Monday, February 16, 2015

የክፋት ዘመን ምን ያህል ይረዝማል?

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ (ከአዲስ አበባ – ma74085@gmail.com)
… ነቢዩ ዳንኤል በተናገረው መሠረት የሚያረክሰውን አፀያፊ ነገር በተቀደሰ ሥፍራ ቆሞ ታዩታላችሁ፡፡ … በዚያን ጊዜ ለነፍሰ ጡሮችና ለሚያጠቡ እመጫቶች ወዮላቸው፡፡ … ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ያልሆነ፣ ወደፊትም እርሱን የሚመስል ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ይመጣል፡፡ እነዚያ ቀኖች ባያጥሩማ ኖሮ አንድም ሰው መዳን ባልቻለ ነበር፤ ነገር ግን ስለተመረጡት ሰዎች [ሲባል] እነዚያ ቀኖች ያጥራሉ፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ፣ ማቴ. 24
road
ሎሬት ፀጋየ ገ/መድኅን “ረሀብ ስንት ቀን ይፈጃል?” በሚል ርዕስ ስለርሀብ ማለፊያ ግጥም አስነብቦናል – ያኔ በደጉ ዘመን፡፡ የክፋትስ ዘመን ምን ያህል ይሆን? ብለን ደግሞ እኛው ለኛው እንጠይቅ፡፡ 17? 23? 40? 100? 1000 ወይንስ ከዚህም በላይ? የክፋትንና የመልካም ዘመናትን መጥባትና ማክተምስ የሚቆጣጠረው አካል ማን ነው? የፍትህ ሚዛኑስ ምን ያህል ምክንያታዊ ነው? የት ሆኖና በምን አግባብና መለኪያስ ነው ቁጥጥሩን የሚያደርገው? እስኪ ከምንገኝበት ሸውራራ ዳይሜንሽን ወጣ ያለ ጥያቄ እንጠይቅ፡፡ መልስ ሰጭ ባይገኝም መጠየቁ አይከፋም፡፡ የኔቢጤው “ፍጠረኝ ሳልለው ፈጥሮኝ ለመከራ፤ ይሄው እበላለሁ የመከራ እንጀራ” ያለው ወዶ እንዳልሆነ ያጤኗል፡፡ሰው ካልመረረው ሽቅብ አንጋጦ የበላይን(ፈጣሪን) አይወቅስም፤ አያማርርምም፡፡

(ሳልረሳው አንድ ነገር ጣልቃ ላስገባ፡፡ ይህን ኢሣት ምን ላድርገው ትሉኛላችሁ? ጆሮው ላይ ተቀምጦ የሚነግሩትን ሁሉ አልሰማ አለ’ኮ፡፡ ምን ዓይነት ዳተኝነት ነው እባካችሁ፡፡ እንዳልተወው በጭራሽ አልችልም፤ እንዳልከታተለውም አልቻልኩም፡፡ ችግሩ የኔም የጣቢያውም ሣይሆን የሚቀር አይመስለኝም፡፡ … “የዶክተር ካሣ ከበደና የቀድሞው ሚኒስትር ዴታ የአቶ ኤርምያስ ለገሠ ቲቪ” በሚል ርዕስ በዚያን ሰሞን አንዲት ማስታወሻ ልጽፍ ከጀልኩና የራስን ተቋም ሰድቦ ለሰዳቢ መስጠት ነውር መሆኑን ከመረዳት አንጻር አስቤ ብቻ ተውኩት፡፡ ነገሩ ማለትም ችግሩ ግን እየባሰ እንጂ እየተሻሻለ ሲሄድ አልታየኝም፡፡ ከቤተሰብ ዘወትር የምጣላበትና “ትንሹ የቤት ውስጥ አምባገነን” የሚል ዘለፋ ያተረፍኩበት ጣቢያ ከሁለት ያጣ ጎመን እያደረገኝ ነው፡፡ እርግጥ ነው ለተቀማጭ ሰማይ ቅርብ መሆኑ ይገባኛል፡፡ ግን ግን ሰማዩ ምንም ያህል ቅርብና በእጅ ተዳሳሽ ይሁን የኢሣትን ችግር በቅጡ ካሰቡበትና ዝናና ስመጥርነት ካላጥበረበራቸው፣ በዚያም ሰበብ ይቺ በምንም ዓይነት መድሓኒት ልትለቀን ያልቻለች ኢዮጵያዊት በአንድ ሥኬት የመኩራራት ስሜት ካላስቸገረቻቸው በስተቀር ዘወትር የሚወቀሱበትን የአቀራረብ ችግር ለመቅረፍ አይሳናቸውም ባይ ነኝ፡፡ የአንጀት ምሥካሬ ለመስጠት ኢሣት አማራጭ የሌለው የሕዝብ ዐይንና ጆሮ መሆኑን ወያኔዎችም ጭምር የሚመሠክሩት የዘመናችን ዐቢይ እውነት ይመስለኛል፡፡ ኢሣት ጣቢያ ለአንድ ቀን እንኳ ቢቋረጥ ጭንቅ ጥብብ የምንል ወገኖች ሞልተናል – “ትልቅ ጦር ባይወጉበት ያስፈራሩበት” ይባላል፡፡ ሆኖም ቢሆን ምንም እንኳን የገንዘብ አቅም ኖሮን ባንደግፈውም ስለሥርጭቱ የሚሰማንን መናገር ግን የምንችል ይመስለኛል፡፡ በነገራችን ላይ “ኢሣትን ዕርዱ” የሚል አማርኛ እንደማይገባኝ በዚች አጋጣሚ ልገልጽ እወዳለሁ፡፡ አማርኛው ምን መሆን እንዳለበት በእውነቱ አላውቅም፡፡ ግና ዕርዳታ ሣይሆን ግዴታ ነው፡፡ ማን ማንን ይረዳል? እኔ ልጄን ሳሳድግ እየረዳሁት ሣይሆን ግዴታየ ስለሆነ ነው፡፡ ኢሣትንም የወለዱ ቅን ዜጎችና እያገለገሉ ያሉ ሀገር ወዳድ ባለሙያዎች ለሀገር ብለው አምጠው የተገላገሉትን ልጅ የመርዳት ሣይሆን በአግባቡ የመደገፍና የማሳደግ ግዴታ ነው እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ያለበት ኃላፊነት፡፡ መርዳት በአማራጭነት የሚቀርብ ነው – አለመርዳትም መብት ነውና፡፡ ኢሣትን መደገፍም እንበለው ማገዝ ግን ሀገራዊ ግዴታችን መሆን አለበት፡፡ ምን ያህል ግልጽ እንደሆንኩ አላውቅም፡፡ ደግሞም እባካችሁ ኢሣቶች ይህን “የኢትዮጵያ መንግሥት” የምትሉትን ነገር ደግሞ ተውን፡፡ ሕዝቧን እየበታተነና ምድሯን እያረከሰ የሚገኝን የወሮበሎች ጥርቅም እንደመንግሥት ቆጥራችሁ የዕውቅና ድጋፍ አትስጡ፡፡ ቢያንስ “የወያኔ/ኢሕአዴግ መንግሥት” ወይም “የኢትዮጵያ መንግሥት ተብዬው” ወይም “ራሱን የኢትዮጵያ መንግሥት ነኝ ብሎ የሚጠራው የወያኔው ቡድን” ብትሉ ምን አለበት? ኧረ ስሙን!
በተረፈ ኢሣቶች መውቀስንና መተቸትን ብቻ ሣይሆን መወቀስንና መተቸትንም ልመዱት እንግዴህ፡፡ አታሞ በሰው እጅ ታምር ነው፡፡ … ኢሣትን በከፈትኩ ቁጥር ከሞላ ጎደል የሚገጥመኝ ዝግጅት አንድም የዶር. ካሣ ከበደና የሲሣይ አጌና ውይይት ነው፤ አንድም የኤርምያስ ለገሠ ገለጻና ማብራሪያ ነው(ፐ! ይህ አንደበተ-ርቱዕ ወጣት ብላቴና ምን ዓይነት ጠቃሚ ሥራ እየሠራ እንደሆነ እኔና ታሪክ ብቻ ነን የምናውቀው!)፣ አንድም (ከተመለሱም ከሣምንታት በኋላ)የደሬና የነፋሲል ቃለ መጠይቅ ከኤርትራ ነው፣ አንድም …፡፡ በቃ – በሚያንገሸግሽ ሁኔታ ዝግጅቶች ይደጋገማሉ፡፡ እውነቴን ነው ማን አስገደደህ እንዳትሉኝ እንጂ – እስኪያንገሸግሽ ድረስ፡፡ በሚቀርብ ዝግጅት ተወራርደህ ቲቪህን ብትከፍት የማሸነፍ ዕድልህ ሰባና ሰማንያ ከመቶ ይሆናል፡፡ ችግራቸው በተወሰነ ደረጃ ይገባኛል – ግን እመብርሃንን በጣም በዛ፡፡ ለምን እንዲህ ይሆናል? ሰዎች በዚህ ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ በዚያው ጣቢያ አልፎ አልፎ እሰማለሁ፡፡ ታዲያ ለምን አንደመጥም? ይህን ተራ ችግር ማረም ምን ይገዳል? ነው ማን ምን ያመጣል? ዓይነት ወያኔያዊ ትዕቢት ዋሽንግተንም ገባች? የሕዝብን አነስተኛ ቅሬታ ከአሁኑ ማዳፈንና ጆሮዳባ ማለትም ከተጀመረ መጨረሻው ምን ሊሆን እንደሚችልና ገበሬው “የዋልንበትን [እርሻ[ አረም በላው” እንደሚለው ሊሆን እንደሚችል መገመት አይከብድም፡፡ ጓዶች፣ እንሰማማ ማለትም እንደማመጥ፡፡ በትዕቢትና ትምክህትም ይሁን በሌላ ምክንያት ችላ መባባል ወያኔንም – ለነገሩ ማንንም – አልጠቀመም፤ በምናብም በአካልም እያሳደደው ያለው የትዕቢቱና የዕብሪቱ የዞረ ድምር ነው፡፡ በመሠረቱ አንድን ቤት ለመሥራት ከባድ ነው – ለማፍረስ ግን በጣም ቀላል ነው – ዝናና ታዋቂነትም እንዲሁ ነው፡፡ አሮጌ ወይን በአዲስ አቅማዳ ከተገለበጠ ውጤቱ የዜሮ ድምር ነው ፤ እ-ል-ፍ የለም፡፡ ባሉበት መንቦራጨቅ፤ በያመቱ ወደታች መንጎድ፡፡
ስለዚህ እንደማመጥ – እንደኔ በዚህ መልክ ስሜቱን ያልገለጠና የሚናደድ በየዓለም ማዕዘን መኖሩን መረዳትም ይገባል፡፡ ባህላችን መናናቅና መጠላለፍ የበዛበት ቢሆንም እንለወጥና የሚመር ትችትንም ቢሆን ተቀብለን በአወንታዊነት እንጠቀምበት፡፡ ሌላው ችግር የግርጌ ላይ የጽሐፍ ዜናዎች ላይ የሚታየው የፊደል ግድፈት ትርጉም እስከማዛባት የሚደርስ መሆኑ ነው፡፡ በሞክሼ ሆሄያት ላይ የሚታየው ‹እንከን› “እዬዬም ሲዳላ ነው”ና አልገባበትም፡፡ ግን ግን ለምሣሌ ከዛሬው ዜና ብጠቅስ – ቆይ አይቼው ልምጣ – አዎ “ወቅሰዋል” ለማለት ይመስለኛል “ወቅሰቃል” የሚል ማሰሪያ አንቀጽ ይነበባል፡፡ ይህን ዓይነት ችግር በተለይም መጠነኛ የሰዋስው ችግር አልፎ አልፎ በነቢቢሲና አልጀዚራም አያለሁ፤ ጥቂት ጊዜ ከተመላለሰ በኋላ ግን አይተው ያስተካክሉታል እንጂ ኒውስባሩ ስህተትን ይዞ ሲንከረፈፍ እንዲውል አያደርጉም፤( በኢሣት ውስጥ የሰው ዕጥረት መኖሩና ሁሉንም ነገር በጥቂቶች ለመሸፈን መሞከሩ እንቅፋት እንደሚፈጥር ግን አልክድም)፡፡ ደግሞም የግርጌ ዜና (ኒውስባር) አንድ ወቅታዊ ዜና በጣም በአጭሩ የሚቀርብበት እንጂ ሙሉ ዜናው የሚዘከዘክበት አይደለም፡፡ በጥቅሉና ከጠቃቀስኳቸው ችግሮች በተጨማሪ የዜና ደረጃዎችን መለየት (የትኛው ወሬ በዜናነት ይቀርባል/አይቀርብም)፣የዜና ቋንጣዎችን ማስወገድ፣ የኢትዮጵያን ቀናት ለምሣሌ ሰኞ/ማክሰኞዎችን ከሌሎች ሀገራት ሰኞ/ማክሰኞዎች ለይቶ ማወቅ ወዘተ. ትኩረት ቢሰጣቸው መልካም ነው – በኢትዮጵያዊ ቅዳሜ ላይ በሚነገር ዜና “ … የኢአወግ ዋና ሊቀመንበር የሆኑት አቶ አጥናፌ አልፎአይቼው ትናንት ረቡዕ ጧት ላይ ከመኖሪያ ቤታቸው በፌዴራል ተወስደው ወዳልታወቀ ሥፍራ መሠወራቸውን የኢሣት ምንጮች ገለጹ” ቢባል ያደናግራል፡፡ የአቅም ጉዳይ ካልሆነ ስለኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ለባለሙያዎች ሥልጠናዎች ቢሰጡ ደግሞ አይከፋም፡፡ ባለኝ ጭላንጭል ዕውቀት ብዙዎቹ የኢሣት ጋዜጠኞች በፕረስ ሚዲያ እንጂ በሬዲዮና በቴሌቪ… ለነገሩ ይሄ ይሄ ምን አገባኝ ልጄ፡፡ ወደጀመርኩት አመራሁ – በዚህ ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ ዴሞክራሲያዊ መብት በሚባል ፈሊጥ የተነሣ ያስቀየምኩት ቢኖር ይቅርታ እጠይቃለሁ፤ ኢትዮጵያዊ ሆነህ መፈጠር እኮ ዕዳ ነው – የሚታየውንም የማይታየውንም፤ የሩቁንም የቅርቡንም እንፈራለን፡፡ መንግሥቶቻችን የለየልን ቦቅቧቃ አድርገውን ቀሩ፡፡ እግዜር ይይላቸው!)
አልቃኢዳንና አይስልን (ISIL/IS/ISIS/ Islamic Caliphate …)፣ ቦኮሃራምንና ሕወሓትን (TPLF)፣ አልሻባብንና “Skull and Bones, Knights Templar, Luciferians, Bohemians … “ የሚሉ ኆልቁ መሣፍርት የሌላቸው የምሥጢራዊ ድርጅቶች ኢሉሙናቲዎችን በየዘመናቱ እያገነነ የዓለምን ምሥኪን ሕዝብ የስቃይ ሰለባ የሚያደርጋቸው ማን ነው? ይህ የመከራ ፍርድ መቆሚያው መቼ ይሆን? ምንም እንኳን የክፋታችን ብዛት ገደብ ያጣ ቢመስልም የዘወትር ጸሎታችን “እንደኃጢያታችን ብዛት ሣይሆን እንደቸርነትህ መጠን ይሁንልን” ነውና የዚህ የሁሉም ነገሮች ገዢና የበላይ ተቆጣጣሪ ይህን ሁሉ የአጋንንት መንጋ የክፋት ሥራ እየተመለከተ እንዴቱን አስቻለው? እጅግ ይገርመኛል፡፡ ፈጣሪ ለፍጡራኑ እንዴት አይቀናም? እረኛው በጎቹን ተኩላ ሲነጥቀው እንዴት አይቆጭም? በመጨረሻው መፍረዱ ለማይቀረው የትግስቱ ኹዳድ ግን ለእንደኔ ዓይነቱ ደካማ ፍጡር የመሮጥ አቅም በጣሙን የሰፋና ተስፋ አስቆራጭ የመሆኑ ምሥጢር ሁልጊዜ ያስጨንቀኛል፡፡ የሱና የኛ የጊዜ ሥሌት መለያየት ደግሞ ከማስደነቅ አልፎ አሁን አሁን ያናድደኝና ያነጫንጨኝ ይዟል፡፡ ግን ምን ምርጫ አለ? ምንም፡፡ ሰዎች ወደው አልነበረም “ወደሽን ቆማጢት ንጉሥ ትመርቂ” ያሉት …
ሰሞነኛ የወያኔና የአይስል የክፋት ተግባራት በጅጉ ስለተመሳሰሉብኝ ትንሽ ማውራት ፈለግሁ፡፡ ሁሉም ነገር እርግጥ ነው ከልኩ አይዘልም፡፡ ዘመኑ የመጨረሻው ትልቅ ክፋት የሚከሰትበትና የሰው ልጆች እውነተኛ ሰይጣናዊ ማንነት በግልጽ እየታየበት የሚገኘበት ነው ማለት ይቻላል፡፡ በሩቅም በቅርብም የሚስተዋሉ አረመኔያዊ ተግባራት ከዚህ ውጪ የሚያናግሩ አይደሉምና፡፡ አንድን ንጹሕ የዓለም ዜጋ የብረት ፍርግርግ ውስጥ ከትቶ በእሳት እያቃጠሉ በሚሰማ የሰቆቃ ጩኸት መደሰትና ዓለምን ማሳዘን ምን ይባላል? ዘመነ ሀሙራቢ፡፡ ዘመነ ኦሪት፡፡ ዘመነ “ጥርስ ለጥርስ፣ ዐይን ለዐይን”፡፡ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡
የዛሬ ጧቱን የቢቢሲ አንድ ዘገባ ድረገፁ ላይ ሳነብ የተሰማኝ ስሜት በቃላት ሊገለጽ አይችልም፡፡ እነዚህ አይስሎች ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ የጨለማው ጎራ – የሲዖሉ ንጉሥ ሊቀ ሣጥናኤል አምርሯል፡፡ ቀኑ ስለቀረበች ይመስለኛል ጎራዴውንና መንሹን አንስቶ ዓለምን እያበራያት ነው፡፡ ምዕመናን – አታጋትረኝ ብሎ መጸለይ ነው፡፡ የትም ሂድ ፣ የትም ግባ … ይህ አፍራሽ ኃይል (Negative Energy/Force) በዓለማችን ዙሪያ ግዘፍ ነስቶ ምድራውያንን እያመሰ ነው፡፡ ጥቂት ጥቂትም ቢሆን መጻሕፍትን ለሚያገላብጡ ወገኖች ይህ ዓይነቱ ድርጊትና አድራጊዎቹ ምን አመላካችና ከምን እንደተላኩም ጭምር መለየቱ ከባድ አይደለም፡፡ የበለሲቱን ማቆጥቆጥ ጭምር ለሚገነዘቡ፡፡ … ምን ቀረው? ምናልባት ግማሽ ወይም ሢሶ ሐሙስ? አላውቅም፡፡ መገመት ግን የሚያስቸግር አይመስለኝም፡፡ ከጭምብሎቻችን ለአፍታም ቢሆን ወጣ ብለን ዘመኑን እንቃኝና የትኛው ምዕራፍ ላይ እንደምንገኝ እናስተውል፡፡ (በነገራችን ላይ ታደሰ ብሩ( ኦ! ታዴ በጣም ነው የምወድህ! ልጅ ይውጣልህ- ወላድ በድባብ ትሂድ ማለት ይሄኔ ነው፤ ለካንስ ጨርሰን አልጠፋንምና ጎበዝ! ‹አሃ፣ ሀገር ቢኖረንና ሲኖረን ለሁለንተናዊ መልሶ ግንባታው ሰዎች አሉን› ብዬ ኮራሁ) በትናንትናው የዕውቀት ብልጭታ የኢሣት ላይ ትምህርቱ ወያኔዎችን እንደየጭቃ አንጎላቸው ደረጃ ከፋፍሎ ያስቀመጠባቸውን ቅርጫቶችና መጠሪያቸውን በጣም ወደድኩለት፡፡ የነሣሞራን የ‹ደነዞች› የቅርጫ መደብ በተለይ በጣም ነው ‹የተላጥኩበት› ማለትም (የተደሰትኩበት)፣ በመጽሐፍ መልክ በቶሎ ቢያወጣው ብዙዎችን ይታደጋል፣ ያስተምራልም ብዬ አምናሁ – የተወሰኑ ወገኖቻችን ከተዘፈዘፉበት የጥፋት አረንቋ ቢወጡልን፡፡ ሰው እኮ እያጣን ነው ውድ ወገኖች! በቁጥር እንዳታምን ጓድ እንትናዬ! ቁጥር አሁን አይሠራም፡፡ ያ ሟች ዘፋኝ – ሶሎሞን ተካልኝ – “አከንባሎሽ ዜሮ፣ ምጣድሽም ዜሮ፣ ሁሉም ዜሮ ዜሮ” ብሎ የማይሞት ዜማ ማቀንቀኑ ጨርሶ እንዳይሞት በጀው፡፡ ጭንቅላት ወደሆድ ወረዳ ወርዶ በፈርስ ውስጥ መሽጎላችኋል፤ አቤት የአጋሰሱ ብዛት!! )
አይስል ተዓምር መሥራቱን ቀጥሏል – ወያኔም፡፡ ጣፋጭ ፍሬ ከዛፍ ላይ ያስታውቃል፡፡ አይስልና ወያላዎችም ማለትም ወያኔዎችም የአንድ ዘር ውጤቶች፣ የድቅድቁ ጨለማ ንጉሠ ነገሥት የሆነው የሰይጣን መንግሥት(ኢምፓየር) ወኪሎች መሆናቸው ከተግባራቸው በቀላሉ ይታወቃል፡፡ በጥፋትም ሆነ አለጥፋት፣ በፍርድም ሆነ አለፍርድ፣ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ሰውን መግደል ያለና የነበረ ነው – ሰውን መግደል በራሱ ስህተትና ኢ-ሃይማኖታዊም ቢሆን፡፡ ግን ግን የአገዳደሉ “ሥርዓት” ሲታይ ብዙ ያስብላል፡፡ ሰውን እንደከብት በማረድ መግደል በልዩ የአገዳደል ሥርዓት (Death Cult) ሰይጣንን ለማስደሰት የሚደረግ አምልኮተ-ጣዖታዊ ድርጊት እንጂ ሌላ ትርጉም ሊሰጠው የሚችል አይደለም፡፡ በ21ኛው ክፍለ ዘመን በእሳት በማቃጠል፣ በሰላ ጩቤ አንገት መቀንጠስ፣ ግማሽ አካልን ጉድጓድ ውስጥ ቀብሮ በድንጋይ መውገር፣ እጅን መቁረጥ፣ አፍንጫን መፎነን፣ በቀን በዐርባና ሃምሣ በሚመደቡ ሺዎች ጅራፎች አንድን ሰው መግረፍ … ዘግናኝ ግድያና ቅጣት መፈጸም፣ መናገርንም አለመናገርንም፣ ማሰብንም አለማሰብንም፣ መተኛትንም አለመተኛትንም … እንደወንጀል ቆጥሮ አንድን ንጹሕ የዓለም ዜጋ ማሰቃየት ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት ምናልባት ቀሲስ አንቷን ሌቪ የደረሰውን የሰይጣን መጽሐፍ ‹ቅዱስ› በማገላበጥ መገንዘብ ይቻል እንደሆነ እንጂ በሰብኣዊ አእምሮ ተመርምሮ ሊደረስበት የሚችል ፍልስፍና አይደለም፡፡ ግርምት ዓለም! ዓለም ዘጠን መባሉ ሌህ ይሆን? ዐይንህን ጨፍነህ ዝም ብለህ ዓለማችንን ብታስባት አንዳች ነገር ሆድህን ያባባዋል – ጤናማ ሰው ከሆንክ፡፡
እነአይስልንና ወያኔን ማን እንደፈጠራቸው፣ ማን አርሞና ኮትኩቶ ለአካለ-ጥፋት እንዳደረሳቸው፣ የጥፋታቸው ተጠቃሚ በዋነኛነት ማን እንደሆነ እዚህ ላይና አሁን መጠቆም ተገቢም አስፈላጊም አይመስለኝም፡፡ እንጂ ወያኔም ሰባት እያለች፣ አይስልም አምስትና ስድስት እያለች ባጭር ማስቀረት የሚችል ኃይል በዓለማችን ውስጥ ነበር፡፡ ግንሳ የተባለ ነገር አይቀርምና መንስዔውና ውጤቱ የሆነውን ቢሆን አፈጻጸሙና ፍጻሜው ግን የሚቀር ባለመሆኑ እንድናይ የተገደድነውን ነገር እያየን እንገኛለን፡፡ የአፍራሹ ኃይል መኪና ነዳጁ አልቆ እስኪቆም ወይም ፈጣሪ ትግስቱን ጨርሶ የመጨረሻ ፍርዱን እስኪሰጥ ድረስ ድንጋይ ቅል ነው፤ ቅልም ድንጋይ፡፡ ምርጫ የለም ወገኔ፡፡ አለማመን ግን ይቻላል፡፡ ዐይንን መጨፈንም፡፡ የአፍራሹ ኃይል አጫፋሪና የሠራዊቱ አባል እንዳንሆን ግን እንጠንቀቅ፤ እኔም እንደጳውሎስ “ቆሞ ያለ የሚመስለው ይጠንቀቅ፤ የወደቀስ የሚያስፈራው የለም” ልበል ይሆን?
ሁለት ሰው በአንድ ሰው መለወጥ ትርፍ አለው፡፡ አንድ አብራሪ ለቅቀው ጆርዳን ውስጥ የታሠሩባቸውን ሁለት አጥፍቶ ጠፊዎችን ማስለቀቅ ይችሉ ነበር፡፡ ሰይጣናዊ ተፈጥሯቸው ግን ያን እንዲያስቡ አላስቻላቸውም፡፡ ለነገሩ አምስትና አሥር አጥፍቶ ጠፊ ልከው አንድ አብራሪ ሊገድሉስ ይችሉ የለምን? እነሱ የሚያስደስታቸው የሌሎች ማዘን ነው፡፡ በማሳዘን የሚደስት አይስልንና ወያኔን የመሰለ አጋንንታዊ ፍጡር ሰዎችን ከማስጨረስ አንጻር እንደፔፕሲ ማስታወቂያ “ተጨማሪ ይጠይቁ!” ይላል እንጂ በገንዘብም ሆነ በቁጥጥሩ ሥር ባሉ እሥረኞች ተደራድሮ የታሠረበተን ሰው አያስለቅቅም፡፡ ሰይጣን ሰውን በማስደሰት አያምንም፡፡
አይስልና ወያኔ ከአንድ ማኅጸን የወጡ ከአንድ ወንዝም የተቀዱ የዲያብሎስ መንትያ ልጆች እንደመሆናቸው የሰው ስቃይና መከራ ያስደስታቸዋል፡፡ ስለሩቅና ቅርብ አለቆቻቸው መናገር አይገባም ብያለሁ፡፡ ስለነሱ ብቻ፡፡ በነዚህ የጥፋት ኃይሎች ልብ ውስጥ ዘረኝነት አለ፡፡ ሃይማኖት ግን ምናልባት ለማስመሰል ካልሆነ በስተቀር እምብዝም የለም፡፡ አይስሎች የእስልምና ህግጋትን በፈለጉት መንገድ እየጠመዘዙ ይጠቀሙባቸዋል እንጂ በአግባቡ እንደኪታቡ አይመሩም፡፡ ወያኔዎች ከናካቴው ሃይማኖታቸው ድርጅታቸው ሕወሓት ናት፡፡ ሁለቱም ዋና መመሪያቸው በግል ጥቅምና ፍላጎት የተቀነበበ ጠባብ ዓላማቸውን በማንኛውም ሥልት ከግብ ማድረስ ነው፡፡ ከፍላጎታቸው አንጻር የሚቆም ማንም ይሁን ማን እጃቸው በገባላቸው ማናቸውም መሣሪያ ያጠፉታል፤ ቋንቋ በነሱ ቤት ዋጋ የለውም፡፡ ለንግግርና ለውይይት የሚያውሉት ጊዜም የለም – ውይይትና ንግግር ጊዜ ማባከኛ እንደሆነ ያምናሉ፡፡
የአይስሎች ዋና ዓላማ በሱኒዎች የሚመራ አንድ ትልቅ እስላማዊ መንግሥት ማቋቋም ነው – በሂደት መላው ዓለምን ወደሱኒነትና ወደሙስሊምነት የሚለውጥ፡፡ በሂደት መላውን ሺዓና ኢ-ሱኒ የእስልምና እምነት ተከታይ የሆነን ሁሉ በማቃጠልና በማረድም ይሁን አሳድዶ ባህር ውስጥ በመክተት የሚያወድም፡፡ በሂደት መላውን የክርስትና እምነት ተከታይ ከአውሮፓና አሜሪካ፣ አፍሪካና አውስትራሊያ – ከሁሉም አህጉራት ጠራርጎ ድራሹን የሚያጠፋ፡፡ በሂደት ሁሉንም ያለም ሀብት መቆጣጠርና በነዳጅ ከብረው ይሠሩትን እንዳጡት እንደሣዑዲዎቹ ነገሥታት ቅንጡ ሕይወት መምራት፡፡ በሂደት ጎጋውን (ተራውን) ዜጋ በሸሪዓ ህግ እግር ከወርች ጠፍንጎ ራስን በዓለም ቅንጦት ማምነሽነሽ፡፡ ይህ ነው የአይስሎች ዓላማ፡፡
ወያኔና አይስሎች ምንና ምን ናቸው፤ የራስጌ ወለባ ያንገት ሀብል ናቸው፡፡ ግጥሙ እንዲያ ይሆን? አዎ፣ ወያኔዎች ዓላማቸው አንድና አንድ ነው፤ ግልጽና ግልጽ፡፡ የመጀመሪያው አማራን ማጥፋት ነው – የአደባባይ ምሥጢር አወጣሁ መሰለኝ፡፡ አማራ ከጠፋ ብዙ ነገር አብሮና ተባብሮ እንደሚጠፋ ያውቃሉ – ወይም ቢያንስ ይገምታሉ፡፡ በሆነ ባልከፋ – ቢያንስ ከነሱ አንጻር፡፡ አማራ ግን ቫይረሱን በመላዋ ኢትዮጵያ ያሠራጨና ቢሞትም የማይቆጨው ይመስለኛል፡፡ የአማራነት ቫይረስ – ችግር ከተባለ – ችግሩ በአንዲት ኢትዮጵያ ማመን ነው፡፡ ተበጣጥሶ በሰማንያና ዘጠና ‹ፌዴራላዊ መንግሥት› ሥር መኖር እንደኢትዮጵያ ላለ ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ፣ ሃይማኖታዊና ሥነ ልቦናዊ ቁርኝት ላለው ሕዝብ እንደማይጠቅም መስበኩ ነው የአማራ ችግር፡፡ ሌሎች ተጓዳኝና መጥፎ የሆኑ ቅንጫቢ ታሪኮች ቢኖሩም እዚህ ላይና አሁን ማንሳቱም ሆነ በአጉሊ መነጥር እያዩ የሞተን መውቀሱ አግባብ አይመስለኝም፡፡ ከፈለግንም ዘመኑ ሲደርስ በአስተማሪነቱ እያወሳን ልናወጋው እንችላለን፡፡ እንጂ አማራንማ በኢትዮጵያ ውስጥ ቢያጠፉት በውጭ እያበበ የጠፋበት ዘሩን በመተካት ሂደት ላይ ነው ያለው አሉ፡፡ እኔማ የት አባቴን አይቼው፡፡ ይቺ የወያኔ የዘር ጨዋታ ግን እንዴት ያለች ረቀቅ ያለች ጨዋታ ናት በል! ሰው አማራ ልሁን ብሎ ይፈጠራል? እንዲያ ቢቻል ኖሮ ነጭ አሜሪካዊ ሆኜ አልፈጠርም ነበር? ታዲያ ወዶና ፈቅዶ ባልተቀበለው ማንነት ሰው ለምንድነው የሚገደለውና የሚሳደደው? ምን ዓይነት ድንቁርና ነው ጎበዝ! ዛሬ በሚሊዮኖች ያጠፋኸው የገዛ ወገንህ ደም ነገ ይለቅሃል? ደሞም የጅልነት ጅልነት አማራና ትግሬ ተለያይቶ ሞቶ የአንድን ግንድ ሁለት ቅርንጫፎች ለማቆራረጥ መሞከራቸው፡፡ ወደ ዝርዝር መግባቱ ይቅርብኝ፡፡
አማራን በማጥፋት ብዙ ነገር እንደሚያገኙ ያምናሉ ብያለሁ – ወያኔዎች፡፡ መነሻቸው ጥፋት በመሆኑ ግን ዱሮም የትም እንደማይደርሱ እናውቅ ነበር፤ አሁንም – እደግመዋለሁ – በተለይ አሁን አሁን መፃኢ ዕድላቸው ለነሱ ባይከሰት እኛ አሣምረን እናውቃለን፡፡ ይሁንና ከጥንትም ቢሆን የዱባ ጥጋብ ካለስንቅ ማዘመቱ ግልጽ ስለሆነ ያፈሰሱት ደምና የከሰከሱት አጥንት የሚያስከትልባቸውን የመከራ ጎርፍ ባይረዱት አልፈርድባቸውም፡፡ የመጨረሻ ዕድሉን የተረዳ አምባገነን መሪ በዓለም ስለመኖሩ አላውቅም፡፡ ከሞላ ጎደል ሁሉም ዐይነ ሥውራን ማለትም ደናቁርት ናቸው፡፡ ጋዳፊ በመቀመጫው ሣንጃ እየተቀበቀበበትም የሊቢያ መሪ እንደነበረና አጋቾቹንም ለማዘዝ እየዳዳው ነበር – አምባገነንነት ኅሊናን በዋናነት ጨምሮ ሁለመናን ያሳውራል፡፡ ጋዳፊ “ምን ሆናችኋል? በሊቢያ ምን ነገር ተፈጠረ?” እያለ ሊገድሉት የሚቋምጡትንና በቁጥጥራቸው ሥር ያዋሉትን ሕዝባዊ ሚሊሻዎች ይጠይቅ ነበር አሉ፡፡ አምባገነን እንዲህ ነው፡፡ እርግጥ ነው – እኛ ጋ አንድ አምባገነን የለም፤ እሱን በፈጣሪ መንገድ ተገላግለነዋል፡፡ ያሉን ቁጥራቸውና መደበቂያ ዋሻቸው በውል ያልታወቀ በቡድን የተደራጁ ማፊያዎች ናቸው፡፡ አሁንም እርግጥ ነው – ከአንድ አምባገነን ይልቅ የዚህ ዓይነት የማፊያዎች ቡድን ከሥሩ ነቅሎ ለመጣል ይበልጥ አስቸጋሪ ሣይሆን አይቀርም፡፡ የተውተበተበው የችግራችን ውል ሲገኝ ግን መፍትሔው ቀላል ነው፡፡
ለፈገግታ – በአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመን ነው አሉ፡፡ አንድን አካባቢ ያወኩ ሽፍቶችን በጦር ለመያዝና ወደመንግሥት ለማስገባት አንድ የመንግሥት ጦር ይላካል፡፡ ከጦርነቱ መልስ የመንግሥት ጦር አዝማች የነበረው ሰው ከሰዎች ጋር ወሬ ይዟል፡፡
ለመሆኑ ጦርነቱ እንዴት ነበር? ብዙ ሰው ተጎዳባችሁ?
ኦ! በጣም ከፍተኛ ጦርነት ነው የተካሄደው፡፡ ብዙ ጦራችን ሙትና ቁስለኛ ሆነብን፡፡ ውጊያው ከባድ ነበር፡፡
እንዴ፣ ያን ያህል? በሽፍቶቹ ወገን ብዙ ኃይል ነበረ ማለት ነው?
አይይይ… እንደሱማ ቢሆን በማን ዕድላችን! ጦርነት የገጠመን ለካንስ አንድ ሽፍታ ብቻ ሆኖ ውር ውር እያለ ጨረሰን እንጂ! በመጨረሻ ግን ተሣካልንና ገደልነው፡፡(የጠላት ትንሽና ጥቂት የለውም፡፡ ጉንዳን ሱሪ ታስወልቃለች፡፡ ደርግ የናቃት ወያኔም በለስ ቀንቷት የመላውን ኢትዮጵያ ሕዝብ ላለፉት ብዙ ዐሠርት ዓመታት ሱሪውን ብቻ ሣይሆን ፓንትና ካልሲውንም አስወልቃ(ና)ለች፡፡ መለመላችንን ያስቀረችንን ወያኔ ተረባርበን ካላስወገድናት ዐጽማችንም ለቅርስነት አይተርፍም፡፡)
ወያኔ ለጥፋት ጉዞው በሥጋትነት ከመዘገበ ፈጣሪንም ቢሆን ከመንበሩ አውርዶ ከማሰርና ከመግረፍ ከመግደልም አይመለስም፡፡ ብዙዎቹ ወያኔዎች አስተሳሰባቸውና ግንዛቤያቸው ከዶሮ ስለማይሻል – አካላቸው እንጂ አእምሯቸው እንደማያድግና ወደታችም እየቀጨጨ እንደሚሄድ ብዙ ጊዜ በመነገሩ እዚህ ላይ አልደግምም – ብቻ ከዶሮና ከጥንቸል አንጎል ስለማይሻል ዋና እምነታቸው ማጥፋት ነው – (They are nihilists). በማውደም የሚያምኑ ለታሪክ ቅርስ ይቅርና ለሰው ነፍስም አንዳችም ደንታ የሌላቸው ናቸው፡፡ የወገናዊነት ስሜትም ለማንም ቢሆን የላቸውም – የራሳችን ነው ለሚሉትም ጭምር፡፡
ካነበብኩት – አይስሎች እስራኤል ፍልስጥኤሞችን ጋዛ ውስጥ ስትደበድብ ደስ ነበር ያላቸው፡፡ ምክንያቱም ቅድሚያ ትኩረታቸው ከእስልምናና ከዐረባዊነትም በወረደ ሱኒያዊነት ነውና፡፡ በ69ዓ.ም የዚያድባሬ ሶማሊያ ኢትዮጵያን ስትደበድብ ወያኔዎች በደስታ ይፈነጥዙ ነበር – በውጊያው ሳይተባበሩትም አይቀሩም፡፡ ምክንያቱም የነሱ አጀንዳ ከኢትዮጵያዊነት በእጅጉ የወረደ ከትግሬነትም ጭምር ያነሰ ተራ ፀረ-አማራና ፀረ-ኦርቶዶክስ አጀንዳ ስለነበረና ስለሆነም ነው፡፡ የጠላትን ጠላት ወዳጅነት በግርድፉ ከተቀበሉት አደገኛ ነው፡፡ እነዚህ አይስሎችና ጓደኞቻቸው ወያኔዎች ግን እስከዚህን የወረዱ በጊዜያዊ ጥቅምና በቂም በቀልና ጥላቻ በታወረ መሠሪ ዓላማ የሚነዱ ማይማን በመሆናቸው የጥፋት ተልዕኳቸውን ተመሳሳይነት በቀላሉ መረዳት ይቻላል፡፡ እነዚህን መሰሎቹ ፍጡራን ሰው ለመሆን የሚቀራቸው የአጨራረስ ችግር አለባቸው፡፡ ከማስሎው የፍላጎት መገለጫ እርከኖችና ከዕድሜ ዓይነቶች ሥነ ልቦናዊ ትንተና አንጻር ስለነዚህ ጎደሎ ፍጡራን አንዳንድ ነጥቦችን መጥቀስ አሰኝቶኝ ነበር – ነገር ባይበዛብኝ ኖሮ፡፡
አይስሎች እስላሞችን ያርዳሉ፡፡ ዐረቦችን ያርዳሉ፡፡ ከተቃወሟቸው የራሳቸውን ሱኒዎችንም ቢሆን ያርዳሉ፡፡ አንጀታቸው ደንዳና አንጎላቸውም ከሩቅ የሚከረፋ ነጭ ጭቃ ነው፡፡ ወያኔዎችም ለይቶላቸው የሚጠሏቸውን እንደአማራ የመሰሉ ወገኖችን ብቻ ሣይሆን ራት ጋብዘውና በሠፈራቸው አስተናግደው ያሳደሯቸውን የራሳቸውን ወገኖች የሚያርዱ ከኢትዮጵያ ቀርቶ ከየትኛውም ዓለም ባህል ያልተቀዱ ነውረኞች ናቸው – ነውረኛ የሚለው ቃል ራሱ አይገልጻቸውም እህቴ፡፡ ሰው ፊት የሆድ አየር ያመለጠውም ነውረኛ – ተሳዳቢም ነውረኛ ከተባለ የወያኔን ድርጊት የመሰለ ወንጀል የሚፈጽም ምን ቢባል ጥሩ እንደሚሆን ፈልጉ – የእስካሁኖቹ ቃላትና ሐረጋት የወያኔን ዕኩይ ድርጊቶች ለመግለጥ በእጅጉ የተቸገሩ ይመስለኛል፡፡ ወያኔዎች ከቋንቋ በላይም ናቸው፡፡ ግን ወንዶች ናቸው! አንድን ጠማማም ይሁን ቀጥ ያለ ዓላማ ከግብ ለማድረስ ቆራጥ መሆን ይገባል፡፡ እንዶድን ውኃ የወሰዳት በየዋህነቷ መሆኑን ወያኔዎች ጠንቅቀው የተረዱ ይመስላሉ፡፡ በመሆኑም ብሂሉ “ገጥመሃል፣ ገጥመሃል” ነውና ለዚህን ያህል ረጂም ዓመት ይህን ወልጋዳ አስተሳሰባቸውን በዬመጋጃዎቻቸው ላይ በውድም በግድም እየጫኑ እስከዚህ መድረሳቸው አድናቆትን ያሰጣቸዋል፡፡ ከ‹ምቀኝነት› በጸዳ መልኩ እዩትና አድንቋቸው፡፡ ይደልዎሙ! መዘናጋትን ሳያውቁ፣ ለጠላቶቻቸው አንድም በር ሳይከፍቱ የውስጥ ጠባቸውንና ቅራኔያቸውን በደም ሣይሆን ብዙውን ጊዜና በተደጋጋሚ በውኃ እያጠቡ እዚህ መድረስ ለብዙዎች መሰል እንቅስቃሴዎችና ተቋማት ከባድ ነው – ምናልባትም የማይቻል ጭምር፡፡ ለዚህም ይመስላል ከውድቡ የሚወጡ እንደስዬና ገብሩን የመሰሉ ሰዎች የፍቅር እትብታቸው አሁን ድረስና መቼም ቢሆን በቀላሉ ሊበጠስ ያልቻለው – ወያኔዎች አንዳች ምትሃት ሣይኖራቸው ይቀራል? በሕወሓትና በመለስ ፍቅር ተነድፎ የሚያለቅሰው ወገን እኮ ብዙ ነው፡፡ እንዘንላቸው፡፡ ተደጋግሞ የተነገረ ውሸት እውነት ነው ይባላል፡፡ እንኳንስ ብዙ ባልተማረና ባልተመራመረ የኛን መሰል ማኅበረሰብ መካከል ባደጉ አገሮችም ዘውጋዊ መናጆነትና ስሜታዊነት የራሳቸው አሉታዊና አወንታዊ ሚና አላቸው – በአንድ ነገር ላይ፡፡
በሌላ ወገን ስንመለከት ደግሞ ወያኔ ብዙ ትግራውያንን ገድሏል – ወንጀል ሠርተው ሣይሆን በኢትዮጵያዊነታቸው ብቻ፡፡ ወያኔ ብዙ ትግሬዎችን ለስደትና ለእንግልት፣ ለእስርና ለሥራ አጥነት ዳርጓል፡፡ ወንጀላቸው ያው ኢትዮጵያዊነት፡፡ የኢትዮጵያዊነትን ቫይረስ ለወጣቱ እንዳያዛምቱበት በመሥጋት ወያኔ ቀደም ካለ ጊዜ ጀምሮ አንቱ የተባሉ ትግራውያንን በልዩ ልዩ ዘዴ ገድሏቸዋል – ለምሳሌ ወባ ሳይዛቸው ወይም የወባ ሥጋት በሌለበት ሁኔታ በወባ መከላከያ ስም መድሓኒት በግዳጅ በማስዋጥ ብዙዎችን እንደገደለ አንብበናል፡፡ ተከታይ ለማፍራት እነሀውዜንን ጨምሮ ብዙ ንጹሓን ዜጎችን በደራ ገበያ ላይና በጸሎት ወቅት በደርግ ጦር የማስጨረስ ሤራዎችን ፈጽሟል፡፡ ለትግራውያን የመጣን የረድኤት እህል ለራሱ በመጠቀም ሕዝብን በርሀብ ጨርሷል፡፡ በትግራይ ሕዝብ ላይ ያልፈጸመው ግፍና በደል የለም፡፡ ይህ የኢትዮጵያ አይስል የደም ሱስ አለበት፡፡ ሱሱ በሚነሳበት ወቅት የሚመርጠው የጭዳ ዓይነት የለም፡፡ አይስሎች መግደል እንደሚያዝናናቸው ሁሉ – አይስሎች ገድለው የሚዝናኑት ሰው ይሁን እንጂ የትኛውም ቢሆን ግድ እንደሌላቸው ሁሉ ወያኔዎችም የደም አራራቸውን ለማስታገስ ትግሬም ሁን፣ አማራም ሁን፣ ኦሮሞም ሁን ይገድሉሃል፤ ሲገድሉህ ደግሞ በአንድ ጊዜ ጸጥ እንድትል አይፈቅዱልህም፡፡ የሚሰጡህ ሞት በኢንስቶልመንት ነው (death by instalment) ፡፡ በአንድ ጊዜ መሞትህ ላንተና ለወዳጆችህ ጥሩ ሲሆን እነሱን ግን አያዝናናቸውም፡፡ እናም እንዲዝናኑብህ ሞትህም በስቃይ የተሞላ መሆን አለበት፡፡ በርሀብ፣ በግርፋት፣ በአሰቃቂ እሥራት፣ በስድብ በማዋረድ፣ ምግብ በመከልከል፣ መድሓኒት እንዳትወስድ በማድረግ፣ ጉድጓድ ውስጥ ካለፀሐይ ብርሃን በርሀብና በስቃይ (ቶርቸር) በማማቀቅ፣ ወዘተ፣ ለቀናትና ለሣምንታት ለዓመታትም ጭምር ያሟሙህና በመጨረሻው አንተም ሳታውቀው እነሱም ሳያውቁትና ምናልባትም ዘንግተውህ በስብሰህ ትሞታለህ፤ ምን አለፋህ ወያኔዎች በግዳይ ዐይጦቻቸው እንደሚጫወቱትና በጨዋታውም እንደሚረኩት ድመቶች ናቸው፡፡ እርግጥ ነው – አንወሻሽምም – የየትኛው ደም ይበልጥ እንደሚጣፍጣቸው ለመረዳት ዐባይ ፀሐዬንና አቦይ ስብሃትን ወይም የመለስ ዜናዊን የሙት መንፈስ መጠየቅ ሊኖርብን ይችላል – ሌሎቹ ሊመልሱልን ካፈሩ ወይም ከፈሩ፡፡ አቤት የአማራ ደም ሲጣፍጣቸው! በምናቤ ፍንትው ብሎ ይታየኛል ወያኔዎች አማራን በማሰቃየት ሊያገኙ የሚችሉት ብዔልዘቡላዊ ደስታና እርካታ፡፡
አንዳንዴ አንድ አምባገነን ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ሮብሰፔር የተባለ ፈረንሣዊ ይመስለኛል “በመቶ ዐይጦች ከመገዛት ይልቅ በአንድ አንበሣ መገዛት ይሻለኛል” ብሎአል – በዚያ በፈረንሣይ አብዮት ወቅት የኮሚቴ ጋጋታ መቆሚያ መቀመጫ ቢያሳጣው ጊዜ፡፡ እውነቱን ነው፡፡ አሁን እኮ ውር ውር እያሉ በጠበጡን፡፡ ቀፎዎቹ እነኃይለማርያም ደሳለኝ በስልክና በብጫቂ ወረቀት እየታዘዙ የሚያከናውኑትን ሥራየቤታዊ የመላላክ ቲያትሮችን ወደ ጎን እንተዋቸውና ሀገሪቱ መሪ አልባ ናት፡፡ የታሠረን ለማስፈታት ማንን ትጠይቃለህ? ለይቶልን በደመ ነፍስ መጓዝ ከጀመርን ሦስት ዓመት ሊሆነነ ነው፡፡ በቁማችነ ሞትነ እኮ፡፡ ሁሉም አዛዥ ነው፡፡ ወንበሮች ባዶ ናቸው፡፡ ትዕዛዝ ታያለህ – አዛዡን ግን አታየውም፡፡ ማን የት ተቀምጦ ትዕዛዝ እንደሚያስተላልፍ አታውቅም፡፡ የተወነባበደ ሁኔታ ነው ያለው፡፡ የጨረባ ተዝካር፡፡ ዳኛ የለም፡፡ ፖሊስ የለም፡፡ አስተዳዳሪ የለም፡፡ ጠያቂም ተጠያቂም የለም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ፀሐይ ብርሀኗን ከልክላለች፡፡ ሁሉም ጨለማ ነው፡፡ እዚህ ስትሄድ እዚያ ይልሃል፡፡ እዚያ ስትሄድ ደግሞ እዚህ ይልሃል፡፡ ሆነም ቀረም ከፖለቲካው ውጪ ላሉ ነገሮች ዘርህና ገንዘብህ በእጅጉ ይጠቅሙሃል – እንደሚያዋጣህ ካመንህ አጥብቀህ ያዛቸው – ግን ዋጋ እንደሚያስከፍሉህ ዕወቅ፡፡ (ለአፍታ ፈታ በል – አንድ ሰው “እናንት ጎንደሬዎች ስትባሉ ‹ገደሉነ፣ በላነ፣ ጠጣነ› እያላችሁ ቃሉን ሁላ በ‹ነ› የምትጨርሱት ሙህናችሁ ነው?” ብሎ አንዱን የዚያ አካባቢ ሰው ይጠይቃል፡፡ ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው – ጠያቂው ጥያቄውን ከማጠናቀቁ ተጠያቂው ሰውዬ ፈጠን ብሎ “ለምዶብነ!” አይለው መሰላችሁ?)
እዚህ አገር ቤት ውስጥ ሰው ሁሉ የደነቆረ ይመስለኛል፡፡ ሰው ተጣርተህ በስንተኛው ጥሪህ እንደሚሰማህ መገመት አትችልም፤ አብዛኛው ዜጋ በራሱ ዓለም ጠፍቷል፡፡ ብቻውን እያወራ የሚሄደው ሰው ቁጥር እያሻቀበ ነው፡፡ እጁን እያወናጨፈ ከራሱ ጋር ክርክር ገጥሞ የሚወራከበው ሕዝብ የትዬለሌ ነው፡፡ ሁሉም ከየራሱ ጋር በሃሳብ ስለተጠመደ ከውጪው ዓለም ጋር ያለው ግንኙነት ከሞላ ጎደል ተቆራርጧል፡፡ እናም ተደነቋቁረናል፡፡ በየቦታው “እ?” እና “ኤ!” በዝቷል፡፡ የነዚህ የመደነቋቆርና የእርግማን ትዕምርቶች መብዛት ደግሞ የጤናማ ማኅበረሰብ ምልክቶች አይደሉም – ወይም ቢያንስ አይመስሉኝም፡፡ መብላት፣ መጠጣት፣ መስከር፣ ሰክሮና አብዶ ለብቻ እያወሩ መሄድ፣ መበሳጨት፣ መለመን፣ በኑሮ ተጎሳቁሎ በየመንገዱ ሲንከላወሱ መታየት፣ የጫት የሲጃራና የሀሽሽ ሰለባ ሆኖ በምርቃና መንጠራወዝ፣ ጎዳናን በበረንዳ አዳሪ ዜጎች መሙላት፣ በአካልና በመንፈስ መቀጨጭ፣ በአስተሳሰብና በአመለካከት መኮስመን … የሀገራችን ዋና ዋና መገለጫዎች ከሆኑ ዋል አደር አልን – ወያኔዎች ግን “በኛ አስተዳደር አልፎላችኋል፤ ከነህንድና ጃፓን ተርታ አሰልፈናችኋል” እያሉ ያላግጡብናል፡፡ ሊነጋ ሲል መጨለሙ የታመነ ቢሆንም የጨለማው መጠን ለብርሃኑ ፍንጠቃ ደደረበትና ሰቆቃዎ ሀበሻ አልቀንስ አለ፡፡ በተተለመልን መንገድ፣ በተቀደደልን ቦይ እየፈሰስን የመከራችንን ዘመን በማራዘም ላይ የምንገኝም ይመስለኛል፡፡
የኢትዮጵያ አይስሎች በርትተዋል፡፡ አባታቸው ከሞተ ወዲህ በተለይ ክፉኛ በመደናገጣቸው ምክንያት ሣይሆን አይቀርም መሥራት የሚገባቸውን መሥራት ከማይገባቸው መለየት አቅቷቸዋል፤ ፍጹሙን አብደዋልም ማለት እንችላለን፡፡ እንዲህ ከሰውነት ተራ ወጥተው ሲቅበዘበዙ ማየት እንደሰው ብቻም ሣይሆን እንደእንስሳዊ የጋራ ምንነትም በጣም ያሳዝናሉ፡፡በዚህ የ21ኛው መቶ የሥልጣኔ ክፍለ ዘመን ውስጥ ዓለም በቴክኖሎጂና በአስተሳሰብ የትና የት ደርሳ ሳለች እነሱ ልክ እንደጨለማው ክፍለ ዘመን የሁሉንም ችግሮቻቸውን መፍትሔ የሚያገኙት ከዱላ መስሏቸው በዚያ አጥፊ መንገድ እየዳከሩ ናቸው፡፡ ምንም ነገር በምንም ዓይነት መንገድ ጠይቅ መልሳቸው አንድና አንድ ነው – ዱላ፡፡ ምናልባትም “ወደ ሒልተን የሚወስደው መንገድ የትኛው ነው?” ብለህ ብትጠይቃቸው የምትለውን ለመስማት ዝግጁ ስላልሆኑና ለጥያቄዎች ሁሉ መልሳቸው አንድ ዓይነት በመሆኑ በሽመል ሊዠልጡህ ይችላሉ፡፡ ዕብደትና በሥልጣን ጥም እየቃዡ በሰቀቀን መኖር ይህን ይመስላል እንግዲህ፡፡ ከትዳር አጋሮቻቸውና ከቤተሰባቸው ጋር እንዴት እንደሚኖሩ ባየኋቸው፡፡
እሳትን ለማጥፋት ውኃ መጠቀም ሲገባቸው ቤንዚን እያርከፈከፉ ናቸው፡፡ ያላስቆጡትና የማያስቆጡትም የለም፡፡ ራሳቸው ተደናብረው ሌላውንና በዝምታ – አላህና እግዜሩ እስኪወርዱ ወይ እስኪፈርዱ – በአርምሞ የሚኖረውን ዜጋ ሁሉ ልክ እንደ አዲስ እረኛ እያስደነበሩ የሌት እንቅልፍና የቀን ዕረፍት እያሳጡት ይገኛሉ – የኢትዮጵያ አይስሎች፡፡ ጭካኔያቸው ለከት አጥቷል፡፡ “እኛ ከሥልጣንና ከሀብት ከምንወገድ 94 ሚሊዮኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ (እንደነሱ አጠራር ሕዝቦች) ገደል ይግባ” ብለው ቆርጠዋል፡፡ የማያደርጉት ነገር የለም፡፡ እንዲያውም ምርጫውን ተመርኩዞ ሊነሱ በሚችሉ የተቃውሞ ሠልፎች በአስለቃሽ ጢስ ሰበብ ገዳይና ዐይን አሣዋሪ ወይም አደንዛዥና አሳባጅ ኬሚካል እንዳይጠቀሙ ሥጋት አለ፡፡ እነዚህ አይስሎች ከምድር ህግም ከሰማይ ህግም ከሞራል ዕሤቶችም በፍጹም ያፈነገጡ በመሆናቸው የፈለጉትን ቢያደርጉና እያደረጉም ባሉትም ጭምር ጠያቂ የላቸውም፡፡ ነፍሰ ጡር ሴት መደብደብና ጽንስ ማስጨንገፍ፣ ሰላማዊ ዜጋን ከብቦ በፌዴራል መሰባበርና ከሰውነት ውጪ ማድረግ፣ሰላማዊ የፖለቲካ ተፎካካሪንና ነፃ ጋዜጠኞችን በጅምላ ማሰርና መደብደብ … ምን ትርጉም ሊሰጠው ይችላል? ለመሆኑ እነዚህ አይስሎች ከየት መጡብን? ኃጢያታችን ምን የከፋ ቢሆን ነው ፈጣሪ እነዚህን ዐውሬዎች ወደኛ የላከብን? ኧረ ግዴላችሁም እግዚኦ እንበል፡፡ በየሃይማኖታችን ለየፈጣሪዎቻችን እንጩህ እንጂ፡፡ የምን ዝምታ ነው፡፡(የፋናውን የወያኔ ቡችላ የብሩክን ውሸት በኢሣት ሰምቼ በሣቅ ፈነዳሁ፡፡ ይህን ታሪካዊ በሣቅ የመፈንዳት ሂደት እባካችሁን ለሱው ለእርጉሙ ማለትም ለብሩክ ንገሩልኝ፡፡ አሁን እሱ ጋዜጠኛ ነው? ድንቄም ጋዜጠኛ! እንዴ፣ እንዴት ትንሽ አያፍርም፡፡ ለነገሩ ወያኔ ቤት እኮ ሀፍረትና ይሉኝታ አይታወቁም፡፡) ወይ ነዶ! በስንቱ እንድንቃጠል ፈቃድህ ሆነ የእስራኤል አምላክ! ለማንኛውም ከነጋበት ጅብና ከፈሪ ዱላ እኛንም፣ ሀገራችንንም ፈጣሪ ይጠብቀን፡፡ በአሁኑ ወቅት በወያኔ እየተሰቃዩ የሚገኙ ወገኖቻችንን ጽናቱን ይስጥልን፡፡ “ወያኔ በሰላም ሥልጣን ይለቃል” ከሚል የዘመናት ሞኝነት(ጅልነት ልበለው ይሆን?) ነፃ የወጣን ያድርገን፡፡ሁሉን ቢያወሩት ሆድ ባዶ ይቀራልና ለዛሬ እዚህ ላይ ይብቃኝ፡፡ አሪቬዴርቺ!
የእነዚህ ነገሮች ምሥክር የሆነው “አዎ! በቶሎ እመጣለሁ” ይላል፡፡
አሜን፣ ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና!
የጌታ የኢየሱስ ጸጋ ከሁላችሁ ጋር ይሁን፤ አሜን፡፡ (ራዕይ፣ 20-21)
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/38844#sthash.FoV7Z7tO.dpuf

No comments:

Post a Comment