Tuesday, November 26, 2013

ኢትዮጵያዊ ዋጋው ስንት ነው?

(ተመስገን ደሳለኝ)
የዚህ ፅሁፍ ማጠንጠኛ የፖለቲካ አመለካከትን መተቸት አይደለም፤ ከዋና ዋና ሀገራዊ አጀንዳዎች ወረድ ያሉ የጉልበታሙን ስርዓት የሥራ አፈፃፀሞችን ማብጠልጠልም አይደለም፤ የተቀናቃኝ ፓርቲዎችን ስንክሳር መንቀስም… አይደለም፡፡ ኢትዮጵያዊ (አል-ሀበሽ) መሆን ለፈተና፣ ለመከራ፣ ለሰቆቃ… መዳረጉ የወለደው ብሶት እንጂ፤ መመረር-ማምረር ነው፡፡ …ይህ የእኛ ዕጣ ፈንታ የሆነበትን ምስጢር መመርመር ነው፡፡
ሰሞኑን የሳውዲ አረቢያ መንግስት ታጣቂዎች እና በድጎማ የሚያድሩ የሀገሬው ተወላጆች በመሰረቱት የጥፋት ግንባር ጉልበታቸውን ገብረው፣ በላብ በወዛቸው በሚያድሩ ስደተኛ ወገኖቻችን ላይ የተፈፀመው አረመኔያዊ ወንጀል፣ የሁሉንም ኢትዮጵያዊ ልብ በከባድ ሀዘን የሰበረ፣ በቁጭት ያንገበገበ አሳዛኝ ፍፃሜ ሆኗል፡፡
ጭፍጨፋው ሃይማኖታዊው ጀሀድ ያወጀው አይደለም፤ ኢትዮጵያዊነት ባመጣው ዕዳ በድሃ ወንድም-እህቶቻችን ጀርባ ላይ ያረፈ ምህረት የለሽ ብትር እንጂ፡፡ …ይህ ግን ለምን ሆነ? ጥያቄ ነው፡፡
ርግጥ ነው፣ እንዲህ አይነቱ የእልቂት ነጋሪት መጎሰም ከጀመረ ዓመታት ነጉደዋል፤ መነሻ ሀገሩ ግን ሳውዲ አረቢያ ወይም ሊቢያ አይደለም፤ እዚሁ ኢትዮጵያችን ምድር ላይ እንጂ…
ዘ-ፍጥረት…
የየካቲቱ አብዮት ድንብዥታ (ሀንግኦቭር) ዛሬም ድረስ ዘመን ተጋሪዎቼን እያሳደደና እያሰደደ ይገኛል፡፡ ያኔ ያ ትውልድ ‹ኑ እንነሳ፣ ከተማውን እንውረር፤ አሮጌውንም ቅፅር በጩኸት አፍርሰን፣ አዲሱን እንፍጠር!› የሚል መለከት መንፋቱ ሙሉ ለሙሉ ስህተት ባይሆንም ‹የተጠሩ ብዙዎች፣ የተመረጡ ጥቂቶች› እንዲል መፅሀፉ፣ እፍኝ ለማይሞሉ ‹ምርጥ ወታደራዊ መኮንኖች› የተናጠል አሸናፊነት፣ የወል ተጠያቂ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ ስለምን ቢሉ? ስለተከሰተው ታሪክ ይሆናል መልሱ፡፡ በርግጥም ‹ፓርቲ› የሚባል የ‹ጦስ ዶሮ› ባነበረው ልዩነት በጥይት ደብድበው ሲያበቁ፣ አፈር ፈጭቶ፣ ውሃ ተራጭቶ ባደገበት መንደር እንደ መናኛ በየመንገዱ አስጥቶ ማዋል፣ ለግብዓተ መሬቱ የጥይት ዋጋ ማስከፈል፣ ወላጆችን እርም መከልከል… ከዚህ የከፋ ምን ሊያመጣ ኖሯል? …ከተኛበት አልጋ እያነቁ መስቀል፣ ከገሀነም በከፋው ቅጣት ‹ወፌ-ላላ› ገልብጦ ማሰቃየት፣ በአንድ ጉድጓድ ስልሳውን አነባብሮ መቅበር… ከዚህ ሌላ ምን ሊያስገኝ ኖሯል? …የሆነውም ይህ ነበር፡፡ እነሆም ያ ትውልድ የፀነሰው የተገነባውን መናድ፣ የተሰራውን ማፍረስ፣ በራስ ወገን ላይ መከራ ማዝነብን የሚመክረው የዘ-ፍጥረት መፅሀፍ ምዕራፍ እዚህ ጋ ነበረ የጀመረው፡፡
አዲስ ታሪክ አልተሰራም!
‹አዲስ ንጉስ እንጂ፣ ለውጥ መቼ መጣ!› እንዳለው ከያኒው፣ ታጋዮቹ በወታደሮቹ ቦታ ከተቀመጡ በኋላ የነበረው-እንደነበረው ነው የቀጠለው፤ ‹ባለሙያ› ገራፊዎች በአሸናፊዎቹ ከመተካታቸው በቀር፣ ማሰቃያ ጎሮኖቹ ዛሬም ወደ ሙዚየምነት አልተቀየሩም፣ መገረፊያው፣ መገልበጫው፣ መግደያው፣ መጋዣው… አሁንም የቀድሞውን ግልጋሎታቸውን እየሰጡ ነው፡፡ ማን ያውቃል? ነገም በዚሁ ይቀጥሉ ይሆናል፤ ለአጎራባች መንደሮች መቀጣጫ በሚል የጭካኔ ፈሊጥ፣ የአማፅያን ኮሽታ የተሰማበትን መንደር ሁሉ ዶግ አመድ ማድረግም፣ የጄነራሎቻችን የጦር ‹ጠበብ›ነት መገለጫ ሆኖ ቀጥሏል፤ በሀውዜን፣ አርባ ጉጉ፣ አርሲ፣ ሐረር፣ ጋምቤላ፣ አዋሳ፣ ኦጋዴን፣ ቀብሪ-ደሀር፣ ደገ-ሀቡር… የፈሰሰው የግፉአን ደም፣ የተከሰከሰው የንፁሀን አጥንት ታሪክ ነጋሪ ጥቁር ሀውልት መሆኑን ማን ይክዳል? ይህንን ሁሉ ምድራዊ ፍዳ፣ ዓለም እንደ ማንኛውም አሳዛኝ ዜና ሰማው እንጂ፣ ሰለባዎቹን ለመታደግ ያደረገው እዚህ ግባ የሚባል እንቅስቃሴ አልነበረም፤ በራስ መንግስት፣ በራስ ወገን መናቅ፣ ክብር መነፈግ፣ ለ‹ምርኮኛ ሕግ› ማደር… ክፋቱ እዚህ ላይ ነው፡፡ የዛሬዎቹ አረቦቹም በወገኖቻችን ላይ የጭካኔ እጃቸውን እንዲያነሱ የልብ ልብ የሰጣቸው፣ ይኸው የእኛው የእርስ በእርስ አለመደጋገፍና አለመከባበር ነው፡፡ ትላንትና በጉራ ፈርዳና ቤንች ማጂ ዞን ጎሳ መመዘኛ ሆኖ ‹ውጡ የክልሉ ተወላጅ አይደላችሁም› በሚል በገዛ ወገኖቻቸው እንደጠላት ሀገር ሰው በጦር መሳሪያ ተከበው፣ ንብረታቸውን ሜዳ በትነው ስለተባረሩ ኢትዮጵውያኖች፣ የሰሙ አረቦች ‹ሳወዲያ አረቢያን ልቀቁና ውጡ› ብለው ይህ አይነቱን መዓት ቢያወርዱ ምን ይደንቃል? የባዕድ ሀገር ሰው የትንኝ ነፍስ ያህል እንኳ ሳይጨነቅ እንደዘበት ህይወታችንን ቢነጥቀን በእርሱ ላይ መፍረድ እንዴት ይቻለናል? አሳልፈው የሰጡን እነማን ሊሆኑ ነው?
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
እመነኝ፣ በሳውዲ አረቢያ ጎዳናዎች የሰው ራስ ቅል እንደ በግ በመጥረቢያ ሲከሰከስ፣ እንደ ጦስ ዶሮ ተጋድሞ ሲታረድ፣ በቁሙ እሳት ሲለቀቅበት፣ ህፃናት የወታደር መለዮ በለበሱ አረመኔዎች ሲረገጡ… ልብህ እያለቀሰ፣ ፊትህ በእንባ እየታጠበ ያየኸው አይነት ጭካኔ ምንጩ ይህ ነው፤ ይህም ነው የኢትዮጵያን ሰው በአልባሌ ምክንያት መግደል፣ እያፏጩ ጉዞን የመቀጠል ያህል ያቀለለው፤ ለዚህም ነው በሙስሊሞች ቅድስቲቷ መዲና ላይ በድንጋጤ የጨው አምድ የሆነ አካለ-ቁመና፣ በሽብር ተውጣ አቅሏን የሳተች እህት፣ ስጋት ያናጠበው ወንድም ተመልክተህ በሀዘን የተቆራመድከው፤ ‹‹ወይኔ ወገኔ!›› ብለህ ደም እንባ የተራጨኸው፡፡ …እናስ! ለዚህ ሁሉ ጥፋት ተመጣጣኝ ዋጋ መክፈል ያለበት ማን ነው? ንጉሥ አብደላና ዕኩይ ተከታዮቹ ብቻ? ወይስ እንዲህ የፊጥኝ አስሮ ለአረብ ሀገራት መቀለጃ የዳረገህ መንግስትህም ጭምር?
ከችጋርና ጭቆና ያልተፋታ ሕዝብ ዳቦና ነፃነት ፍለጋ እግሩ ወዳደረሰው ሀገር ተሰዶ መኖሩ በእኛ የተጀመረ አይደለም፤ እንዲያውም ስደተኞችን ካስተናገዱ ከመጀመሪያዎቹ ጥቂት የዓለም ሀገራት መካከል በግንባር ቀደምነት የምትጠቀሰው የእኛዋ የአቢሲኒያ ምድር ኢትዮጵያ ነች፡፡ የሩቁን ትተን እስከ የኃ/ስላሴ ስርዓት ፍፃሜ ድረስ የነበረውን ተጨባጭ ሁነት ብንመለከት እንኳ፣ ‹አረብ ቤት› በሚል ተቀፅላ የሚታወቁት ብዙዎቹ ሱቆችና የንግድ መደብሮች፣ በስደት መጥተው እኩል እንደ ዜጋ ሀገራችን መኖር በቻሉ አረቦች የተያዙ ነበሩ፡፡ የዛሬን አያድርገውና ይህች ገናና ሀገር ለሌሎች ሀገራት ሕዝቦች የነፃነትና የክብር ተምሳሌትም ነበረች፡፡ በመፅሀፍ ቅዱስም ሆነ በቅዱስ ቁርአን ውስጥ በፈሪሐ እግዚአብሔርነቷ፣ በፍትሐዊነቷና በርትዓዊነቷ ስሟ ተደጋግሞ የተወሳና የተመሰከረላት፣ የታላቅ ሕዝብ ታላቅ ሀገር ነበረች፡፡ ዛሬ በተፈጥሮ ማዕድን በልፅጋ የሀበሻ ስደተኞች መናኸሪያ ለመሆን በበቃችው ሳውዲ አረቢያ የተወለዱት ነብዩ መሀመድ የዛሬ 1400 ዓመታት ገደማ በስደት መጠለያነት የመረጧት፣ ሀገሪቷም ተከታዮቻቸውን እጇን ዘርግታ በመቀበል ከራሷ ዜጋ እኩል ተንከባክባ ያኖረቻቸው ስልጡን ሀገር ነበረች፡፡ ማን ነበረ ‹ወርቅ ላበደረ…› ያለው? እነሆም ዘመኑ ተቀያየረና ‹‹የኋላኞቹ ፊተኞች፣ የፊተኞቹ ኋለኞች›› ይሆኑ ዘንድ ግድ በማለቱ ዛሬ አብዛኞቹ የአረብ ሀገራ ኢኮኖሚያዊ ልዕልና እየተጎነፀፉ ሲመጡ፣ እኛ የኋሊት ተንሸራተን ቁልቁል ለመውረድ በቃን፡፡
ምንም እንኳ እነዛ ሁሉ መልካም መገለጫዎቻችን ዛሬም ድረስ ባናጣቸውም፣ በብሔር ክፍፍልና በእርስ በእርስ ሹኩቻ የተነሳ ግን በደህነት ማጥ ውስጥ ተዘፍቀን፣ እኛም በተራችን መሰደድ ዕጣ ክፍላችን ሆኖ ቀረ፡፡ ዛሬ አብዛኛው ወጣት በሀገሩ የመኖር ተስፋው በመሟጠጡ፣ በስደት ወጀብ የሚንገላታ፣ ማረፊያ እንዳጣች ወፍ ሲናወዝ መሽቶ የሚነጋለት ብኩን ሆኗል፡፡ በሀገሩ እጅግ ከመመረሩም የተነሳ ራሱን ለሻርክ ጥርስ፣ ለእንግልት፣ ለግርፊያና ለበልዓ-ሰቦች አሳልፎ እስከ መስጠት በሚያደርሰው የስደት ጉዞ ለማለፍ የማያመነታ ትውልድ ለመሆን ተገዷል፡፡ ይህ ከድህነት ወለል ስር ያሳደረን የዘመን ግርሻ፣ ይህ ከመንግስት ጋር አይንና ናጫ ያደረገን አምባገነናዊ አገዛዝ፣ ለዚህ ሁሉ አሳረ-መከራ ዳርጎን፣ ከሀፍረት ጋር አንገታችንን እስደፋን… ውለታን ከማስረሳቱም በላይ ለከፋ በደል አጋልጦ ቁጭት አስታቀፈን፡፡
ሰሞኑን ‹‹የበላችበትን ወጪት…›› ከሰበረችው ሳውዲ አረቢያ የተሰማው አሰቃቂ ዜናም የእዚህ የኢትዮጵያን ስደተኞች ተከታታይ ፍዳ ጉትያ ነው፡፡ እርግጥ አብዛኛው የአረብ ሀገራት መሬቱ ሰለጠነ እንጂ ሕዝቡ ገና ጨለማ ዘመን ውስጥ ነው፤ ሌላ ሌላውን ወደጎን ብለን የሰሞኑን አውሬአዊ ባህሪያቸው እንኳን እንደ አይነተኛ ማሳያ ልንወስደው እንችላለን፤ ይህ ድርጊትም እንሰሳዊ ባህሪያቸው የስነ-ዝግመት ለውጥን ገና አለማገባደዱን ያመለከተ ነው፡፡ ከአንድ ክፍለ ዘመን በፊት ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ምኒሊክ አድዋ ላይ፣ ያውም ሀገራቸውንና ዙፋናቸውን በጦር ኃይል ለመንጠቅ የጎመዠችው ሮም ያዘመተቻቸው ወታደሮች፣ እልፍ አእላፍ ሠራዊታቸውን ፈጅተው፣ የቅርብ ወዳጆቻቸው የሆኑ የጦር አበጋዞቻቸውን ገድለው የማታ ማታ የሽንፈትን ፅዋ አስጎንጭተው ከማረኳቸው በኋላ በርህራሄ ተንከባክበው እንደያዟቸው የዓለም ታሪክ ያውቀዋል፡፡
በሀገሩ ኑሮ አልቃና ብሎት፣ በሰው ምድር የሰው አደፋ አፅድቶ፣ ቆሻሻ ለቅሞ… ፋታ የማይሰጠውን የእህል ውሃ ጥያቄ ለመሙላት በማሰነ፣ ሆድቃን በሳንጃ መዘርገፍና የዱር አውሬ እንኳ የማይፈፅመው የጋርዮሽ ሴት ደፈራ መፈፀም… ምን አይነት ‹ኢብሊሳዊ› (ሠይጣናዊ) ተግባር ነው? የተቸነፈን መልሶ ማቸነፍ፣ የወደቀን መርገጥስ ‹ከመክፈር› (ፈጣሪን ከመካድ) በምን ይለያል?
አሁንም እደግመዋለሁ፡- ይህ ፖለቲካ አይደለም፤ እየፈሰሰ ስላለ የንፁሀን ደም፣ የወላድ መሀን ስለሆኑ እናቶች፣ ጧሪ ቀባሪ ስላጡ የተራቡ አባቶች፣ አሳዳጊ አልባ ስለሆኑ ህፃናት፣ ያለሚስት ስለቀሩ አባወራዎች፣ ባላቸውን ስለተነጠቁ የቤት እመቤቶች … የሰቆቃ እሪታ ነው፡፡ በወጡበት ሰው ሀገር ላይ ወድቀው ስለሚቀሩ ወገኖቻችን ዋጋ ስለመጠየቅ ነው፤ ለነጋዴው መንግስታችን ኢትዮጵያዊው ዜጋ ዋጋው ስንት እንደሆነ የመሞገት ጉዳይ ነው፡፡
ሀገር ማለት…
ሀገር ምን ማለት ነው? ‹ሀገር› የሚለውን ቃል የኢህአዴግ መራሹ-መንግስት መዝገበ ቃላት ምን ፍቺ ሰጥቶት ይሆን? ሉዓላዊነትስ በ‹አብዮታዊ ዲሞክራሲ› ቀዩ መፅሀፍ አንደምታው ምን ይሆን? …ቀለብ ሰፍረን የምናሳድረውን ሠራዊት ሞቋዶሾ ድረስ ልኮ፣ የባራክ ኦባማን ስጋት ማቃለል? በ‹ተባበሩት መንግስታት› ስም የሲ.አይ.ኤ ቅጥረኛ ሆኖ በሱዳናዊያን የውስጥ ችግር ላይ-ታች እንዲማስን ማድረግ? የሕዝብ ደህንነት መ/ቤትስ ኃላፊነቱ የእናንተንና የቅምጦቻችሁን ደህንነትና ምቾት መጠበቅ ነውን? የአምባሳደሮቻችን የሥራ ድርሻ ፓስፖርት ማደስና የመግቢያ ፍቃድ መስጠት ብቻ ነው? በስደተኛ ወገኖቻችን ላይ ‹ጊንጥ ሰላይ› መሆን? ቦንድ መሸጥ? ‹ኢህአዴግ ጌታ ነው› እያሉ መስበክ? …ወይስ የዜጎችንም ደህንነት መከታተልና መጠበቅንም ጭምር? …ይህ ነው የወቅቱ ዓብይ ጥያቄ፡፡
የዲፕሎማሲ ግንኙነትስ ምን ማለት ነው? አገዛዙ በአንድ ወቅት ተቀማጭነቱ ኳታር-ዶሀ የሆነው ‹አልጄዚራ› ቴሌቪዥን ‹ስሜን አጠፋ› በሚል የኳታርን ኢምባሲ እንደ ዘጋው አይነት ስራን ብቻ የሚመለከት ይሆን? ከዋነኞቹ ለጋሽ ሀገራት በግንባር ቀደምነት የምትመደበው ኖርዌይስ ኢምባሲዋ የተዘጋው ለማን ትርፍ ነበር? ለብሔራዊ ጥቅም መቆርቆርስ ‹ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት አልተከበረም› ብለው ዘገባ ባወጡ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ላይ ያንን ሁሉ አቧራ ማስነሳት ይሆን?
ሌላው ቢቀር የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለምን እንደ ተመሰረተ ይዘነጋል? አባቶቻችን ኮሪያና ኮንጎ ድረስ የዘመቱት ለዓለም ዜጎች ሰላም መሆኑስ እንዴት ይረሳል? የድርጅቱ አባል ሀገራት የፈረሙት ስምምነትስ የሳውዲ አረቢያን ሽፍትነት እንኳ ለመከላከል አቅም አይኖረውም? በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት እልፍ አእላፍ ወታደሮቻችን ካለቁብን በኋላ ከባረንቱ የተመለስነው፣ ባድሜ ላይ የቆምነው፣ በዛላንበሳ የታገድነው… የማንን ሕግ አክብረን ነበር? ያውም ‹በስለላ ስራ ሊሰማሩ ይችላሉ› ተብለው የተጠረጠሩ ኤርትራውያን እንዲያ በክብርና በእንክብካቤ ወደ ትውልድ ሀገራቸው የተሸኙት፣ በጦር ሜዳ የተሸነፈው ሻዕቢያ ተፈርቶ ነበር እንዴ? …ይህ ነው እንቆቅልሹ፡፡
ዛሬስ መንግስታችን የስደተኛ ዜጎችን ደህንነት በምልዓት የማይከታተለውና የድረሱልኝ ጩኸታቸውን ሰምቶ ፈጥኖ እጁን የማይዘረጋላቸው ለምን ይሆን? ጉዳዩ ከአቅሙ በላይ ሆኖበት? ወይስ በለመደው የንቀት መነፅር አይቶ እንዳላየ በቸልተኛነት አልፎት ነውን? በርግጥ ይህንን የበደል ማማ ካለፈው ታሪኩ አንፃር ከገመገምነው ምክንያቱ ሀገራዊ ስሜቱ ደካማና ከሥልጣኑ ሌላ ምንም የሚያሳስበው ነገር ባለመኖሩ ብቻ እንደሆነ ይገባናል፡፡ ሌላው ቀርቶ ሠማያዊ ፓርቲ የአረቦቹን ወደር የለሽ ጭካኔ ለማውገዝ በሳውዲ አረቢያ ኢምባሲ በር አጠገብ የጠራውን የተቃውሞ ሰልፍ ያገደው ‹ይህ አይነቱ ሀገራዊ መቆርቆር ነገ ደግሞ መስቀል አደባባይን በሕዝብ ሱናሚ ለማጥለቅለቅ መነቃቃት የሚፈጥር ገፊ ምክንያት ሊሆን ይችላል› ብሎ በስጋት ስለተጠፈነገ ይመስለኛል፡፡
የሆነው ሆኖ የመንግስት ህልውናም ሆነ አቅም በእንዲህ አይነቱ ወቅት ነውና የሚፈተነው ኢህአዴግም በዚህ ተግባሩ ዜጎቹን የመታደግ ገት እንዳሌለው አስመስክሯል፡፡ መቼም በሲ.አይ.ኤ ተላላኪነቱ በ‹ዋይት ሀውስ› ማህደረ-መዝገብ ውስጥ ከጊዜ ጊዜ እየዳጎሰ የመጣው የ‹ውለታ›ው ዶሴ ለእንዲህ አይነቱ ፈታኝ ወቅት መሆን ይሳነዋል ማለት ይከብዳል፡፡ ሼክ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ ጥቂት የማይባሉ የሳውዲ ነጋዴዎች፣ ሀገራችን ውስጥ በበርካታ የንግድ ዘርፎች ተሰማርተው አትርፈው ማደራቸው፣ በሰፋፊ እርሻዎች ዘርተው ማጨዳቸውስ እንደምን ተዘነጋ? ይህ ቢያንስ በነፍስ-ውጪ ነፍስ-ግቢ ለተያዙ ወገኖቻችን እንዴት የመደራደሪያ ጉልበት መፍጠር ሳይችል ቀረ? …በርግጥ መለስ ዜናዊ በ2004 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ከጎራ ፈርዳ ስላፈናቀላቸው አማርኛ ተናጋሪ ወገኖቻችን በተጠየቀበት ጊዜ ‹‹ደን ጨፍጫፊዎች ናቸው›› ሲል የስላቅ መልስ እንደሰጠው ሁሉ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድኀኖምም የሳውዲውን እልቂት በተመለከተ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቦ ‹‹የማባረር ሥራው በኢትዮጵያውያን ላይ ብቻ ያነጣጠረ እንዳልነበረ ተረድተናል›› በማለት መቀለዱ፣ ስርዓቱ ‹አስተዳድረዋለሁ› ከሚለው ሕዝብ ይልቅ ሥልጣኑንና ተያይዘው የሚመጡ ጥቅሞቹን በዜጎች ሕይወት ጭምር ተደራድሮ ከማስከበር እንደማይመለስ የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡ እንደ መንግስት በሀገር ሀብት እንደአሻው እየተምነሸነሸ፣ ‹ግዴታዬ የባቡር መንገድና ኮንዶሚንየም ቤት መስራት ብቻ ነው› ማለቱ ይህንኑ ይመሰክራል፡፡ አሊያማ ፋሺስቱ ጣሊያን እንዲያ በርካታ ድልድዮች፣ መንገዶች፣ ቤቶች… ገንብቶ ሲያበቃ፣ ‹ሀገር› ማለት ሕዝብ የሰፈረበት ሉዓላዊ ግዛት ማለት ነው ተብሎ ያ ሁሉ መስዕዋትነት ተከፍሎ በኃይል እንዲባረር ባልተደረገ ነበር፡፡
‹ሕዝቤን ልቀቅ!›
በዘመነ-ኦሪት በግብፅ ዙፋን ላይ በተፈራረቁ ፈርኦኖች፣ ለባርነት የተዳረጉ ዕብራዊያንን ነፃ ያወጣ ዘንድ በፈጣሪ ተመርጦ የተላከው ሙሴ ‹‹እግዚአብሄር ‹ያመልከኝ ዘንድ ሕዝቤን ልቀቅ!› ብሎሀል›› ማለቱ በቅዱሳት መፃህፍት መገለፁ እውነት ነው፡፡ በዚህ ዘመን ደግሞ ራሱን ‹ኢህአዴግ› ሲል በሚጠራው ‹አምሳለ-ፈርኦን› ለመከራና ለሀፍረት የተዳረጉ ሕዝቦች አርነት ይጎናፀፉ ዘንድ ‹የሙሴ ያለህ!› የሚለው
ጩኸታቸው ከተራራ ተራራ እያስተጋባ መሆኑ ሌላ እውነታ ነው፡፡ በሳውዲ አረቢያ የግፍ ሰለባ የሆኑ ኢትዮጵውያን ደምም ዋይታ እየተበራከተ ነው፤ ስርዓቱ እንዲህ አይነቱ ሰቆቃን ለፖለቲካ ትርፍ እየተጠቀመበት መሆኑንም ሰሞኑን የመንግስት እና ደጋፊዎቹ ሚዲያዎች የሚያሰራጩትን ዘገባ መመልከት በቂ ነው፡፡ መቼም መሬት ልሰው፣ አፈር ቅመው ያፈሩትን ንብረት ተነጥቀው፣ ባዶአቸውን እየተመለሱ ያሉ ስደተኞችን ‹በሀገራችን መስራት ይሻለን ነበር› እንዲሉ ማስገደድ ለርካሽ ፖለቲካዊ ትርፍ ካልሆነ በቀር ሌላ ትርጉም የለውም፡፡ አስከፊው ድህነታችን ጉርሻ እስከ መግዛት፣ ከቆሻሻ ገንዳ ውስጥ ቅልጥም እስከ መምጠጥ፣ የወደቀ ምግብ ከውሻ ጋር ተጋፍቶ እስከ መመገብ… በደረሰበት በዚህ የችጋር ዘመናችን ላይ በምን አመክንዮ፣ ከየትኛው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ተመዝኖ ሊታመን ይችላል ተብሎ ነው ‹ሀገር ውስጥ ሰርቶ በሰላም መኖር ይቻላል› የሚለው ተራ ፕሮፓጋንዳ ነጋ-ጠባ የሚደሰኮረው? ምንድር ነውስ የሚሰራው? እዚህ እኛ ሀገር የማንን መፀዳጃ ቤት ንጽህና መጠበቅ ይሆን የአረቦቹን ያህል ዳጎስ ያለ ክፍያ ማስገኘት ቀርቶ፣ በቀን ሁለቴ ለመብላት የሚያግደረድረው? ቅጥ አንባሩን ያጣው የግብር ፖሊሲያችን፣ እንጀራ ቸርቻሪዎችን ሳይቀር አሳድዶ የእለት ጉርሻቸውን እየነጠቀና በተንሰራፈው ድህነት ላይ ተጨማሪ እልቂት አውጆ ድሆችን ለማጥፋት ሰይፉን በሚያወናጭፍበት በዚህ ወቅት፣ ወጣቱ እንዴት ብሎ ነው በሀገሩ ሰርቶ መኖር ይችላል የሚባለው? ገና ጀንበር ከማዘቅዘቋ ጎዳናውን የሚያጥለቀልቁት ህፃናት ሴተኛ አዳሪዎችንስ ምን እንበላቸው? የትኛው ተቀጣሪስ ነው በደሞዙ የወር ቀለቡን ሳይሳቀቅ መሸመት የቻለው? …ሁላችንም የመዳፋችንን ያህል አብጠርጥረን የምናውቀው በመሬት ያለው ተጨባጭ እውነታ ይህ ነው፡፡
እነሆም በመጨረሻ እንዲህ ማለት ወደድኩ፡- ስርዓቱ ሰባኪው እንዳለው ‹የከንቱ ከንቱ፣ ከንቱ› ቢሆንም፣ አቶ መለስ ዜናዊ በኤርትራ የመጀመሪያው የነፃነት ዓመታዊ ክብረ በዓል ላይ ተገኝቶ በአስመራ ሳባ ስታዲዮም ለተሰበሰበው ህዝብ በደርግ የደረሰባቸውን በደል በማስታወስ ‹‹በእናንተ ጀርባ ላይ ያለው ጠባሳ በእኛም ላይ አለ›› ሲል ሀዘኑንና መቆርቆሩን እንደገፀላቸው ሁሉ፣ በሳውዲ አረቢያ የግፍ ሰለባ የሆናችሁ ወንድም-እህቶቼ ሆይ! የእናንተ ሰቆቃና በደል፣ በእኛም ግንባር ላይ ተቸክችኮ ሀፍረታችችንና ውድቀታችንን የጋራ እንዳደረገው የታሪክ ፍርድን መጠበቁ አይቀሬ ነው፡፡ እመኑኝ ያች ዕለትም አብረን የምንነሳበት፣ ከፍ ብለን የምንበርበት ትሆናለች፡፡›
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

No comments:

Post a Comment