Wednesday, September 9, 2015

የዞን9 ጦማርያን ጉዳይ በድጋሚ ለመስከረም 27 ተቀጠረ።

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለዛሬ በተደጋጋሚ የተላለፈው የብይን ጥበቃ በድጋሚ ዳኞች አልተሟሉም በሚል ሰበብ ለ37ተኛ ጊዜ ተቀጥሯል።
በዳኞች አለመሟላት የተነሳ ችሎቱን ማስቻል አልችልም ብለው በቢሮ ተከሳሾችን እና ጠበቆችን የጠሩት ዳኛ ዘሪሁን ብይኑ ቢሰራም ለማሳወቅ ሁሉም ዳኞች መገኘት ስላለባቸው ለመስከረም 27 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥተናል ብለዋል ።
ተለዋጭ ቀጠሮ ተከሳሾችን ቤተሰቦችን እና ውሳኔውን ሲጠብቁ የነበሩ ብዙ አጋሮችን በከፍተኛ ደረጃ ያስከፋ ነበር ።

ከአንድ ወር በኃላ በመደበኛው የፍርድ ቤት መከፈቻ የተቀጠረው ችሎት ተከሳሾች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ ይሰናበቱ ወይስ ይከላከሉ የሚለውን ውሳኔ ያነባል ተብሎ ይጠበቃል።
የዞን9 ማስታወሻ
በአሳፋሪው የፍትህ ስርአትና በስራ አስፈፃሚው በሚዘወሩት ዳኞች እንደተከሳሽም ሆነ እንደአገር ማፈራችንን እያሳወቅን ይህ በውጤታማ እና ሰላማዊ ወጣቶች ህይወት ላይ መቀለድ፣ በታሪክም ሆነ በወደፊትዋ ፍትሃዊ ኢትዮጲያ ፊት የዳኞችን አንገት የሚያስደፋ ተከሳሾችን ደሞ የሚያኮራ ተግባር ሆኖ እንደሚታወስ በእርግጠኝነት እንናገራለን።
የዞን9 ጦማርያን በአምባገነን አገዛዝ የሚዘወሩ የጭቆና እጆች የማያንበረክኳቸው ኩሩ እና ነፃ ወጣቶች ናቸው።

No comments:

Post a Comment