Tuesday, January 8, 2013

ሕዝቦች የስልጣን ባለቤቶች ናቸው፡፡ የምርጫው ውጤትም በእጃቸው ላይ ነው፡፡ኢትዮጵያ ውስጥስ ?

ኢትዮጵያ ለዘመናት የነገሰና ስር የሰደደ ድህነት፣ ስራ አጥነትና ማህበራዊ ቀውስ የተንሰራፋባት ሃገር ናት፡፡ ኑሮ ያደቀቃቸው ዜጎች ከመተዳደር ለመገዛት የተመቹ መሆናቸው ዓለም የመሰከረው እውነታ ነው። የስራ እድል፣ ትምህርት፣ የቀበሌ ራሽን፣ የጤና አገልግሎት፣ የመሰረተ ልማት ፍጆታ፣ የመኖርያ ቤት አቅርቦት በገዢው ፓርቲና በመንግስት ችሮታ ስር በተያዙባት ኢትዮጵያ፤ የኢህአዴግ አባል መሆን በተለይ ደግሞ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኘው ማህበረሰብ የመብት ጉዳይ ሳይሆን አማራጭ የሌለው የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ በ2002 ምርጫ ኢህአዴግ 99.6 በመቶ ማሸነፍ ባልቻለ ነበር፡፡ 

ጤናማና ሚዛናዊ በሆነ ዴሞክራሲያዊ የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ውስጥ አንጻራዊ ብልጫ ማስመዝገብ ፍትሐዊ ነው፡፡ ዘጠና ዘጠኝ ነጥብ ስድስት በመቶ በምርጫ ማሸነፍ ግን በመድብለ ፓርቲ ስርዓቱ ላይ ትልቅ ችግር መኖሩን ጠቋሚ ነው፡፡ ለንጽጽር ስለማይመች በዴሞክራሲ የበለጸጉት ሃገራትን የምርጫ ውጤት መፈተሹ የማይሞከር ነው፡፡ ይህም ሆኖ በሁለንተናዊ የድል ባለቤትነታቸው የሚተማመኑት ሶሻሊስቶችም ቢሆኑ ብቻቸውን እንደተወዳደሩ እያወቁ፤ የማይደግፋቸው ማህበረሰብ ሊኖር እንደሚችል ቀልባቸው ስለሚነግራቸው የምርጫ ውጤታቸውን ከዘጠና አምስት በመቶ በላይ አያሳድጉም፡፡ ከዚህ አኳያ ኢህአዴግ ለዴሞክራሲው ይቅርና ለቀልቡና ለጥላው እንኳን መታመን ያልቻለ ድርጅት መሆኑን ምርጫ 2002 በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ የስልጣን ባለቤት የሚሆንበት ግዜ ቅርብ ነው ።
                                                      ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!
                                                                     ከሰብኣዊ

No comments:

Post a Comment