Monday, February 16, 2015

እኔም ቀንቶኝ ወይዘሪት ነፃነትን የምስመው መቼ ይሆን?

ነፃነት ዘለቀ አንዳንድ  ሰዎች በዕድል ያምናሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ በሥራ ብቻ  የሚያምኑ አሉ፡፡ ጥቂቶች በሥራም በዕድልም ያምናሉ፡፡ የኔ ምድብ ከነዚህኞቹ ነው፡፡ አንድ ሰው መቶ ዓመትም ቢለፋና ቢደክም በጥረቱ ላይ መጠነኛ ዕድል ካልታከለበት ሊሣካለት የመቻሉ አጋጣሚ አናሳ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ እንደኔ አስተሳሰብና እምነት ዕድል ያልተጨመረበት ጥረት ሥምረቱ የልብ የሚያደርስ አይሆንም፡፡ የአንዱ ወይ የሌላው ባሪያ መሆን እንደማይገባ ግን እረዳለሁ፡፡ ለአንድ ዓላማ ሥኬት መልፋትና መድከም ይገባል፡፡ ዕድል ሲሰምር የልፋት ውጤት ያማረ ይሆናል፡፡ እዚህ ላይ ግን በተለያዩ አቋራጭ መንገዶችና በሙስና የሚገኝን ሀብት በዕድል ወይም በጥረት እንደተገኘ መቁጠር አይቻልም፡፡
በዘረኝነት ደዌ የተበከለ አንድ ወያኔ ከሙገር ስሚንቶ ፋብሪካ ሊመለስም ላይመለስም በሚችል ርካሽ ዋጋ የፋብሪከውን ምርት እንዲወስድና አየር በአየር በውድ ዋጋ ሸጦ በአንድ ጀምበር ከመናጢ ድሃነት ወደ ሚሊዮኔርነት እንዲለወጥ ቢደረግ በዚህ ሂደት ሥራም ዕድልም የሉምና ይህ ዓይነቱ ወያኔያዊም እንበለው ደርጋዊ አሠራር ከሥሌታችን ውጪ ነው፡፡ ሥራ የምንለው በወያኔው የመስፍን ኢንጂነሪንግ አሻጥር ለኪሣራ እንደተዳረገው ማሩ ተፈራ ወይም በወያኔው አምባሰል ሻጥር ተሠርቶበት እንዲከስርና ከሀገርም እንዲሰደድ እንደተደረገው ገብረየስ ቤኛ(አማልጋሜትድ) ለዘመናት ለፍተው ሀገርንና ወገንን የሚጠቅም ጥሪት የማፍራት ሂደታዊ እንቅስቃሴን ነው፡፡ ዕድል የምንለው ለምሣሌ እኩል የጥራት ደረጃ ያላቸው ምርቶች ወደ ገበያው ገብተው በማስታወቂያ ልዩነት ወይም በሌላ አሣማኝ ምክንያት የአንዱ ሲሸጥና አምራቾች ሲያድጉ የሌላኛው ወገን ግን ዕድል ሳትሰምርለት ቀርታ ከገበያው ለመውጣት ሲገደድ ነው፡፡ ሥራና ዕድል ውስጥ መመቀኛኘትና በሻጥርና በዘረኝነት መጠላለፍ የሉም፡፡ ባሣለፍኳት የእሁድ ለሰኞ አጥቢያ ሌሊት (የካቲት 1/2007) የአፍሪካ ኳስ የዋንጫ ጨዋታ ይካሄድ ነበር፡፡ እንደጥንቱ በጋለ ስሜትና መቁነጥነጥ ባይሆንም ለመዝናኛነት ያህል ይህን ጨዋታ ከሁለት ልጆቼ ጋር መከታተል ያዝኩ፡፡ ሰዓቱ እኩለ ሌሊት ገደማ በመሆኑ ለኢትዮጵያውያን አስቸጋሪ ነው – በተለይ ለእንደኔ ዓይነቱ እንቅልፋም፡፡ አርሰናል ቢሆን ተጎልቶ የሚያድረው አንደኛው ልጄ የመጀመሪያውን ግማሽ – እያንጎላጀ – እንደምንም ጨርሶ ወደመኝታው ሄደ፡፡ ከፊልም ውጪ ለስፖርት በተለይም ለእግር ኳስ ደንታ የሌለው ሌላው ወንድሙ ሶፋ ላይ ተጋድሞ “እየተመለከተ” ቢቆይም ለአስተያየቶቼ የአጸፋ መልስ ማጣት ምሥጋና ይግባውና እርሱም አካሉን አጠገቤ አስቀምጦልኝ በሞት ታናሽ ወንድም መሸነፉን ያስተዋልኩትና ብቻየን እንደቀረሁ ያጤንኩት ሁለተኛው አጋማሽ ከመጀመሩ በፊት ነበር፡፡ የአፍሪካ ዋንጫ እንደዱሮው የተሟሟቀ አልመስልህ አለኝ፡፡ አንደኛ የሕዝቡ በተለይም የወጣቱ ስሜት በአውሮፓ እግር ኳስ ተማርኮ መፈጠሩን እንኳን በማያውቁለት የአርሴና ማንቼ ፍቅር በመለከፉ፣ ሁለተኛ የአብዛኛው ሕዝብ ኑሮ ከእጅ ወደ አፍም መሆን አቅቶት በችጋር እየተንጠራወዘ እንዲኖር በመገደዱ ለዚህ ዓይነቱ ቅንጦት ቦታ የሌለው በመሆኑና ሦስተኛ በሌሎች ለጊዜው ያልተከሰቱልኝ ምክንያቶች የተነሣ የአፍሪካ የእግር ኳስ ጨዋታዎችን ያን ያህል ክብደት ይሰጣቸዋል የሚል ግምት የለኝም፡፡ እኔ ለምሣሌ ይህን የመጨረሻውን ጨምሮ ግፋ ቢል አራት ጨዋታዎችን ብመለከት ነው – እንዲያውም ሦስት ናቸው፡፡ ይህንንም ሆን ብዬ ሣይሆን በአጋጣሚ ነው፡፡ ወያኔዎች – ዞረን ዞረን መቼም የብዙዎቻችን የነገር ማጠንጠኛ/አዝማች ወያኔ ነው – ወያኔዎች መላ ሰውነታችንን ቀስፈው ስለያዙት እነሱ በጫኑብን የኑሮ ቀምበርና የግፍ አገዛዝ ከምብከንከን አልፈን ለዚህ ዓይነቱ ቅንጦት ብዙዎቻችን አልታደልንም፡፡ በትናንቱ ጨዋታ እንደእግር ኳስ ተንታኝ ሣይሆን – ሙያየም ዝንባሌየም ባለመሆኑ – እንደተራ ታዛቢ አንዳንድ ነገሮችን በትዝብት መልክ ባቀርባቸው እኛንም ጎላ ባለ ሁኔታ ስለሚያካትተው የአፍሪካውያን ባሕርይ መጠነኛ ግንዛቤ ያስጨብጣል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እናም አፍሪካ ከመሬቱ ይሁን ከሰዎቹ ብዙ ሊባልልን የሚገባን መሆናችንን የተረዳሁበትን ይህን ጨዋታ ባጭሩ ልቃኝ፡፡ ጨዋታው ተጀመረ፡፡ ተጋጣሚዎቹ (የዱሮዋ አይቬሪኮስት) የአሁኗ ኮትዲቩዋርና (የዱሮዋ ጎልድኮስት) የአሁኗ ጋና ናቸው፡፡ (ስምን መለዋወጥ የአፍሪካ ፋሽን የሆነ ይመስላል፡፡) ሁለቱም ጥሩ እንቅስቃሴ ቢያደርጉም፣ ሁለቱም የተወሰኑ የግብ ሙከራዎችን ቢያሳዩም ዕድል የአንዳቸውንም በር ሳታንኳኳ መደበኛ ሰዓቱ ተጠናቀቀ፡፡ እንደብዙዎቻችን ግምት(እኔ ራሴንም በገማችነት ማስገባቴን ያጤኗል!) ወደተጨማሪ ሰዓት ገቡ፡፡ ጨዋታው እልህ አስጨራሽና የዓለምን ዋንጫ የሚያስንቅ ፉክክር ነበረው፡፡ ስቴዲዮሙ ግን ያው የአፍሪካ መገለጫ የሆነው  – የአስተናጋጅ ሀገር ቡድን ለመጨረሻው የዋንጫ ጨዋታ ካላለፈ ጭር የማለት ነገር ይታይበታል፡፡ በአውሮፓና አሜሪካ ከወራትና ሣምንታት በፊት ተሸጦ የሚያልቅ ትኬትና ወንበር በኢኳቴሪያል ጊኒ ግን ሊያውም በመዝጊያው የዋንጫ ጨዋታ ብዙ ባዶ መቀመጫዎች ነበሩ፡፡ ሌሎች ዓለማት ምን እንደሚታዘቡን እንጃልን፡፡ የዚህ ነገር መንስኤው አንድም እንደጠቀስኩት የራስን ቡድን ከማጣት የሚመነጭ ኩርፊያ ነው ወይም ድህነትና እርሱ የሚፈጥረው ለነገሮች ግዴለሽ የመሆን ጠባይ ነው፡፡ በዋናውም ሆነ በተጨማሪው ሰዓት አንዳንድ ተጫዋቾች በሰላማዊ የወዳጅነት የእግር ኳስ ግጥሚያ ላይ ሣይሆን ሀገራቸውን ወክለው የቀደምት ኢትዮጵያውያንን ጀግንነት በሚያስታውሱን ጉንደትና ዐድዋን በመሰሉ ዐውደ ግምባሮች ላይ ለጨበጣ ውጊያ የተሠለፉ ነበር የሚመስሉት፡፡ እግር ኳስን ከሰላማዊ “ጦርነት” አዘልለው ከተመለከቱት እጅግ አደገኛ ነው፡፡ ብዙ ክስተቶችን ከአፍሪካም ከላቲን አሜሪካም ከአውሮፓም መጥቀስ ይቻላል፡፡ ኢኳዶርና ኢልሣልቫዶር ጦርነት ውስጥ እስከመግባት አድርሷቸዋል ይባላል፤ በግብጽ በቅርቡ በ50 እና በ100 መሃል የሚቆጠሩ ዜጎች (74?) ስቴዲየም ውስጥ በተፈጠረ ግርግር አልቀዋል፡፡ አቅል የሣተ የድል ፍቅርና ናፍቆት ወደ ጥፋትና ውድመት ይመራል፡፡ ሰዎች የስፖርትን ዓላማ ዘንግተው ለምን ወደዚህ አስቀያሚ ሁኔታ እንደሚገቡ ግልጽ አይደለም፡፡ በሀገራችንም በገና ጨዋታ ወቅት በሩር ወይም በጥንግ  ተጀምሮ ወደዱላ ድብድብ እንደሚገባ ከልጅነት ገጠመኞቼ አስታውሳለሁ፡፡ “የየጁ ደብተራ ቅኔው ቢጎድልበት ቀረርቶ ጨመረበት” ማለት ይሄኔ ነው፡፡ ኧረ ጎረምሳውም “ለፍቅር ብተኛት ለጠብ አረገዘች!” ይላል፡፡ አዎ፣ አንዳንድ የፍቅርም ይሁኑ የሰላማዊ ወዳጅነት ጅማሮዎች መጨረሻቸው ጠብና አምባጓሮ ከዚያም ባለፈ የቀደመ ወደ ዘብጥያ ወይ ወደ ጫካ የተቀደመ ደግሞ ወደሚቀርበው የመቃብር ሥፍራ የሚሄድበት አስቀያሚ ገጽታ ካልተወገደ በሰላምና በጦርነት መካከል ያለው ልዩነት እንዳደናገረን ይኖራል፡፡ ትልቅ የማስተዋል ጉድለት ይታያል፡፡ ከአውሮፓውያኑ ተጫዋቾች በሚለይ መንገድ አንዳንድ ተጫዋቾች ያሳዩት የነበረው የመጎሻሸም አሣፋሪ ምግባር ሳይጠቀስ የሚታለፍ አይደለም፡፡ ዳኛው ሆደሰፊ ባይሆን ከተሰጡት ብዙ የማይባሉ ቢጫ ካርዶች የበለጠ  በዛ ያለ ቁጥር ካርድ ልናይ በቻልን ነበር፡፡ ጠበንጃ አልያዙም እንጂ ለመደበኛ ውጊያ ወደ ኳስ ሜዳ የገቡ የሚመስሉ ተጫዋቾች ነበሩ፡፡ አንዱ እንዲያውም አንዱን ተጋጣሚ በቴስታ አፍልሶታል፤  ከተቃራኒ ተጫዋቹ የመልስ ምቱን ለመቀበልና ሒሳቡን ለማወራረድ ሌላ የጊዜ ቀጠሮ ባያስፈልገውም፡፡ አንደኛው ወገን በግድ ማሸነፍ እንዳለበት የሚያውቁ አይመስሉም፡፡ ማሸነፍና መሸነፍ የማይነጣጠሉ መሆናቸውን፣ የማሸነፍን የድል ስሜትና የመሸነፍን መሪር ጽዋ ደግሞ እንዳመጣጡ ማስተናገድ ያለና የነበሩ መሆኑን የዘነጉ ተጫዋቾች ነበሩ፡፡ አውሮፓዊ ልምድ ያላቸው የመሰሉኝ አንዳንድ ተጫዋቾች ተቃራኒያቸውን በማቀፍና ተፈጥሯዊ ፈገግታ በማሳየት የፌይር ፕሌይን ደምብ ሲያከብሩ በተቃራኒው እንደወያኔ ሰብኣዊ ዕድገታቸውን የጨረሱ የማይመስሉና እንደፊጋ በሬ ያገኙትን የተቃራኒ ጎራ ተጫዋች ሁሉ በምናባዊ ቀንዳቸው ደስቀው መሬት ሊያስግጡ የሚቋምጡም ነበሩ – እንደ አፍሪካዊነት ሁላችንንም ያሣፍራል፡፡ አውሮፓውያኑ ተጫዋቾች በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቢገኙ እንዲህ ይሆኑ ነበርን? ብዬ አነጻጽር ነበር፡፡ አይመስለኝም፡፡ እነሱ ሳይሻሉ አይቀሩም፡፡ ቢናደዱና ቢያለቅሱም ወደዐውሬነት ጠባይ እስከዚህን ወርደው ግን ሁከትና ግርግር የሚፈጥሩ አይመስለኝም፡፡ ልዩነታችንን በሚገባ ተገነዘብኩ፡፡ ይህ ልየነታችን በመሪዎቻችን የስብዕና ማንነትና ዐውሬያዊ ተፈጥሮም በጉልህ የሚታይ ነው፡፡ የመላዋን አፍሪካ አምባገነን መሪዎች ለምሳሌም ሙጋቤንና ሙሴቪኒን ብናይ በጠባያቸው ከዐዞና ጉማሬ የሚለዩ አይደሉም፡፡ የአንድን ሀገር ሕዝብ አፍኖና ረግጦ  እንደብረትም ቀጥቅጦ ከ30 እና 40 ዓመታት በላይ መግዛት የዐውሬነት እንጂ የሰውነት ባሕርይ አይደለም፡፡ በዕድሜ ይፍታህ ዐውሬነት የተቀፈደዱ ምሥኪን ፍጡራን ናቸው፡፡ ለነሱም ማዘን ይገባል፡፡ ልዩነታችንን ከመገንዘቤም የተነሣ ብዙ ተናደድኩ፡፡ ጨዋታው ሊያልቅ የደቂቃዎችን ዕድሜ እየተጠባበቀ ነው፡፡ ከማለቁ በፊት ግን የብዙ ተጫዋቾችን ጉልበትና የኛን የተመልካቾችን ትግስት ጨርሷል፡፡ በ90 ደቂቃው መደበኛ ሰዓት አልተሸናነፉም፡፡ በጭማሪው የ30 ደቂቃ ጊዜም እንዲሁ አልተሸናነፉም፡፡ ምንም ግብ በማንኛቸውም ቡድን ደጅ ዝር አላለም፡፡ ግብ ጠባቂዎቹም ጩልሌ ናቸው – ብዙም የሚፈታተናቸው ሙከራ ባይገጥማቸውም፡፡ እንደተፈራው የጨዋታው የመጨረሻ ዕጣ ወደ መለያው የሪጎሪ ምት ተዛወረ፡፡ ተጫዋቾች እፎይ አሉ፤ የነሱን ተሰናስኖኣዊ(የቡድን) ኃላፊነት አጠናቀቁ፡፡ አሁን ጭነቱ በሁለት ሰዎች ላይ ወደቀ – መቺውና ግብ ጠባቂው – መሳትና መረብን ማስደፈር የለባቸውም፤ የሞት የሽረት ጉዳይ ነው፡፡ ሁሉም ምጥ ላይ ነው፡፡ ትንፋሽ የሚያጥርበት እባብ አንገት ላይ ቢጠመጠም እንደእስካርፍ የሚቆጠርበት የውጥረት ሰዓት፡፡ … እንዳጋጣሚ ከመነሻው ጀምሮ ራሴን ያገኘሁት የኮትዲቯር ደጋፊ ሆኜ ነበር፡፡ ምክንያቱን በውል አላውቅም፤ ምናልባት ግን ጋናዎች የኛን ተጫዎቾች አንድ ወቅት ስላንገላቱብን ያ በ“ሰብኮንሼሴ” ውስጥ ተቀርቅሮ አስቸግሮኝ ይሆናል፤ ስህተተኛነቴ ግን ለኔም ግልጽ ነው፡፡ ቂመኝነትና አድልዖ እንኳንስ በእግር ኳስ በፖለቲካም ሊኖር እንደማይገባ አምናለሁ፡፡ ግን ሰው ሰው ነውና ምን ይደረግ? ብዙውን ጊዜ ስሜታዊነት ያጠቃናልና ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ አስደናቂ ጅማሮ፡፡ ኮትዲቯሮች በሚያሳዝን ሁኔታ የመጀመሪያዎቹን ሁለት ኳሶች አበላሹ፡፡ አንዱ ተያዘ – ሌላው ውድማ በላው – ተሳተ፡፡ ጋኖች (ጋናዎች) ድላቸውን ከወዲሁ ማጣጣም ጀመሩ፤ ስለማሸነፋቸው እንኳን እነሱ እና ተመልካቾችም እርግጠኞች የሆንን መስለናል፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎች ብዙ ተመልካቾችና የማንኛውም ወገን ደጋፊዎች ፈረንጆች “Do not count your chickens before they are hatched.”የሚሉትን የንግግር ዘይቤ ያስታወስን አይመስለኝም – ጋና እንደምታሸንፍ ያመንን፣ አምነንም ተስፋ የቆረጥን ብዙ እንደሆን እገምታለሁ፡፡ ኳስ ድቡልቡሏ ግን ተዓምር መሥራቷን ቀጠለች፡፡ ኮትዲቯሮች በተጓዙበት መንገድ ተጉዘው ጋናዎች በተመሣሣይ ሁኔታ  ሁለት ተከታታይ ኳሶችን አበላሹ፡፡ ዕድል ፊቷን ነሳቻቸውና የመሸነፍ/ማሸነፍ ዕጣቸውን ለሁለቱም በእኩል ሚዛን አስቀመጠችላቸው፡፡ ጭንቀት ወረደ፤ ጭንቀት ጨመረ፡፡ በዚህ የእኩልነት ጉዞ አሥር፣ አሥር ኳሶች ለየግብ ጠባቂዎች እቅፍ ተላኩ – እስካሁን የተያዘ ወይ የባከነ ኳስ የለም፡፡ ግብ ጠባቂዎቹ፣ እያለፏቸው መረቦቻቸውን የሚያነጉዱትን ኳሶች በዐይናቸው ቂጥ እያዩ ብቻ ከመገልመጥና ከመሸኘት በስተቀር ምንም ነገር ማድረግ አልቻሉም፡፡ የሁሉም ሙቀት እየጨመረ ሄደ፡፡ አሥራ አንደኛው ኳስ ለበረኞች ተመደበ፡፡ የኮትዲቯሩ ገባ፡፡ የጋናው መታ፡፡ በሚገርም ሁኔታ ያቺን ኳስ የግብ አቅጣጫዋን አጨናገፈባትና አወጣት፡፡ ስቴዲየሙ ተናጋ፡፡ ልቅሶውና ሙሾው፣ ዳንኪራውና የደስታ ሲቃው ተጀመረ፡፡ አንድ ነገር ግን ይቀራል – የኮትዲቯሩ ቦርተሌ መምታትና ልኩ መታወቅ አለበት፡፡ የጋናው ኪፐር ገባ፡፡ የኮትዲቯሪ ጊላ ኳሷን ወደግብ ሊጠልዝ አመቻችቶ አስቀመጠ፡፡ ሙቀት ጨመረ፤ ሙቀት ቀነሰ፡፡ ብዙም የተጨነቀ ሳይመስል በጨዋታው ጉዳት የደረሰበት መሆኑን በተደጋጋሚ ሲገልጥ የነበረው የኮትዲቯሩ ግብ ጠባቂ መታ፡፡ ዶላት፤ በአስተማማኝ ሁኔታ ከመረቡ ጋር አዋደዳት፡፡ ዓለም አለፈች፡፡ ይህ አጋጣሚ ነው ብዕሬን ለማንሳት የወዲያው ምክንያት የሆነኝ፡፡ ከመሬቱ ይሁን ከሰው አፍሪካውያን ሀዘንንም ደስታንም በቅጡ መያዝ የምንችል አልመስልህ አለኝ፡፡ የስታዲዮሙ  ሁኔታም ዱሮ የማውቀውን የፍስሀ በላይ ይማምን “አልቃሽና ዘፋኛ” ቲያትር አስታወሰኝ፡፡ በዚህ ልቅሶ ነው፤ በዚያም ልቅሶ ነው – የዚህና የዚያ የልቅሶ መንስኤ ግን የተለያዬ ነው፤ አንዱ የደስታ ሌላኛው የሀዘን፡፡ ‹አየው› የሚባለው የጋናው ተጫዋችማ እናቱም ቢሞቱ (በሕይወት ካሉ) እንዲህ የሚያዝንና የሚያለቅስም አይመስለኝም፡፡ አንዷ ሴት አታልቅሽ ቢሏት “አታልቅሽ ነው እሚያስለቅሰኝ” እንዳለችው ነው የሆነው ነገሩ ሁሉ፡፡ ሲያባብሉት እየባሰበት ስቴዲየሙን በሞላ በዕንባ አነፋረቀው፡፡ የአሸናፊውም ወገን የድል ደስታ ቅጥ አጣ፤ መተዛዘን ጠፋ፡፡ ሁለቱም በፉክክር የሚያዝኑና የሚደሰቱ ይመስላል – አንዱ ፈንጠዝያውን ወይም ልቅሶውን ሲጨምር ሌላውም ለመጨመር የተማማሉ መሰሉ፡፡ ለገላጋይ አስቸገሩ፡፡ ሁለቱም አስጠሉኝ፡፡ ሀዘንና ደስታ ብርቁ የሚሆንበት ሰው ደስ አይለኝም፡፡ ወደኛ ቢመጡና ዐርባ ዓመት ሙሉ እዝን በማይመጣበት ሀዘን መኮራመታችንን ቢያዩ ምን ሊሉ ነው? ሆ! ደሞም ለኳስ፡፡ እናቱ ወንዝ የወረደችበትና የሞተችበት እኩል ያለቅሳሉ አሉ፡፡ ሁለቱም ተሳስተዋል፡፡ የሆነው ቢሆን በዕድልም እንበለው በሥራ ኮትዲቯሮች ቀንቷቸው የቋመጡላትን ዋንጫ ስመዋል፡፡ የደስታቸው አገላለጽ በተወሰነ ደረጃ ድንበሩን ስቶ የተቀናቃኝ ወገንን ወደ ማብሸቁ በመጠጋቱ አናደዱኝ እንጂ ድሉ ይገባቸዋል – የልፋታቸው ውጤት ነው፤ ሁለቱም ለፍተዋል ለነገሩ፡፡ ያሸነፉት ወገኖች በለስ ቀንቷቸው ዋንጫይቱን ሳሙ፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያንስ የሀገራችንን ነፃነት እንደነሱ ዕቅፍ አድርገን የምንስማት መቼ ይሆን? መቼ ነው ሀገራችን ውስጥ ለሁሉም ዜጋ የሚሆን የነፃነት ቀንዲል የሚበራውና ከኋሊት ጉዞ ተላቅቀን በዘመናዊ አመለካከትና አስተሳሰብ  በተቃኘ ቁሣዊና መንፈሣዊ ሥልጣኔ የምንመራው? መቼ ነው ከጎታች የዘረኝነትና የሃይማኖት ክፍፍል ተፅዕኖ ተገላግለን በአንዲት ሀገር ዜግነት፣ በአንድ ሉዓላዊ መንግሥት፣ በአንድ ብሔራዊ ስሜት … በነፃነት የምንኖረው? መቼ ነው የተበታተነው ሕዝባችን ከነዕውቀቱና ልምዱ ወደ ሀገር ቤት ተመልሶ ሀገራችን በአዲስ መንፈስ የምትገነባው? ኧረ መቼ ነው ስደትና እንግልት፣ ረሀብና በሽታ፣ ማይምነትና ድንቁርና፣ አረመኔነትና ሆዳምነት፣ ሙስናና ልበደንዳናነት… ከኢትዮጵያ ራስ የሚወርዱት? ዜጎች “መብታችን ይከበር” ብለው በጮኹ በፌዴራልና በሥውር የደኅንነት ታጣቂዎች ባልተወለደ አንጀት መቀጥቀጣቸው የሚያቆመው መቼ ነው? ለገዢዎች የማያጎበድዱና በሕግ የሚመሩ የመንግሥት ተቋማት የሚኖሩን መቼ ነው? መቼ ነው በማስፈራራትና በማሽቆጥቆጥ ከሚገዙን የቀን ጅቦች የምንገላገለው? ህግ አውጪ፣ ህግ ተርጓሚና ህግ አስፈጻሚ አካላት የሚፋቱትና አንዳቸው የአንዳቸውን ዕንባ ሣይጠብቁ የሕዝብን አደራ የሚወጡት መቼ ነው? እነቃሊቲና ዝዋይ በንጹሓን የኅሊና  እሥረኞች መጥለቅለቃቸው የሚያቆመው መቼ ነው? …  “ደግ ተመኝ ደግ እንድታገኝ ይባላል”ና በበኩሌ በያለንበት በሚደርስብን መከራና ግፍ ብዙ እየተማርን ስለምንገኝ የዚህ ሁሉ ግፍና መከራ ጽዋ የሞላና በቅርብም ነፃነታችንን የምንጎናጸፍ ይመስለኛል፡፡ ሁሉም ነገር የሚያምረው በነፃነት ሲሆን ነው፡፡ እግር ኳሱም፣ ልማቱም፣ ዕድገቱም፣ ምኑም ምናምኑም አእምሮህን ደስ የሚያሰኘው ነፃነት ስትኖር ነው፡፡ ካለነፃነት ሆድህ በቁርጥና በጮማ እንዲሁም በውስኪ ቢገሰር እንኳን የኅሊና እርካታ ከቶውን ሊኖርህ አይችልም፤ የመንፈስ ርሀብ ያንገላታሃል፤ የወገኖችህም ሰቆቃ ያሰቃይሃል፡፡ ለዚህም ነው ብዙዎቻችን በሀገር ቤት የምንኖር ዜጎች ምንም እንኳን አካላዊ የምግብ ርሀብ ባያሰጋንም በነፃነት ዕጦት ምክንያት ሌት ከቀን እዬዬ እያልን የምንኖረው፡፡ ከኢትዮጵያ የነፃነት ብሥራት ቀጥለው እንደሚመጡ ለሚጠበቁት ቀጣዮቹ የዓለምና የአፍሪካ ዋንጫዎች በሰላም ያድርሰን፡፡ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/38840#sthash.QBBEceXG.dpuf

No comments:

Post a Comment