Tuesday, September 29, 2015

ኑሮ በመፈክር (ጌቱ ኃይሉ)

ጌቱ ኃይሉ
አቶ ዠ 57 አመታቸው ነው። መተዳደሪያ አላቸው። እንዴት ያለ ሙያ!! ባሥራ ሰባት አመታቸው የጀመሩት። አርባ አመት ሙሉ ያለማቋረጥ እየሰሩ ያሉት። ሰዉ ከሥራው በመንግሥት ለውጥ፣ በሰበብ ባስባቡ ሲባረር እሳቸው ሥራ አላጡም። ሥራቸው? መፈክር አድምቆ መጻፍ።
መጀመሪያ በሁለት ቃላት ጀመሩ። በነጻ “ኢትዮጵያ ትቅደም!” ብለው አድምቀው ጻፉ። ከዚያ እየተከፈላቸው ደግሞ “ከቆራጡ መሪ ጋር ወደፊት !!” ብለው ቀጠሉ። ሰውየው ብቻቸውን ሲቀሩ። ወደ መጨረሻው ግድም ደግሞ “አብዮታዊት እናት ሃገር ወይም ሞት” ብለው ደጋግመው አድምቀው ጻፉ። “አብዮታዊት እናት ሃገር ወይም ዝምባብዌ!” ብለው አላፌዙም።

አቶ ዠ ፕሮፌሽናል ናቸው። የከፈለ ያጽፋቸዋል። ጊዜው እየረዘመ ሲሄድ መፈክሮቹም መርዘም ጀመሩ። አንድ ገጽ የሚሆን መፈክር ጻፍ ሲባሉ እንኳን “እሺ፣ ሂሳቡ ይሄ ነው።” ብለው ቀጠሉበት።
“ከልማታዊው መንግስታችን ጋር በመተባበር ድህነትን ታሪክ ለማድረግ የየበኩላችንን ድርሻ በቅንነት እንወጣ” ብለህ ጻፍ ሲባሉ አሳምረው ጻፉ። “የቅንድባችንን ጸጉር በማሳደግም አስተዋይነታችንን እናጎልብት !!” ብለው አላፌዙም።
“የሚሰጠንን የአቅም ግንባታ እና የተሃድሶ ስልጠና በማጠናቀቅ ለሃገራችን የህዳሴ ጉዞ የበኩላችንን አስተዋጽኦ እናበረክታለን !!” ብለህ ጻፍ ሲባሉም “እሺ!” እንጂ “በሥልጠናው ወቅት በሚሰጠን የውሎ አበል ግድቡ አቅራቢያ ያለች የገጠር መንደር ሄደን እያጨበጨብን እንጨምሳለን !!” ብለው አላፌዙም።
“ኢትዮጵያ ካሊፎርኒያና አውስትራልያ ተመሳሳይ ናቸው!!” ብለው መፈክር ለመጻፍ በራሳቸው አነሳሽነት ከጀሉ። “ምክንያቱስ?” ሲባሉ “ሦስቱም ሀገሮች ድርቅን ምንም ማድረግ አልቻሉምና !!” ብለው ማፌዝ ግን አልከጀሉም። ያ ፌዝ “copyrighted” ነውና!
“እኔ የምለው? እንዴት ነው ይኸ ነገር? ‘ሙያ በልብ ነው’ የሚባለው ያባቶቻችን ብሂል ገደል ገባ እንዴ? መፈክር ብቻ ሆነ እኮ ነገራችን። አርባ አመት ሙሉ መፈክር። አርባ አመት ሙሉ ፉከራ! አንድ ነገር ሳንሰራ! አይ የኛ ነገር!” ጓደኛቸው አቶ ጠ ጠየቃቸው።
“ዝም በል አንተ! መተዳደሪያዬን እንዳታሳጣኝ…” መለሱ አቶ ዠ።
እባክዎን ሳያስፈቅዱ ላለመቅዳት መልካም ፈቃድዎ ይሁን።

No comments:

Post a Comment