Thursday, February 19, 2015

ኢትዮጵያ ውስጥ የስፖርት ጋዜጠኛ ወይስ ተርጓሚ ነው ያለው? (ሁኔ አቢሲኒያ)

Addis-Ababa-Stadium
“የምን ማራዶና የምን ፔሌ ፔሌ 
እኛም አገር አለ ገብረመድኅን ኃይሌ”
ደምሴ ዳምጤ ጎልታ የምትጠቀስለት መንቶ ግጥሙ ነበረች፡፡ ለአገሪቱ ስፖርት ዕድገት በተለይም እግር ኳሱ እንዲያብብ በሙያው ያደረገው ጥረት ኢትዮጵያውያን ተጫዋቾች ክሂላቸው ከማንም እንደማያንስ በማንፀባረቅ ነበር፡፡ በ1970ዎቹ መጨረሻና በ80ዎቹ መጀመርያ ጎልተው ወጥተው የነበሩት እነሙሉጌታ ከበደ፣ ሙሉጌታ ወልደየስ፣ ገብረመድኅን ኃይሌን ሲያወድስ ገጣሚ ሆኖ በመገኘት ነበር፡፡
ስፖርት እንደ አንድ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ምጣኔ-ሃብታዊ ጉዳይ ራሱን የቻለ ሰፊ ርዕሰ ጉዳይ እየሆነ የመጣ ሲሆን ሊሰጠው የሚገባው ግምትም ያን ያህል እየከበደ መጥቷል፡፡ በመሆኑም እነዚህን ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ምጣኔ-ሃብታዊ ጉዳዮች ብቻ የሚተነትኑ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃን እንዳሉ ሁሉ ስፖርታዊ ጉዳዮችን ብቻ የሚተነትኑ ጋዜጦች፣ ሬድዮኖች፣ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች፣ ድረ-ገጾች እና ሌሎች መገናኛ ብዙሃን በርካታ ናቸው፡፡

በአሁኑ ወቅት በሃገር ቤት እየተተገበረ ያለው የስፖርት ጋዜጠኝነት ምን ያህል ሙያዊ እና ስነምግባራዊ ነው ለሚለው እኔም በርካታ አሉታዊ አስተያየቶች አሉኝ፡፡
eth football team1በአብዛኛው ለሃገርቤት መገናኛ ብዙሃን ስፖርት ማለት የእግር ኳስ ጨዋታ ሆኗል ያውም የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታ፡፡ የእግር ኳስ ጨዋታ ካለው አዝናኝነት፣ ከተመልካቹ ብዛት እና ከሚያንቀሳቅሰው ከፍተኛ ገንዘብ አንጻር በጋዜጣ ላይ የሰፋውን ቦታ እና በሬድዮ እና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ላይ ደግሞ የበዛውን የአየር ሰዓት ቢይዝ የጎላ ጥያቄ ላያስነሳ ይችላል፡፡ ሆኖም በእኔ ዳሰሳዊ ግምት በተለያየዩ የኤፍ ኤም እና የኤ ኤም ሬድዮ ጣቢያዎች ከሚቀርቡ የስፖርት ዝግጅቶች ብዙውን ግዜ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ሁኔታ እና አንድ አንድ ግዜ ከዘጠና በመቶ በላይ የእግር ኳስ ጉዳይ የሚተነተን ሲሆን ከዚህም የሚበዛው የአውሮፓ የእግር ኳስ ክለቦች ጨዋታ ጉዳይ ነው፡፡
ይህ የሆነበት ምክንያት በተለያዩ ጉዳዮች ተፅዕኖ ሊሆን ይችላል አንደኛ የእግር ኳስ በተለይም ደግሞ የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታ ከሌሎች ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች የተሻለ አዝናኝ ነው ተብሎ ስለሚገመት፤ ሁለተኛ በሃገር ውስጥ አብዛኛው የስፖርት አድናቂ ማህበረሰብ የእግር ኳስን በተለይም ደግሞ የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታን የበለጠ ይወዳል ተብሎ ስለሚገመት፣ ሦስተኛ ደግሞ በተለይ ከአውሮፓ ሃገራት መገናኛ ብዙሃን የሚለቀቁ እጅግ ብዛት ያላቸው እና የየክለቦቻቸውን ሁኔታ የሚተነትኑ መረጃዎች በተትረፈረፈ ሁኔታ ማግኘት መቻሉ የጋዜጠኞችን ትኩረት በመሳቡ ሊሆን ይችላል፡፡ በእነዚህም ሆነ በሌሎች ምክንያት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን የአውሮፓ ክለቦችን የእግር ኳስ ጨዋታ ተንታኝ ሆኗል፡፡
ዋናው ርዕሰ ጉዳይ ተረስቶ ከጨዋታው ጋር የማይያያዙ ጉዳዮች በበለጠ ትኩረት ሲዘገቡ ይስተዋላል፡፡ እከሌ የተባለው አንድ የአውሮፓ ክለብ ተጫዋች የሴት ጓደኛ ስትደሰት እና ስትበሳጭ ምን እንደምታደርግ ጠቀመውም አልጠቀመውም ለኢትዮጵያዊ ስፖርት ተከታታይ ይቀርብለታል፡፡ አሁንም ጠቀመውም አልጠቀመው ስለተጫዋቹ አባት፣ እናት እና ሌሎች ዘመዶች ማንነት እና ምንነት እንዲያነብ ወይንም እንዲያዳምጥ ይደረጋል፡፡
የእኛ ሐገር የስፖርት ጋዜጠኞች በተደጋጋሚ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን ሊያሠለጥኑ በሚመጡ የውጭ ሐገር አሠልጣኞች ጭምር መሣለቂያ ሆነዋል የቅርቡን ብናስታውስ እንኳን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በማሊ ብሔራዊ ቡድን መሸነፉን ተከትሎ በተዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ሐገር ቤት የሚገኙ የመንግስት እና የመንግስት ደጋፊ ጋዜጠኞች ለቡድኑ መሸነፍ አሰልጣኙን ተጠያቂ ለማድረግ የተለያዩ ጥያቄዎችን የጠየቁ ሲሆን ለጋዜጠኞቹ ምላሽ የሠጡት የብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ በጋዜጠኞቹ አቅም እና እውቀት ተሳልቀዋል፡፡eth football team2
አንድ የኢቲቪ ጋዜጠኛ አሰልጣኙን “ቀኝ ተከላካይ ቦታ ችግር እያለ ለምን ሌላ ተጫዋች አልቀየሩም” ብሎ ሲጠይቅ አሰልጣኙ በግርምት “እንግዲህ ጎበዝ የቀኝ ተከላካይ እጥረት እንዳለ አውቃለው በዚህ ቦታ ጎበዝ ተጫዋች የባርሴሎናው ዳንኤል አልቬስ ነው እርሱ ደግሞ ብራዚላዊ ሆነ እንጂ ኢትዮጵያዊ ቢሆን አሰልፈው ነበር በተረፈ ደካማ ተጫዋች ለመኖሩ ተጠያቂ የሐገሪቱ አሰራር እንጂ የእኔ አሰለጣጠን አይደለም” ሲሉ አክለዋል፡፡
ሌላው አስገራሚ ጉዳይ “እኛ የተሸነፍነው በማሊ ብሔራዊ ቡድን እንጂ በኦሮሚያ ብሔራዊ ቡድን አይደለም” ሲሉ ጋዜጠኞቹ ጫጫታ አሰምተዋል፡፡ አሰልጣኙ ትክክል ናቸው ምክንያቱም ለኦሮሞ ጎሳ ብሔረሠብ የሚል ስያሜ ከሠጠን ለአማራውም ጎሳ ብሔረሰብ የሚል ስያሜ ከሠጠን እና ብሔር ማለት ደግሞ የአንድ ሐገር ነዋሪ መሆኑን የሚያውቅ ጭንቅላት ካለን ለምን የኦሮሚያ ብሔራዊ ቡድን የአማራ ብሔራዊ ቡድን ሲባል ንዴት ውስጥ እንገባለን፡፡ ዘይትገርም ነው ነገሩ የመንግስት ጋዜጠኛው የብሔርን ትክክለኛ ትርጓሜ ሣያውቅ በየደቂቃው ብሔር ብሔረሠብ ሲል ይውልና የኦሮሞ የአማራ ብሔራዊ ቡድን ተብሎ ሲጠራ እምቧከረዩ ይላሉ ብሔር አለ ካላቹህ የአማራ ወይም የኦሮሞ ብሔራዊ ቡድን ሲባል ምን ያናድዳችኋል፡፡
eth footballአብዛኛው ኢትዮጵያዊ የስፖርት ጋዜጠኛ የውጭ ሐገር ስፖርት ሲተነትኑ ለሚሰማቸው ኢትዮጵያዊ የስፖርት ታዳሚ አፍ የሚያስከፍት ቃላት ሲያወጡ ይሠማል በጥቂቱ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ክህሎት ላለው ግለሠብ ግን የእነርሱን ወሬ ከእንግሊዝ የስፖርት ታብሎይዶች የተተረጎመ መሆኑን እማኝ ሳያስፈልገው የመረጃውን ምንጭ በመግለፅ ያስረዳችኋል፡፡ ይህን ጊዜ እኛ ሐገር ያለው የስፖርት ጋዜጠኛ ሳይሆን የእንግሊዝ የስፖርት ጋዜጣዎችን ወደ አማርኛ እና ወደተለያዩ የሀገራችን ቋንቋ ተርጉሞ የሚያቀርብ የስፖርት ጋዜጣ ተርጓሚ መሆኑንን ልብ ይሏል፡፡
ለዚህም ይመስለኛል አንድ ኢትዮጵያዊ የስፖርት ጋዜጠኛ ስለ ኢትዮጵያ ቡና እግር ኳስ ክለብ ድክመት ከሚያወራ ይልቅ ስለ አርሠናል ድክመት እና ስለ ማንችስተር ቀጣይ እቅድ ቢያወራ ይቀለዋል፡፡ የቀለለው በርካታ መረጃን ስለሚያገኝ እንዲሁም ያንን መረጃ ወደአማርኛ ተርጉሞ ለማቅረብም ምቹ ስለሆነ ነው፡፡ ስለ ኢትዮጵያ ቡና ስለምን ለምን አታወሩም ሲባሉ መልሳቸው ስለ ቡና መረጃ ከየትም አናገኝም የሚል ነው፡፡ ይህ እጅግ አሳፋሪ እና አሸማቃቂ መልስ ነው የአርሠናልን ጉዳይ የእንግሊዝ ታብሎይድ ላይ የሚፅፍ አንድ ብሪታንያዊ ጋዜጠኛ መረጃው መጥቶለት ሳይሆን ሄዶ ጠይቆ ነው መረጃውን ያመጣው፡፡ የኢትዮጵያ ጋዜጠኛ ግን የቡና ወይም የኤልፓ ዜና እቤቱ ድረስ በኢንተርኔት መስኮት እንዲመጣለት ይጠብቃል፡፡ ከዛም ውጪ አዲስ አበባ ስታዲየም ገብቶ ጨዋታ አንብቦ ትንተና ለመስጠት ያለው እውቀት አነስተኛ መሆኑን ተረድቶ አልያም ለመሸፈን ሲል ስለ ሮናልዶ የወገብ ቁጥር ይነግረናል፡፡
በአንድ ወቅት ፌስቡክ ላይ “ብሔራዊ ቡድኑ ከተሸነፈ ለመንግስት ጋዜጠኛው ጥፋተኛ ፌዴሬሽኑና አሰልጣኙ እንጂ ፌዴሬሽኑን እና አሰልጣኙን በበላይነት የሚመራው የስፖርት ሚኒስትር አይደለም” የሚል ፅሁፍ ማስነበቤን ይታወሳል፡፡ ይህ ነገር ዛሬም ሳይቀየር የመንግስት ሚዲያውን ስከታተል እንደጠበኩት አሰልጣኙን ሲሰድቡ ነው የሚያረፍዱት፡፡ አሠልጣኑ ምን ማድረግ እንደነበረበት ግን አይነግሩንም ምክንያቱም ይህን ለማድረግ እውቀት ያስፈልጋል አልያም የገነነ መኩሪያ አይነት ስፖርታዊ እይታ ያስፈልጋቸዋል፡፡genene
እግር ኳሳችን እንዳያድግ እንቅፋት የሆነው የስፖርት ሚኒስቴር እንጂ አንድ አሰልጣኝ ሊሆን አይችልም አሰልጣኝ በመቀያየር ውጤት ሊመጣ አይችልም፡፡ አሰልጣኝ ከተቀየረም እንደ ገነነ መኩሪያ በእውቀት ተመርተን ሐሳብ ማቅረብ ይኖርብናል፡፡ ካልሆነ ግን ዘወትር የስፖርት ሚኒስተርን ችግር ይፋ ሳናወጣ እና እንደገነነ መኩሪያ ሊብሮ Genene Mekuria Libro የመሳሰሉትን ድንቅ ኢትዮጵያዊያን አቅም እውቀት ትተን የትም ልንደርስ አንችልም፡፡ በህይወቴ በሐገራችን ስፖርት ዙሪያ ሳስብ የገነነ መኩሪያን አቅም ኢትዮጵያችን እንድትጠቀም አለመደረጉ ሁሌም የሚያነገበግበኝ ጉዳይ ነው፡፡ ገነነ ብሔራዊ ቡድኑን ይመራ ዘንድ የግድ በባለስልጣናቱ ተወዳጅ መሆን የለበትም፡፡
እጅግ የሚከፋው ግን እንዲህ ከላይ የጠቀስኳቸውን ስህተቶች በሙሉ ባካተተ መልኩ የሚተገበረው የስፖርት ጋዜጠኝነት ትክክለኛው ስፖርት ጋዜጠኝነት እንደሆነ እየተወሰደ መምጣቱ ነው፡፡ አንድ ጉዳይ በተሳሳት መልኩ በተደጋጋሚ ሲተገበር እና ለየት ባለ መልኩ በተስተካከለው መንገድ ጉዳዩን የሚያቀርበው ሲጠፋ ያ የተሳሳተ መንገድ በዘልማድ ተቀባይነት ያገኘ መንገድ ሆኖ ይቀጥላል፡፡ ስፖርት ጋዜጠኝነትም በዚህ መልኩ እየነጎደ ሲሆን ይኄ ሙያውንም ባለሙያውንም ቀስ በቀስ መጉዳቱ አይቀርም፡፡
‪#‎ሁኔ አቢሲኒያ

No comments:

Post a Comment