Tuesday, January 1, 2013

እንጠንቀቅ ! እየተበላላን እንዳንጠፋፋ፡፡

ዘረኝነት በወለደው ጦስ በአሜሪካ በነጮች መንደር ጥቁሮች ማለፍ እንኳ አይችሉም ነበር፡፡ የነጮች ምግብ ቤትና የጥቁሮች ምግብ ቤት እንዲሁም ትምህርት ቤት እስከ ቅርብ ዓመታት የተለያዩ ነበሩ፡፡ በዘረኝነት ናዚዎች ከስድስት ሚሊየን በላይ አይሁዳውያንን ጨፍጭፈዋል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ጥቁሮች በውሾች ሳይቀር ተበልተዋል፡፡ በሴራሊዮን የአንድ ወር ሕፃናት አድገው ይዋጉናል ተብሎ እጃቸው ተቆርጧል፡፡ በአገራችንም በኢትዮጵያ በተለያዩ ዘረኝነት በወለደው ጦስ በክልሎች አሰቃቂ ወንጀሎች ተፈጽመዋል፡፡ 
አንድ ሰው ሲናገር፣ ‹‹በሰሜን ያለ የአንበሳ መንጋ ወደ ደቡብ ቢሄድ፣ በደቡብ ያለው የአንበሳ መንጋ አንተ ከሰሜን ነህ፣ እኔ ከደቡብ ነኝና አልፈልግህም አይለውም፡፡ ሰው ግን ሰሜንና ደቡብ እያለ ይጠፋፋል፤›› ብሏል፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረትን ሁሉ ሁሉንም በየወገኑ ፈጥሮታል፡፡ የአንበሳ ወገን አንበሳ ነው፣ ስለዚህ በመንጋ ይጓዛል፡፡ የወፍ ወገንም ወፍ ነው፣ ስለዚህ በአንድነት ይበራሉ፡፡ የሰው ወገንም ሰው ነው፣ ስለዚህ በኅብረት መኖር ይገባዋል፡፡ የሰው ልጅ ግን አራዊትና አእዋፋት ያከበሩትን የተፈጥሮ ሕግ እየጣሰ በኅብረት መኖር አቅቶታል፡፡ የምዕራቡ ሰው ከምሥራቁ ሰው የዓይን አቀማመጡና የአፍንጫ ስፍራው አንድ ዓይነት ነው፡፡ ይህ የሚያሳየን ሁላችንንም አንድ እጅ እንደ ፈጠረን ነው፡፡ አንድ እጅ አበጅቶን መከፋፋት፣ አንድ አባት ሳለን መለያየት አይገባም፡፡ 

አዎ በደቡብ ያለው የአንበሳ መንጋ ከሰሜን የመጣውን እኔ ደቡብ ነኝ አንተ ከሰሜን ስለሆንህ አልፈልግህም አይለውም፡፡ ሰው ግን ዛሬም ሰሜንና ደቡብ እያለ ይለያያል፡፡ መለያየቱ መጠፋፋትን እንደ ወለደ ቋሚ ምስክሮች አሉን፡፡ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ በመላው ዓለም የዘረኝነትና የሃይማኖት ጽንፈኝነት እየተጋጋለ ይገኛል፡፡ ላይ ላዩ የሚወራው ስለ አንዲት ዓለም ነው፤ እውነቱ ግን ሰዎች እስከ ጐጥና እስከ ቀበሌ ወርደው ተለያይተዋል፡፡ መልካም ሰው ቢሆንም የእኔ ዘር አይደለምና አልቀበለውም፤ ጎበዝ ቢሆንም የእኔ ጎጥ ተወላጅ አይደለምና ሥፍራ አይገባውም ማለት የተለመደ ሆኗል፡፡ ሰው የራሱን ዘር መውደዱ፣ ቋንቋውን አክብሮ መጠቀሙ መልካም ነው፡፡ የገዛ እናቱን ለመውደድ የሌላውን እናት መጥላት እንደማያስፈልግ ሁሉ የራሳችንን ዘር ለመውደድም የሌላውን ዘር መጥላት አያስፈልገንም፡፡ ዘረኝነት በብዙ ክፉ ነገሥታት የሚሰበክ ክፉ ስብከት ነው፡፡ ምክንያቱም ሕዝቡ ካልተከፋፈለ አይገዛልንም የሚል ሥጋት ስላላቸው ነው፡፡ 
በሩዋንዳ በሁቱና ቱትሲ የደረሰውን እልቂት ማሰብ እንኳ ይከብዳል፡፡ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ አንድ ሚሊዮን ሕዝብ አልቋል፤ ነጭ ዓባይ እስኪቀላ ምድሪቱ በደም አበላ ተመትታለች፡፡ መታወቂያ እየታየ በሚገደልበት የሩዋንዳ የጨለማ ወር በአገራችን ዘሩንና ብሔሩን የሚገልጥ መታወቂያ ይሰጥ ነበር፡፡ ሰው እንኳን ከታሪክ ከዛሬም መማር እንዳቃተው ምስክር ነው፡፡ እንደ ሩዋንዳ እንሆናለን የሚል ሟርትም ሲነገር ብዙ ሰምተናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ጠብቆን ከዚህ ደርሰናል፡፡ 
ያልተወራረዱ የዘረኝነት ጥፋቶች በምድራችን ላይ አሉ፡፡ ስለዚህ ይቅር መባባል፣ የመናናቅን ዘመን ቀብረን እግዚአብሔር በሰጠን ምድር በሰላም መኖር ይገባናል፡፡ ይህንን በትልቁ ማወጅና ብሔራዊ የእርቅ ቀን ማዘጋጀት የሃይማኖት ተቋማት ትልቅ ድርሻ ነው፡፡ ዛሬ የተዳፈኑ ነገሮች ለነገ ሰደድ እሳት ናቸው፡፡ 
የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር በኢትዮ-ኤርትራ ግጭት የአብያተ ክርስቲያናት ድርሻ ምን ያህል እንደሆነ ሲጠየቁ፣ ‹‹እንኳን እኛን ሊያስታርቁ ፍርድ ቤቶቻችንን ያጣበበው የእነርሱ ጉዳይ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ዘረኝነት ቤተ ክርስቲያንን እየበከለ ነው፡፡ ሙያህ ምንድነው? ማለት ቀርቶ አገርህ የት ነው? መባል ከጀመረ ሰንብቷል፡፡ በውጭ አገር ባሉ አብያተ ክርስቲያናት የአማራ ቤተ ክርስቲያን፣ የኦሮሞ ቤተ ክርስቲያን እያሉ መለያየት የተለመደ ነው፡፡ እግዚአብሔርንም የእኛ ዘር ማድረጋችን አሳፋሪ ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ስም በከንቱ መጥራት ትልቅ በደል ነው፡፡ ይልቁንም የዘረኝነት ግንብ ፈርሶ አይሁዳዊ አረማዊ መባባል ቀርቶ ሁሉ በክርስቶስ አንድ የሆነባት ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ያፈረሰውን ወገንተኝነት እንደገና መካብ አይገባትም፡፡ ክርስቶስ የሞተው ተለያይተው የነበሩትን ለማቀራረብ፣ የተጣሉትን ለማስታረቅ ነው፡፡ ለዓለም የተሰበከውም የምሥራች ይህ አንድነት ነው፡፡ የሚያለያዩ ነገሮች ቢነሱ እንኳ አንድ የሚያደርገን ክርስቶስ ከልዩነታችን በላይ ነው፡፡ 
‹‹ለአንቱ ማደሪያ የለዎ ከነአህያዎ መጡ›› እንዲሉ ለራሳችን አንድ ሳንሆን ሌሎችን አንድ ማድረግ አንችልም፡፡ ከዚህ በኋላ ሰዎችን በክርስቶስ ካልሆነ በቀር በሀብታቸው፣ በቀለማቸው፣ በዘራቸው ለማወቅ አልሻም የሚል መሐላ ልናደርግ ይገባል፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ሰው በአመለካከቱ እንጂ በዘሩ ሊዳኝ አይገባውም፡፡ ክፋትና ደግነት የሰው ጠባይ እንጂ የዘር ጉዳይ አይደለም፡፡ የትም ቦታ ክፉ፣ የትም ቦታ ደጎች አሉ፡፡ ብቻ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በአንድ ጊዜ ክርስቶሳዊ በአንድ ጊዜ ዘረኛ መሆን እንደማይቻል ሊያውቁ ይገባቸዋል፡፡ አንዱን መምረጥ ግድ ይላል፡፡ 
አንድ የአንበሳ ግልገል ተገኝቶ በባለሙያ ተይዞ በሔሊኮፕተር ተሳፍሮ ቤተ መንግሥታችን እንደ ገባ በአንድ ወቅት በዜና ሰምቻለሁ፡፡ አንድ እናቱ የሞተችበት ሕፃን በአገራችን ይህ ይደረግለት ይሆን? ሰሞኑን በአሜሪካ ምድር 20 ሕፃናትን የፈጀ ምክንያት የለሽ አደጋ ተከስቷል፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ለሁለተኛ ጊዜ በቅርቡ የተመረጡት ባራክ ኦባማ ዕንባቸው ሲፈስ ዓይተናል፡፡ እኛ አገር ቢሆን ሃያ ነው ሰላሳ የሚለው ቁጥር ያጣላናል፡፡ ተኳሹ ከየትኛው ፓርቲ ወይም ወገን መሆኑ ያስጨንቀናል፡፡ ነገር ግን አንድ ሰውም ትልቅ ነው፡፡ እውነተኛ አመራር የብዙኃን መብት ብቻ ሳይሆን የአንድ ግለሰብም መብት የሚያከብር ሊሆን ይገባዋል፡፡ ማንም ያድርገው ሰው በሰው ላይ ይህን በማድረጉ ማዘን ይገባናል፡፡ 
አንድ ሊቅ ‹‹ታይፑን በቅጡ ሳንጠቀምበት ኮምፒውተር መጣ፣ እርሱም ሳይገባን ሌላ ለመቀበል እየተሰናዳን ነው፤›› ብለውኛል፡፡ ስለ እንስሳት መብት መነጋገር ጀምረናል፡፡ የሰው መብት ግን አልተሟላም፡፡ ሁሉንም ቀማሾች እንጂ አንዱን እንኳ ለመጥገብ የታደልን አይመስለኝም፡፡ ብዙ መናገር መውደድ ጥቂት ለመኖር አለመግደርደር ምንኛ ክፉ ነው! ዝርያቸው እየጠፋ ስላለ አራዊትና ዕፅዋት የሚደረገውን ውይይትና ጥረት ማድነቅ ይገባናል፡፡ ከዚያ በፊት ግን በጎዳና የወደቁ ሕፃናት አድገው ለዚህች አገር ምን ዓይነት ዜጋ ይሆናሉ? ብለን ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ እኛ ልጆቻችንን በከረሜላ እየደለልን ወደ ትምህርት ቤት ይዘን ስንሄድ እኛ አናያቸውም እነርሱ ያዩናል፡፡ የእኛም ልጆች ያድጋሉ፣ እነዚያም የጎዳና ልጆች ያድጋሉ፡፡ ነገ ባላጋራ እንደሚሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ልጆቻችን ስለሚኖሩበት ቤት ብቻ ሳይሆን ለአገርም ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ 

ፍጥረት ተደጋግፎ ይህችን ዓለም ያስቀጥላታል፡፡ ስለዚህ አራዊቱም ሆነ ዕፅዋቱ መኖር ላይ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ የሰውን መብት ካላከበርን የእነዚህን መብት ማክበር አንችልም፡፡ ከናሳ የምርምር ጣቢያ ወደላይ የሚመጥቁት መንኰራኩሮችን የሚያዩ በአጠገባቸው ያሉ የላቲን አገር ድሆች፣ በጎዳና የወደቁ ሕፃናት በትዝብት ‹‹የምድሩን ችግር ጨርሳችሁ ይሆን?›› ሳይሉ አይቀርም፡፡ በአገራችንም እኛ ስለ ኑሮ ውድነት  ስናስብ ቀኑ የጨለመባቸው ድሆች ረሃባቸው በእግዚአብሔር ፊት ይከሰናል፡፡ ስለከሰሰንም በልተን ጤና፣ ቤት አድረን ድፍረት አላገኘንም፡፡ 
እየሞቱ ያሉ ድሆችን ለመታደግ ስንዴ ጭነው የሚሄዱ መኪኖች መንገድ ይቀራሉ፡፡ የረሃብተኛውን ስንዴ ሽጠው ሀብታም ለመሆን ብዙ ርካሾች ያስባሉ፡፡ እንዲህ ያለ ጭካኔ የት ይገኛል? እንዲህ የሚያደርጉትን ነው ሃይማኖተኛ ቀናዕያን እያልን የምናወድሳቸው፡፡ በእውነት ልባችን እጅግ ጠንካራ ነው፡፡ የምንናገራቸው መልካም ቃላት እንደ ገደል ማሚቶ የሰማናቸው እንጂ የኖርናቸው አይደሉም፡፡ ንግግር ውሰት ሲሆን ውርደት የኑሮ ጭማቂ ሲሆን ክብር አለው? ስለ ሰብዓዊነት እናወራለን፤ ስለ መብት እንናገራለን፡፡ ይህን የምንናገረው በዚህ ስም የመጣ በጀት ስላለ ብቻ ነው፡፡ የአገር ለውጥ የእያንዳንዳችን ለውጥ ውጤት እንጂ የመሪዎች ብቻ መለወጥ አይደለም፡፡ 

ብዙ ትምክህቶች ያሉን ሕዝቦች ነን፡፡ ኩሩ ሕዝቦች መሆናችን ሲነገር የኖረ ነው፡፡ እውነት ነው ጣሊያንን መልሰናል፣ በተቃራኒው ረሃብን መመለስ አልቻልንም፡፡ ጦር አንስተናል መዶሻ ግን አላነሳንም፡፡ ጥይት በትነናል፣ መሬታችንን ግን አላረስንም፡፡ ከመካከላችን የቀደመን ካለ ጠልፈን ለመጣል የምንኖር፣ በመልካም ነገር ሳይሆን በክፋት የምንወዳደር፣ ቂማችን እንዳይጠፋ ሐውልት እየተከልን የምናዘክር ነን፡፡ ጅብ ፊትና ኋላ ሆኖ አይሄድም ይባላል፡፡ ምክንያቱም ከፊት ያለው ታፋው ሲገላበጥ ከኋላ ያለው ጐምዥቶ ይገምጠዋል፣ ከጀመረውም ይጨርሰዋል፡፡ ስለዚህ ጅብ የሚጓዘው ተጠባብቆ ነው፡፡ ሰው የገዛውን ልብስ እንኳ ለመልበስ ዙሪያውን የሚፈራበት ማኅበረሰብ በመሆናችን ልናዝን ይገባናል፡፡ ከፊት የቀደመ ካለ እንቦጭቀዋለን፣ እስክንጨርሰው እንቅልፍ የለንም፡፡ ስለዚህ ኑሮአችን የመጠባበቅ ነው፡፡ የተማረው እውነትን ለመናገር ፈርቶ እንዳልተማሩት እየተናገረ ‹‹ጐመን በጤና›› እያለ የሚኖርበት ምድር ሆኗል፡፡ 
‹‹ኢትዮጵያ የአንድ ሐዋርያን ደም ያላፈሰሰች አገር ናት›› እንላለን፡፡ አዎ እስራኤላዊ ሐዋርያ አልገደልንም፡፡ የራሳችንን ሐዋርያት፣ እግዚአብሔር የላከልንን መምህራን ግን ፈጅተናል፡፡ መማር ዕዳ እስኪመስል የተማሩትን ስም ሰጥተን፣ ያልተማሩትን ጎፈር አልብሰን የምንኖር ነን፡፡ ይህ ተግባር ዛሬም ድረስ ያልቀረ ጽዋው ያልሞላ በደል ነው፡፡ 

የቤተ መንግሥቱም ትምክህት ‹‹ኢትዮጵያ በታሪኳ የሌላውን ግዛት ደፍራ የማታውቅ፣ የራሷንም የማታስደፍር አገር ናት፤›› የሚል ነው፡፡ እውነት ነው፡፡ ሌላውን የምናከብረውን ያህል ጎረቤታችንን ብናከብር መልካም ነበር፡፡ ወሰን እየገፋን፣ የድሆችን ርስት በግፍ እየነጠቅን፣ ላጨበጨበልን ሽልማት ላላጨበጨበልን ሞትን እየከፈልን የምንኖር ነን፡፡ የሐሳብ ልዩነት እንኳ መሣርያ የሚያማዝዘን፣ ለሁሉም ነገር የመደብነው በጀት የሃይማኖት ውግዘትና የመንግሥት ጥይት መሆኑ ያሳዝናል፡፡ የሐሳብ ፍጭትን እስከፈራን ድረስ እውነት አትበራም፡፡ 

አዎ የሌላውን አገር ድንበር አልገፋንም፤ ወንድማችንን ግን አልበደልንምን? አዎ የሌላውን ንብረት አልቀማንም፤ ጉቦ በልተን ግን በንፁኃን ላይ አልፈረድንምን? ለድሆች የመጣ መድኃኒት አውጥተን አልሸጥንም? አዎ ቅድሚያ ለፈረንጅ እንላለን፤ ቅድሚያ ለሰው ልጅ የምንለው መቼ ነው?

አዲሱ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሰሞኑን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስመራ ሄደው ከኤርትራ መንግሥት ጋር ለመነጋገር ፈቃደኛ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡  የእርስ በርስ ግጭታችንን ለመፍታት ይህን ሆደ ሰፊነት ማነው የነጠቀን? 


በንጉሡ ዘመን አንድ ትልቅ፣ አስተዋይ የሆኑ የኦሮሞ ባላባት አጠገባችን ያሉትን አማሮች እናስወጣ ብለው ጥቂት ግለሰቦች ያማክሯቸዋል፡፡ እርሳቸውም ሚስታቸውን ጠርተው ከነጩ ጤፍና ከጥቁሩ ጤፍ ዘግነሽ አምጭልኝ አሏት፡፡ ነጩንና ጥቁሩን ጤፍ ደባለቁና ‹‹ይህንን ለይታችሁ አምጡልኝ ከዚያ በኋላ እንነጋገራለን፤›› አሉ፡፡ ሰዎቹም ‹‹እንዴት መለየት እንችላለን?›› አሉ፡፡ እርሳቸውም ‹‹እኛ ኢትዮጵያውያን መለያየት እንችልም›› ብለው አሳፍረው ሸኙ፡፡ አዎ ዛሬም እንዲህ ያሉ አስተዋዮችን ያስነሳልን፡፡ የማይለየውን ነገር ለመለየት ስንሞክር ትልቅ አደጋ ይፈጠራል፡፡ 


እርስ በእርስ በመበላላትና በመነካከስ አንዱ ጠፍቶ አንዱ አይኖርም፡፡ መበላላት ለመጠፋፋት ነው፡፡ እግዚአብሔር ከአየሩ፣ ከፀሐዩ፣ ከምድሩ መርጦ ሰጥቶናል፡፡ የበደለን ጠባያችን ነውና እንታረም! እየተበላላን እንዳንጠፋፋ!
                         ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!!!!!!!!!

No comments:

Post a Comment