመፈለግ ከአንባገነናዊ ባሕርይ የተነሣ መሣሪያ አንሥቶ ለመግደል ፈልጎና አስቦ ሰላማዊ ዜጎችን ግንባር ግንባራቸውንና ደረት ደረታቸውን እያሉ ለመግደል ታስቦ መፈጸሙ ነው እንጅ ብዛቱ ነው ወይ መታየት መነጻጸር ያለበት? በብዛቱስ ቢሆን በምርጫ 97ዓ.ም. የተነጠቀውን ድምፁን ለማስመለስ ለማስከበር በተቃዉሞ የወጣው ወጣት የወያኔን ጭካኔ ዐይቶ መለስ ባይልና እንደ ደርግ ዘመን ወጣት የጨከነ የቆረጠ የማይመለስ ቢሆን ኖሮ ወያኔስ ቢሆን ወጣቱን በሙሉ ጨፍጭፎ በመጨረስ ጎዳናውን ሁሉ የደም ጎርፍ ሳያጎርፍበት ይመለስ ነበር ወይ? እንኳንና ወጣቱ ሁሉ ተነሥቶ ያችን ታክል ለተወጣው እንኳ የታዘዙት የአየር ኃይል አባላት “በሰላማዊ ወገናችን ላይ አንተኩስም” በማለት አብራሪዎቹ ከድተው ወደ ጅቡቲ ሸሹ እንጅ ወያኔማ ሰላማዊ ሕዝብ እንዲጨፈጨፍ ሄሊኮፕተር ያዘዘ አረመኔ አገዛዝ አይደለም ወይ? ጉዳዩ በተጠያቂነት መንፈስ ሕዝብ የጠየቀውን መብቱን የማክበርና ያለማክበር ጉዳይ ነበረ እንጅ አላግባብ የተቃጣን ሕዝባዊ ጥቃትን ወይም ዐመፅን የመከላከል ጉዳይ ነበረ ወይ? ጉዳዩ ይሄ ባልሆነበት ሁኔታ ያ የተፈጸመ ግድያ ሕጋዊ ወይም አግባብነት ያለው የሚሆነው እንዴት ሆኖ ነው? ይህ እውነታ እንዳለ ሆኖ “ራሴን የመከላከል ሕጋዊ እርምጃና ሰላምና መረጋጋትን ማስፈን ስላለብኝ ይሄንን ማድረግም መብትና ግዴታየ ስለሆነ ነው” ከተባለም ደርግስ ቢሆን ታዲያ “ነጭ ሽብር” ተብሎ ለተሰነዘረበት ጥቃት እራስን ለመከላከል ብሎ “ቀይ ሽብርን” ከመፈጸም የተለየ ሌላ ምን ምክንያት ነበረው? ወያኔ ሲገድል ሲያፍንና ሲያጠፋ እንደ ደርግ በብዙኃን መገናኛ እነከሌን እነከሌን ገድያለሁ ብሎ አለመናገሩ ነው እንጅ በደርግ ጊዜ ከተፈጁት ዜጎቻችን ይልቅ በወያኔ ዘመን የተፈጁት የታፈኑት ዜጎቻችን ብዙ ጊዜ እጥፍ አይበልጡም ወይ? ደርግ ሰዎችን ሲገድል የፖለቲካ (የእምነተ-አሥተዳደሩ) ተቃዋሚዎች ከሚለው በስተቀር ሌላ ምክንያት ነበረው ወይ? ወያኔ ግን ከዚህ በተጨማሪ ሌላ የመግደያ የማጥፊያ የማፈኛ ምክንያት ጨምሮ በመምጣት “ጠላቴና መጥፋት ያለበት ዘር” ብሎ በሀገራችን ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ደረጃ ዘርን ከመገደያ ምክንያቶች አንዱ አድርጎ አማራን በግልጽም በሥውርም ጎጆ ዘግቶ በላያቸው ላይ ከማቃጠል ጀምሮ እስከ በጥይት መደብደብ ድረስ፤ በራሱ ሕገ መንግሥት “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል መዘዋወር መኖር ንብረት ማፍራት ይችላል” የሚል መብት ታዉጆ እያለ መብታቸውን በመንፈግ ከኖሩበት ተወልደው ካደጉበት ንብረት ካፈሩበት ሀገራቸው እያፈናቀለ እያሳደደ ግፍ እየፈጸመና መኖሪያ እያሳጣ ያለው ማን ነው? ደርግ በየትኛው ብሔረሰብ ላይ እንዲህ ዓይነት ሰይጣናዊ ሴራ አሲሮ ብሔረሰብን ለይቶ በጠላትነት ፈርጆም እንዲህ ዓይነቱን የዘር ማጥፋት ወንጀል በየትኛው ብሔረሰብ ላይ ፈጸመ? ጭራሽ እንዲያውም ያባበለ መስሎት በሁሉም እረገድ የኤርትራና የትግራይ ተወላጅ የሆኑትን ልዩ ተጠቃሚ አድርጎ አስተናገደ እንጅ በትግራይ ተወላጆች ላይ ትግሬ ስለሆኑ ብቻ መቸና የት ወያኔ እየፈጸመ ያለውን ዓይነት ግፍ ፈጸመ? ወያኔ እየደጋገመ የሚያነሣው የሀውዜኑ የጦር አውሮፕላን ጥቃትም እኮ ወያኔ ሆን ብሎ ደርግን በዓለማቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ለማስጠቆር በውጤቱም ርካሽና ግፈኛ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ያስፈጸመው እንደሆነ በራሱ በወያኔ አመራሮች የተረጋገጠ እውነት ከሆነ ሰነበተ፡፡ ስለሆነም ይህች የምትጠቀስ የጦርነት አደጋ ደርግን ሳይሆን ወያኔን የሚያስኮንን አስገራሚና አሳዛኝ ድርጊት ከሆነ ቆይቷልና ይሄም የናንተ ሥራ ነው፡፡ እንደ ወያኔ ሁሉ ደርግ ዘሬ ብሔረሰቤ ነው ብሎ ከኢትዮጵያ ሕዝብ አንድን ብሔረሰብ ነጥሎ ተጠቃሚ ለማድረግ በማሰብ ሁሉንም ነገር በቅድሚያና በተለየ ሁሌታ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማን ወይም ለየትኛው ብሔረሰብ ታጥቆ ሠራ? “ኢትዮጵያ ትቅደም” የሚል መሪ ቃል በመያዝ በነገሮች ሁሉ የኢትዮጵያን ጥቅሞች በማስቀደም ለመሥራት ከመሞከር ውጪ እንደ ወያኔ ሁሉ መቸና የትስ የሀገርን ብሔራዊና ሉዓላዊ ጥቅም ከራሱ ከግል ጥቅሙ በማሳነስ ለራሱ ጥቅም የሀገርንና የሕዝብን ጥቅም አሳልፎ በመስጠት የሀገር ክህደት መቸና የትስ ፈጸመ? ደርግ መቸ ነው እናንተ ወያኔ ካልሆናቹህ በስተቀር እያላቹህ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርትን አንዳንዴም የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርትን መማር አትችሉም እያላቹህ እንደምትከለክሉት ከትምህርት ገበታ እንደምታባርሩት ደርግ የዜጎችን መሠረታዊ የዜግነት መብት የከለከለው መቸ ነው? እንደናንተ ሁሉ ደርግ መቸ ነው “የፖለቲካ ፓርቲ የንግድ ድርጅትና የብዙኃን መገናኛንም ማቋቋም አይችልም” የሚል ሕግ ካወጣ በኋላ የንግድ ድርጅቶችን አቋቁሞ ኢፍትሐዊና ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ በመነገድ ሀገርንና ሕዝብን የበዘበዘው የመዘበረው የዘረፈው መቸ ነው? የፓርቲ የብዙኃን መገናኛዎችን አቋቁሞ ከሀገር ጥቅም በተጻራሪ የቡድን ጥቅሙን ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ ያጧጧፈው መቸ ነው? የእናንተ ጉድ ተዘርዝሮ አያልቅምና ወዘተረፈ ብየ ልዝጋው፡፡ ወያኔዎች ሆይ! እራሳቹህን ከደርግ ጋር ስታነጻጽሩ ስታወዳድሩ ስታፎካክሩ ትንሽም እንኳን አታፍሩም? መቸ ነው እንደሚያስብ እንደሚያገናዝብ ሰው ልካቹህን አቅማቹህን ማንነታቹህን አውቃቹህ አፋቹህን ይዛቹህ ቁጭ የምትሉት? ሐፍረት የሚሰማቹህ መቸ ነው? ጤነኞች አይደላቹህምና መቸም ታደርጉታላቹህ ብየ አልጠብቅም፡፡ እኔ ይሄንን ይሄንን የማነሣው አፍቃሬ ደርግ ሆኘ ወይም ለደርግ ጥብቅና ለመቆም ሳይሆን ይህ አገዛዝ እሻላለሁ ብሎ ከሚያስበው እጅግ የባሰና ከምኑን የማይደርስ እንደሆነ ለማሳየት ነው እንጅ ደርግንስ አልወድም እጠላዋለሁ፡፡ ደርግን ከጠላሁ ደግሞ ወያኔን ምን ያህል ልጠላ እንደምችል አስቡት? ከላይ እንዳየነው የባሰ እንደመሆኑ መጠን እጅግ እግጅ እጠላዋለሁ፡፡ እናም እነ አቶ ማንትስየም ሆናቹህ የወያኔ ባለሥልጣናት ይሄንን ያህል ናቹህና ኅሊና ካላቹህ ማሰብ ማገናዘብ የምትችሉ ጤነኞች ከሆናቹህ ደርግን እያነሣቹህ “ቢያንስ ከደርግ እንሻላለን” በማለት ማስተዛዘኛ እንዲታሰብላቹህ መሞከራቹህን ብታቆሙ መልካም ነው፡፡ እንዲህም መሆናቹህን ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ስለሚረዳ ልካቹህ ይሄ ስለሆነም ነው ሕዝቡ ደርግን እንኳ ለመናፈቅ የበቃው፡፡ አይገባቹህም እንጅ “ደርግ ከእናንተ ተሻለ እናንተ ደግሞ ከደርግ እጅግ ባሳቹህብን” ሲል ነው “አትመጣም ወይ መንጌ አትመጣም ወይ?” እያለ ያዜመው እሽ?፡፡ እንዴ! ሰው እንዴት አስቦና አቅዶ አውቆ ጥፋት እየሠራ የሚሠራው ጥፋት እንዴት አይታወቀውም? እንዴት ይጠፋዋል? እንዴት ያጣዋል ጃል? ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!! ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/41297#sthash.uFAdi7Bw.dpuf

No comments:

Post a Comment