Wednesday, May 13, 2015

የሀገር ሀብት ዘረፋ፤ስደት፤እሥራትና ግድያው እንዲቆም ህወሃትን ከሥልጣኑ አውርደን መጣል ግዴታችን ነው።

ገብርየ በለው።  
ካልገደሉ አያቆሙንም ነው ያለው ሐብታሙ አያሌው?( ወጣቱ የፖለቲካ መሪ)ሟች ማን ገዳይ ማን?ታጋይ ይሞታል እንጅ ትግል አይሞትም።
    EPRDFፋሽስቱና አረመኔው የህወሃት ቡድን ፀረ-ሕዝብነቱን ፀረ-ኢትዮጵያዊነቱን አጠናክሮ ለ24 ዓመታት ያህል ሲዘልቅ ከባድና ከፍተኛ የሆኑ ጠባሳ የታሪክ አሸራዎችን እያስመዘገበ ማለፉ በግልጽ የሚታወቅ የሚጨበጥና የሚዳሰስ ታሪካዊ ክህደት ነው።በተለይ ከ1997 ምርጫ በኋላ በቀቢጠ ተስፋ የሚሠራውን አሳጥቶት ይገኛል ከ2007 ምርጫ በፊት በምርጫ መስናዶ ያሳያቸው የአውሬነት ባህርያትም በውል ሊስተዋሉ የሚገባቸው ናቸው።
     በአንፃሩ ደግሞ ይህን የህወሃት ታሪካዊ ክህደትና የቅጥረኝነት አስነዋሪ ተግባር ለመመከት በኢትዮጵያዊነታችን የምናምን ዜጎች የሄድንበት ርቀት ወንዝ የሚያሻግር ሆኖ አላገኘሁትም። ጉዳዩ ህወሃት የሰጠን የቤት ሥራ ብቻውን አቅም እንድናጣ አድርጎናል ብየም አልገምትም። የራሳችን ችግርም አስተዋፅኦ አድርጓል።
እንደኔ አመለካከት ቁልፉ ጉዳይ እዚህ ላይ ነው ያለው ብየ አምናለሁ። ለምን ቢባል ሕዝቡ ለአመጽ ዝግጁ አይደለም ብለው ምክንያት ሲፈጥሩ የነበሩ የተቃዋሚ ድርጅቶች ሕዝቡ ጥሏቸው ሄዶ እነሱን ጭራ አድርጓቸው ይገኛል። የተቃዋሚ ኃይሎች በራሳቸው መካከል ያለውን ግንኙነት ስንመለከት ተስፋ ሰጭ አይደለም።
     የተቃዋሚ ኃይሎች መጀመርያ ራሳቸውን ሊፈትሹ ይገባል በተለመደው ስሌት እንደ ከዚህ ቀደሙ ሕዝብ ያገኘውን ድል ለመንጠቅና ሥልጣን ላይ ቁጢጥ ለማለት ከሆነ አድፍጣችሁ ያላችሁት የናንተ መደራጀት ገደል ይግባ እንድንል ይገፋናል።ምክንያቱም ሕዝቡ አሁን የሚፈልገው-፦ የድርጅት ብዛት ሳይሆን ጠንካራ የሕዝቡን ትግል በመምራት ወደ ፊት የሚያራምድ ሁሉም ጎሳዎችና ነገዶች በእኩልነት፤በአንድነትና በጋራ ተከባብረውና ተባብረው የሚኖሩባት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን የሚገነባ፤የሕግ የበላይነትና ፍትሕ የሰፈነባት፤ሉዓላዊነቷ የተከበረና የታፈረ ሥርዓት የሚያመጣ ለሕዝብ ተአማኒነት ያለውን ድርጅት ነው።
    ዛሬ በቅርብም ይሁን በሩቅ የሚገኙ የኢትዮጵያ ወዳጅ አገሮች ፊታቸውን ዞረውብናል እንዲያውም በአገር ውስጥና በውጭ አገር ኢትዮጵያውያን እየታደኑ እንዲታሰሩ፤ለሰው በላው ህወሃት ተላልፈው እንዲሰጡና እንዲገደሉ እያደረጉ ነው።ኢትዮጵያውያን አገር ጥለው እንዲሰደዱ የሚያደርገውን አንኳር ጉዳይ እንመልከት ካልን፦ተወልደው ባደጉበት አያት ቅድመ አያቶቻቸው ደማቸውን አፍስሠው፤አጥንታቸውን ከስክሰው አስከብረው ባቆዩአት አገራቸው እንዳይኖሩ ያደረገው ህወሃት ነው።ህወሃት ሀብታቸውን ዘርፎ በድህነትና በችግር እንዲማቅቁ አድርጓል፤ያስራቸዋል፤ይገድላቸዋል፤አስሮ ክብርን በሚነካና በእጅጉ በየትኛውም አገር ታይቶና ተሰምቶ በማያውቅ ሁኔታ እርቃናቸውን ሆነው የሚመረመሩባትና ራሳቸውን ወደታች ዘቅዝቆ ወፌ ይላላ የመገረፉባት፤በፈላ ዘይት የሚጠበሱባት፤በቀዝቃዛ ውሃ የሚሰቃዩባት የባርያ ሽያጭ በቀረበት በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ወጣት ሴቶችንና ወንዶችን ወደ የተለያዩ አገሮች በኩንትራት ለዘመናዊ ባርነት አሳልፎ የሰጠ ከሃዲና ወሮበላ ቡድን በሥልጣን ላይ ያለባት አገር ናት ኢትዮጵያ ።ታዲያ ይህ ያላሰደደ የቱ ነው የሚያሰድደው?ከስደቱ ባሻገር ሌላ የተሻለ አማራጭ የለም ወይ?ለሚለው አማራጭ አለው።ራስን ነፃ ለማውጣት መታገል።ዳሩ ግን ትግሉን ከማን ጋር?የሚል ጥያቄ ሲነሳ የተቃዋሚ ኃይሎች የሚመልሱት ጥያቄ ይሆናል።
        አንድ በቅርቡ ኢትዮጵያ ደርሶ የተመለሰ ሰው እንዳወራኝ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሆቴል ሰዎች በልተው ያተረፉትን ምግብ(ቡላ) ከመደፋቱ በፊት ከሆቴሉ ሠራተኞች በመረከብ ከሰባት መቶ እስከ ስምንት መቶ ደመወዝ የሚከፈላቸው ቤተሰብ ማስተዳደር የሚያስችል አቅምና ተመጣጣኝ ክፍያ ስለማያገኙና የኑሮ ሁኔታው ጣራ ላይ በመወጣቱ የተመለሰ ምግብ ገዝተው ቤተሰብ እየመገቡ እንደሚገኙ ገልጾልኛል። በአንጻሩ ደግሞ እግረ-ደረቁ የህወሃት ቡድን ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ አደገች ተመነደገች እያለ የተለመደ የውሸት ቱልቱላውን ሲያናፍስ ይስተዋላል።
     ከሩቅ ሆኖ መተንበይ አዳጋች ቢሆንም በሕብረተሰቡ ላይ እየደረሱ ያሉት የደረሱት በውጭም በሀገር ቤትም የተፈጠሩት ሁኔታዎች እንደሚያመለክቱት በወርሃ ሚያዝያ የመን፤ደቡብ አፍሪካና ሊቢያ ላይ ብቻ በክርስቲያን ኢትዮጵያውያን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት የተሠነዘረብን ወርሃ ሚያዝያ የኢትዮጵያ ጥቁር ቀን የሆነበት የካቲት 12 እንድናስብ ያደረገን የህወሃት ሥርአት አላኖር አላስኬድና አላስቀምጥ ብሏቸው ዳቦ ፍለጋ ሲንከራተቱ ሕሊናን በሚሰቀጥጥ ዘግናኝ ሁኔታ እንደ በግ ሲታረዱና በጥይት ሲቆሉ ተመልክተናል።ይህ በእውነቱ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ ለሚያምን ሁሉ እንቅልፍን የሚነሳ፤ብሔራዊ ሞራልን የሚሰብር ሁኔታ ተከስቷል፤ደርሶብናል።ይህን ሁሉ ችግር ያመጣብን የጠባቦችና የጎጠኞች የህወሃት ድናቁርቶች ስርአት ነው።በመግደል በማሰርና በማሰደድ የሀገር ሀብት በመዝረፍ የስርአት አልበኝነት ስርአትን በማራመድ የሥልጣንን እድሜ ለማራዘም በከንቱ መንደፋደፍ ይህንም እንኳን ለማድረግ አቅም ይጠይቃል። ህወሃትን፦ ሕገ-አራዊቱ ሕግ አያስጥለውም።
ይህ በአገር በቀል ጣሊያኖች እየተካሄደ ያለው ፋሽስታዊ ሥርዓት እንዲያከትምና እንዳይደገም እኛ ኢትዮጵያውያን ምን ልናደርግ ይገባል?
አንድ ላለመሆን በጋራ ጽናት እንዳይኖረን መደማመጥ፤መከባበር፤መተማመን እንዳንችል የተስማማንና ለህወሃት ለም አፈር ሆነን በግል ባኅርያችን አገርን በጠራራ ፀሐይ የሚሸጥ፤ሕዝብን የሚፈጅና የሚያስፈጅ ከባእዳን ወግኖ የሚሞግተንና የሚወጋንን ህወሃትን የስልጣን ዘመኑ እንዲራዘምለት በማድረግ እኛው ራሳችን ነዳጅ ሆነን እያገለገልነው ስለምንገኝ መጀመርያ ከዚህ አደጋ ራሳችን ማውጣት አለብን።
አሁን እንደምንመለከተው በተቃዋሚ ኃይሎች አካባቢ (እየተፈፀሙ)እየተሠሩ ያሉት ሁኔታዎች ችግሮችን ተባብሰው እንዲቀጥሉ የሚያደርጉ በመሆናቸው በድርጅቶች ዙርያ ያለው ችግር ሳይቀረፍ እታገላለሁ ማለት በእንቅርት ላይ ጀሮ ደግፍ ስለሚሆን ይህን የማጋለጥና ሕዝብ እንዲያውቀው ማድረግ ይህ ሲሆን ተገደው ለሕዝብ ፍላጎት ተገዥ መሆናቸውን ማረጋገጥ።(ለአብነትም የቅንጅት፤መኢአድና የአንድነት ወርሾች ህወሃት ያደራጃቸው የህወሃት ጉጅሌዎች ናቸው)፤በውጭም ኢህአፓን ብቻውን ብንጠቅስ በአሁኑ ሰአት ከሶስት የተከፈለበት ሁኔታ ይገኛል፤የአርበኞች ግንባር ከሁለት ከተከፈለ ቆይቷል።በሌሎች ዙርያም ቱጃሩ እጀ ረጅሙ ህወሃት ላለመኖሩ ማስተማመኛ የለንም።በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሰርጎ መግባትና ማደናቀፍ የህወሃት ተግባር ስለሆነ ራስን ማጥራት ያሻል።
ተጨባጩን የህወሃት ሁኔታ ስንመለከት በሕዝብ ዘንድ አመኔታን ያጣ ወይም ከሕዝቡ መነጠሉን አምኖ ሁሉንም ነገር በኃይል ለማስቀጠል እየጣረ ያለበትና አባላቱም እየጣሉ መጥፋትና ማጉረምረም መጀመራቸው አንድ በመጨረሻዋ ሰአት ላይ የሚገኝን ስርዓት የሚያመላክቱ መሆናቸውን ያሳየናል።እዚህ ላይ ትኩረት አድርጎ በመሄድም ብዙ ድክመቶች ይታያሉ፡ህወሃት የሕዝቡን የትግል ስሜት ለመስለብ አቅጣጫ ሲቀይር ህወሃት የሚያናፍሰውን መከተል ሳይሆን በተፃራሪው የመቀስቀሻ ነጥቦችን አውጥቶ ማጋለጥ ያስፈልጋል።ህወሃት ልማታዊ መንግሥት ሊሆን አይችልም ምናልባትም ፎቆች፤መንገዶችና ቤቶች ተገንብተው ሊሆን ይችላል እነዚያ ግን ሀብትነታቸው የማን ነው? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል።ህወሃትን ራሱን ሊጠቅም የሚችል ነገር ካልሆነ በስተቀር በፍጹም ለሕዝብ ጥቅም የሚሰጥ ልማት እንደማይሞክረው የተረጋገጠ ነው።
ጅብ እንደ አገሩ ይጮሃል እንዲሉ አንዳንዶች ህወሃትን በሰላማዊ መንገድ ታግለን እናስወግዳለን ብለው የተነሱ ሲሆን አንዳንዶቹ ደግሞ ህወሃት የሰላማዊ ትግል ምንነት የሚገባው ድርጅት ስለአልሆነ እሱ በመጣበት መንገድ በመሄድ የጫካ ሕጉንና ሰው በላውን የህወሃትን ስርዓት እናስወግዳለን ብለው ራሳቸውን በተቃዋሚ ኃይል የመደቡና የተሰለፉ ይገኙበታል።ይህ ሰልፍ ህወሃት በራሱ አምሳል የለጠፋቸውን አይጨምርም።ከዚህች ነጥብ ላይ አንድ መጨመር የምፈልገው ነገር ቢኖር ህወሃት በመሃላችን እየገባ አንድነታችን አብሮነታችን ሲንደው እኛስ ለምን እሱ በሄደበት ሄደን አንከፋፍለውም?እርስ በርሳቸው እንዲባሉ አናደርጋቸውም?ለምሳሌ ህወሃት ብአዴን ብሎ የሚጠራውን ድርጅት ወስደን አማራ የሆኑትን አማራ ያልሆነው ድርጅት እንደ በግ ሲነዳቸውና እጃቸውን ቆልምሞ ሲያስር ሲያሳድድ፤ሲገድል፤ሲዘርፍ በቃ እጅህን ሰብስብ እንዲሉት ማድረግ አይቻልም ወይ?ነበረብን አሁንም ማድረግ አለብን።
ከሁለቱም ሰልፎች አንዳንድ ወስደን ብንጠናከር ህወሃት የማይወድቅበት አንድም ምክንያት የለም። ነፍጥ ካነሱት አንዱን ከሰላማዊ ተሰላፊዎች አንዱን ብንመርጥና የመምራት ኃላፊነቱን እንዲወስዱ ብናደርግ በሰው ኃይል በገንዘብና በተለያዩ ቁሳቁሶች አቅም መፍጠር ይቻላል። ሁልጊዜ በአንድ አይነት መንገድ እየሄዱ መታገል ስልትን ማስበላትና ትግሉን ከምንኮላሸት አያድነውም። የትግል ስልቶች እንደየ ወቅቱ የፖለቲካ ትኩሳት መቀያየር ይኖርባቸዋል።በግሌ እንደተመለከትኩት ሁለቱም አሰላለፍ በብዛኛው እያስቀጨ ያለው የአማራውን ነገድ ሕዝብ ነው ለምን? ያልን እንደሆነ፦
       1/ ህወሃት ሰበበ-አስባብ ፈልጎ ማጥፋት የሚፈልገው ገና ድርጅቱ ሲመሰረት ዓላማየ ብሎ የተነሳበትም የአማራውን ሕዝብ  በመሆኑ፡ 2/ አሁን ላሉት የተቃዋሚ ኃይሎች የመታገያ ነጥብ መነሻ የሚሆኑ ብዙ ምንያቶች ያሉት በመሆኑና የአማራ ነገድ ሕዝብ የሚኖርበት አካባቢ ለትግል ጥሩ የተፈጥሮ አቀማመጥ ስለአለውና ከጎረቤት አገር የሚያዋስን በመሆኑ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሉዓላዊነት ጉዳይ የጎላ ታሪክ ያስመዘገበ ኃላፊነትና ግዴታውን የሚያውቅ ሕዝብ በመሆኑ አካባቢው ሊመረጥ ይችል ይሆናል። 3/ ከአንድ ጹሑፍ ያገኘሁት መረጃ እንደሚገልጸው በድሮ ጊዜ የወሎ የመሬት ቆዳ ስፋት 94.400 ኪ/ሜትር የጎንደር መሬት ቆዳ ስፋት 74.200 ኪ/ሜትር፤ የትግራይ 65.900 ኪ/ሜትር ሲሆን በአሁኑ ሰአት የትግራይ መሬት የቆዳ ስፋት 102.000 ሆኖ ይገኛል።ይህ ማለት ህወሃት ከሁመራ፤ወልቃይት፤ጠገዴ፤ጠለምት፤ዳንሻን ከጎንደር ራያና ሰቆጣ አበርገሌን ከወሎ በመውሰድ ያደረገውን ትግራይን የማስፋፋት ሊሎች አጎራባች ክፍለ ሀገሮችን የማሳነስና ሕዝቡን የማፈናቀል አብይ ዓላማ መሆኑን የሚገልጽ አንድ የመታገያ አጀንዳም ስለሚሆን የትግሉ ማዕከል ሊሆን ይችላል ዳሩ ግን ከጥቅሙ ጉዳቱን የሚያመዝን እዳይሆን በጥናት የተደገፈ የትግል ስልት መቀየስን ይጠይቃል ይህ የተሟላበት አካሄድ አይመስልም።
በሀገር ቤትና በውጭ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ትግል ማቀናጀትን በሚመለከት 1/ ዲያስፖራው ሊያበረክት የሚችለው አስተውጾ ምንድን ነው?ብሎ መለየት 2/ በሀገር ቤት ያለው ሕዝባዊ አመጽ ሊደረስበትና አመራር ሊያገኝ መቻል አለበት እንዴት ብሎ ለሚለው ጥያቄ፦1/ በሰላማዊ ትግል ላይ የሚገኙትን መጠቀም 2/ የህቡእ አደረጃጀትን ስልት መከተልና ቴክኖሎጅውን በመጠቀም መረጃ መለዋወጥ አስፈላጊ ናቸው ብየ አምናለሁ።በተለይ ለዚህ እኩይና ፀረ-ሕዝብ የሆነ የህወሃት የጀርባ አጥንት በሆኑት የደህንነት፤የመከላከያ፤የፌደራልና የየክልል ፖሊስ፤የክልል ፈጥኖ ደራሽ፤የአጋዚ ሠራዊት እየተባለ በሚጠራውና በካድሬው አካባቢ የሚደረጉትን እንቅስቃሴዎች በሰላ ሁኔታ መከታተል።
    አገርን ለመገንባትና ለማበልፀግ ጤናማ ሕብረትሰብ ፤የተማረና በሙያ የሰለጠነ ኃይል እንዲኖረን ለማድረግ ከድኻው ሕዝብ የሚሰበሰበውን ግብር ለትምህርት በመበጀት ሁኔታው በሚፈቅደው መጠን በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ በቁጥሩ የማይናቅ ምሁር ኢትዮጵያ እንዳላት ይታወቃል። ይሁን እንጅ ይህ አስተሳሰበ ኩድኩድ የህወሃት ቡድን የኢትዮጵያ ምሁራንን ኮቴ ኮቴያቸውን እያለ አገር ጥለው እንዲሄዱ አድርጓል፤የቀሩት ዱላውንም ችለን በሀገራችን ያሉትን ደግሞ የህወሃት አባል አይደላችሁም በማለት ከሥራ ገበታቸው እንዲፈናቀሉና ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እንዳያስተዳድሩ አድርጓል።በውጭ ያለው ምሁርም እባብ ያየ በልጥ ይሸሻል እንዲሉ ወደ ሀገሩ ተመልሶ ሕዝቡንና አገሩን እንዳያገለግል በመደረጉ የባእዳን አገልጋይ ሆኖ ይገኛል።
   እኛ ኢትዮጵያውያን በውጭው ዓለም የምንታወቀው ድህነትና በርሃብተኛነት ብቻ እንዲሆን ሆነ ተብሎ የተሸረበብን ተንኮል ፍጥነቱንና እድገቱን ጨምሮ ስደተኛ የሚለው ታክሎበት ወገኖቻችን በሀገር ውስጥ ከመዋረድና ሶስተኛ ዜጋ ሆኖ ከመገኘት ሞትን ለመጋፈጥ ወይም ለጊዜው ሞትን አምልጦ ዳቦ በልቶ ለማደር የሰሐራን በርሃ ሲያቋርጡ ርሃብ፤አውሬና የውሃ ጥማት የፈጃቸው፤ባህር አቋርጠው ሊወጡ ሲሉ ያለቁት፤በየመን፤በደቡብ አፍሪካ፤በሳኡዲ ዐርብያ በግፍ ያለቁት፤ሊብያ በጥይት የተቆሉትና በቢላ እንደ በግ የታረዱት በውስጣችን እንደ እሳት እያንገበገበን ባለበት ወቅት ህወሃትና የህወሃት ግብረ በላዎች መሳለቂያ ሲያደርጉን ተመለከትን ከዚህ ወዲያ ውርደትና ሞት የለም።ብሔራዊ ሞራላችንን ነክተውታል፤ከወላጆቻችን የወረስነውን አኩሪ ታሪክ አርክሰዋል፤ድንበራችን አስደፍረዋል፤ሉዓላዊነታችንን አስደፍረዋል፤አንገታችን ደፍተን እንድንሄድና አደባባይ እንዳንወጣ አድረገውናል። ጎበዝ!! ለትግልና ህወሃትን ለማስወገድ እነዚህ በቂ አይደሉም?ጥያቄየ አንድ እንሁን አንዲት አገርና አንድ ሕዝብ ነው ያለን የሚለው ነው።
     ድርጅቶች በበዙ ቁጥር የሕዝብ ኃይልና የገንዘብም ይሁን የቁሳቁስ(ማቴርያል) አቅማችን ያንኑ ያህል ነው የሚያንሰውና በውስን አቅም የጥቃት ሰለባ እንድንሆን የሚያደርገን።ለምን ለህወሃት የሚመች ለም መሬት ሆነን እንገኛለን? ሕዝባችን ሲጨርሱት፤ተራ በተራ ነጣጥለው፤ከፋፍለው ሲፈጁት ምን እየጠበቅን ነው?መካካዱ፤አለመተማመኑና በጥርጣሬ የመተያየቱ አባዜ ያብቃ !! ተራውን ለህወሃት እንስጠውና እኛ በአንድነት በጋራ ቆመን የጋራ ጠላታችን የሆነውን የህወሃትን ግባተ መሬት እናፋጥንለት።በምርጫው ዋዜማ እያሰማ ያለውና በምን መሰናዶ ላይ እንዳለ ይታወቃል ዛሬም እንደ ምርጫ 1997ቱ ወገኖቻችን የሞት ሰለባ እንዳይሆኑ እንታደጋቸው በግንባር ቀደምትነት የተደራጁ የተቃዋሚ ኃይሎች ኃላፊነት ቢኖርባቸውም እያንዳንዱ ሕዝቡን አገሩን የሚወድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በዚህ ጉዳይ ላይ ሊረባረብበት ይገባል።
               እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ከጥፋት ይጠብቃት!!
    በባእድ አገር በአሰቃቂ ሁኔታ የሞቱ ወገኖቻችን ነብስ ይማር ቢተሰባቸውን ጽናት ይስጥልን!!
                          ሕዝባዊ እንብኝተኝነቱ ይጠንክር!!!
                                       ገብርየ በለው።  
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/41331#sthash.OrdimU3b.dpuf

No comments:

Post a Comment