Wednesday, June 17, 2015

የስደቱን መከራ ወደ ምፍትሔ መፈለጊያ እድልነት መቀየር ይቻላል? የመነሻ ሀሳቦች (ፈቃደ ሸዋቀና)

ማስታወሻ ፥ (የዚህን ጽሁፍ መሰረታዊ ይዘት በቅርቡ በተካሔደው ኢሳት ባዘጋጀው ጉባዔ ላይ አቅርቤው ነበር። የኢትዮጵያን ሁኔታዎች አዘውትሮ እንደሚከታተል ኢትዮጵያዊ በሀገራችን የሰፈነው ዘግናኝ ድህነት የፈጠረውን አሳዛኝና አዋራጅ ስደትና ወደፊትም መፍትሔ ካልተበጀ ሊፈጥር የሚችለውን ችግር ገምቼ የባሰ ድህነት ውስጥም ሳንዘፈቅ ችግሩን ምን ብናደርግ ነው መቋቋም የሚቻለው በሚለው ጥያቄ ላይ ሳሰላስል የመጣልኝ ሀሳብ ነው። የሰጠሁት የመፍትሄ ሃሳብ በጉባዔው ላይ ትንሽ አቧራ አስነስቶ ነበር። አንዳንዶችም የየዋህ ሀሳብ አድርገው ወስደውታል። እኔ ችግር ማውራትና ማማረር የሰለቸኝ ሰው ነኝ። ብሶት በባዶ ከማውራት ብዬ የመሰለኝንና ብዙ ዋጋ ሳያስከፍል የችግራችን መፍትሄ ይሆናል ያልኩትን ሀሳብ ነው አቅርቤ ውይይት መቀስቀስ የሞከርኩት። የሌሎችን ሀሳብ ማየትና መከራከር እፈልጋለሁ። ሀሳቤን በተሻለ ሀሳብ ለመለወጥ ዝግጁ ነኝ። የማነሳው ሀሳብ ስራ ላይ የሚውል አለመምሰሉ ይገባኛል።
ሙከራዬ የመፍትሄውን ሀሳብ ከማርቀቅ ይልቅ ማዋቀር ላይ ይበልጥ ያተኮረ ነው። የተሟላ ለመሆን ብዙ ውይይት ይጠይቃል። ሀሳቡ ስራ ላይ የሚውለው ተገቢውን በቂ አቅም ገንብቶ በገዥው ሀይል ላይ ተጽዕኖ በመፍጠር እንጂ በልምምጥና ለቅንነት አቤት በማለት ብቻ አይደለም። በዚህ ሀሳቤ ላይ ሊሞግቱኝ የፈለጉ ሰዎች የኔን ሀሳብ ማንጓጠጥ ብቻ ሳይሆን ይህ የኔ ሀሳብ በምን ቢተካ የተሻለ እንደሚሆን የማስረዳት እዳ እንዳለባቸው ሊያውቁ ይገባል። ያን ጊዜ ነው ክርክራችን ትርጉም የሚኖረው።)
መግቢያ፥
ችግሩን አጉልቶ ያሳየን መታረድ ላይ መድረሳችን እንደሆነ እንጂ በስደት የሚደርስብንን ውርደትና ሰቆቃ መመዝገብ ከጀመርን ከርመናል። በየአረብ አገሩ እህት ወንድሞቻችን የሚደርስባቸው መከራ ፣ ወገኖቻችን ስደት ሀገር ከመግባታቸው በፊት መንገድ ላይ ስለሚደርሰው አልቂትና ስቃይ መስማት ከጀመርን ቆይተናል። ሀዘናችን ውስጣችን ድረስ የተሰማንን ያህል በሁላችንም ጭንቅላት ውስጥ የሚጉላሉት ጥያቄዎች አልተመለሱልንም። ይህ ሰቆቃ የመጨረሻው ለመሆኑ ምን ዋስትና አለ? ነገ የባሰ የሚሰቀጥጠን ነገር እንደማይመጣስ በምን ማረጋገጥ ይቻላል? ለምንድነው ከመከራ የማይማር ህዝብ የሆነው? በአለም ዙሪያ ያሉ ማህበረሰቦች አንድ ችግር ደህና አድርጎ ከደቆሳቸው በኋላ ሁለተኛ እንዳይደግማቸው ችግሩን መማሪያ አድርገው መፍትሔ ሲያበጁለት እናያለን። እኛ ተመሳሳይ ችግር እየደጋገመ ሲመታን ዝም ብለን የምንቀጥለው ለምንድነው? ችጋር ህዝባችንን በየጊዜው እየተመላለሰ የቀጠቀጠው ከመጀመሪያው እልቂት መማር ስለተሳነን አይደል? ለመሆኑ ሰደት በተስቦ (epidemic) ደረጃ በሀገራችን እንዲሰፍን ያደረገው መሰረታዊ መንስዔ ምንድነው? መፍትሔውስ? በኔ እምነት ብርቱ ህዝብነታችን የሚለካው ለነዚህ ጥያቄዎች የሚያዋጣ መልስ ፈልገን ስናገኝ ነው። ብዙ ህዝቦች መጥፎ አጋጣሚን ወደ ዘላቂ ችግር መፍቻ ዕድል (opportunity) ይቀይሩታል። እኛ ብዙ ተመሳሳይ ነገር እያጋጠመን አበላሽተነዋል። ይህንንም በቅርቡ የደረሰብንን ውርደትና ሀዘን ባናበለሸው ጥሩ ነው። ኢትዮጵያ በርሀብተኛነት ከደረሰባት የገጽታ ብልሽት ባልተናነሰ በስደተኛ ህዝብ ሀገርነትም ገጽታዋ ክፉኛ እየተበላሸ ነው።
ባለንበት ዘመን ስደት በብዙ ሀገሮች አዲስ ነገር አይደለም። የብዙ ሀገር ሰዎች ወደሌላ ሀገር ይሰደዳሉ። የስደቱ ዓይነትና መጠን ግን በጅጉ ይለያያል። የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም በቅርቡ ባንድ ክርክር ላይ የኛውን ችግር ለማቅለል በሚመስል መንገድ ስደት አሜሪካኖችም ይሰደዳሉ ሲሉ ሰምቻለሁ። የሰዎችን ከሀገር ሀገር መጓዝና መኖር ሁሉ ስደት በሚል ስም በመጥራት አንድ ለማድረግ መሞከር አሜሪካኖች እንደሚሉት አፕልና ኦሬንጅ ማደባለቅ ነው። ስደት ሁሉ አንድ አይነት አይደለም። ቢያንስ የብዙ ሀገሮች ስደተኞች እንደኛው ሀገር ሞትና ህይወት ሀምሳ/ሀምሳ ሰጥተው የሚጓዙበትና የሚዋረዱበት አይነት አይደለም። የኛ ስደት በመጠንም በዓይነትም ብዙ ተወዳዳሪ የሌለው በጅጉ አደገኛና አዋራጅ ነው። ከሳውዲ አረቢያ ዜጎቻችን በዚያ ቁጥርና ጊዜ ውስጥ የተባረሩበት ሁኔታ በአለም ላይ ተወዳደሪ የሌለው ሬኮርድ ነው። የኛ ሀገር ስደት ስር የሰደደ የክፉ ችግር ምልክት ነው። “ስደት በሁሉም ሀገር አለ” በሚል መሸንገያ ራሳችንን ማታለል አንችልም። ከዚህ ቀደም ጋለፕ (Gallup) የተባለ የህዝብ አስተያየት ተመራማሪና አጥኚ ተቋም በኢትዮጵያ መሰደድ የሚፈልገው ወጣት 46% እንደሚሆን ነግሮን ነበር። ለዝርዘሩ (ይህን ይመልከቱ)። ከሀገራችን ወጣት እኩሌታው ያህል ስደትን የሚመኝ መሆኑን ስናይ ሀገሪቱ ላይ እንድ ትልቅ ህመም እንዳለ አለመገንዘብ ሞኝኘት ነው። ከላይ እንዳልኩት የኛ ስደት በወረርሽኝ (epidemic) ደረጃ ላይ ያለ ነው። የሚሰደደው ሁሉም አይነት ሰው ነው። የተማረ ፣ ያልተማረ ፣ ባለስልጣንና ስልጣን የሌለው ሁሉ የሰደዳል። ከሰው ጋር ሀገሪቱ በጥረት የምታገኘው የውጭ ምንዛሪ ሁሉ ከሀገር ሲወጣም እያየን ነው። እኤአ ከ2000 እስክ 2009 ባለው ጊዜ ውስጥ 11.7 ቢሊዮን ዶላር ሀገር ጥሎ መውጣቱ ተነግሮናል (ይህን ይመልከቱ)። ይህ ለኛ አይነት ድህነት ለሚፈነጭበት ሀገር ቀላል ኪሳራ አይደለም። ይህ ሀገር ውስጥ ያለ ሁሉ ወደ ውጭ ይበልጥ ሲያይ የሚመጣ ነገር ነው። አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የፈረንጅ ስም የወጣላቸውን ሆቴሎች ፣ የቁርስ ቤቶች ፣ መዋዕለ ህጻናትና ሌሎች ተቋሞችን ልብ ብሎ ላየ ከተማዋ ራሷ እዚያው ሆና የተሰደደች ትመስላለች ። የስኬት (Success) መለኪያችን ራሳችንን ትተን ውጭ ሀገር መምሰል ሲጀምር ነው ስደት ባህል መሆኑን የምንረዳው። ይህ ፈጽሞ የጤነኛ ሀገርነት ምልክት አይደለም። የመዘዘኛ መጭ ጊዜ ጠቋሚ እንጂ።
በኔ እምነት አደገኛ ሰደትንና ሀገራችንን ያንፈራጠጠባትን ባለብዙ ፈርጅ ችግር ማሰወገድ የሚቻለው በስፋት የሚተባበር መንግስትና ህዝብ መፍጠር የሚቻልበት ሁኔታ ሲኖር ፣ ሐገሪቱ ለዜጎቿ የምታጓጓ (Attractive) ሀገር ስትሆንና የተረጋጋ ህይወትም ሊኖርባት የምትችል ሀገር ካደረግናት ብቻ ነው። የሃሳቤ ማጠንጠኛ ይህ ነው። ያንድ ሀገር ሰዎች የፖለቲካና የሀሳብ ልዩነትን ሁሉ የጠላትነት ግንኙነት እያደረግን እስከወሰድን ድረስ መከራችን የሚያባራበት ጊዜ አይኖርም። በተለይ የሀገሪቱ ልሂቃን የህዝቡና የሀገር ጥቅም ላይ የማንስማማ ከሆነ የፈረሰ ሀገር ላይ ለመኖር እንደወሰንን ይቆጠራል። የማይስማሙ ሰዎች አጥፊና ጠፊ ሳይሆኑ የሚኖሩበት ስርዓት ካልገነባን የሀገሪቱ ችግር ፈች ሁሉ ስደተኛ ወይም አመጸኛ ነው የሚሆነው። ባለንበት ዘመን ወጣትና የተማረ የሰው ሀይል ለስደት እየገበሩ ፣ በዜግነቱ የማይተማመንና የማይመካ ዜጋ እያበራከቱ ሀገር እገነባለሁ ህዝብ ከድህነት አወጣለሁ ማለት ደግሞ ከንቱ ወሬ ነው። ይህ ብቻም አይደለም። ማንኛውም ችግር አድጎ አድጎ የመጨረሻ የመገንፈል ደረጃ ላይ ይደርሳል። ያን ጊዜ ደግሞ መፍትሔ ለማግኘት በጣም ይመሻል። ከመሸ በኋላ ችግር ሊፈቱ የሞከሩ ሀገሮች የደረሰባቸውን ደግሞ አይተናል።
ከማርክሳዊ አስተሳሰብ ጋር የወሰድነውና ያልለቀቀን የፖለቲካ “መስመር” የሚባል ግንዛቤና በዚያ መስመር ላይ ያልተሰለፈ ሁሉ እንደ ጠላት ወይም አንድ ቀን ሊያጠቃን እያደባ እንደተቀመጠ ጠላት አደርጎ የመቁጠር ፖለቲካ ኋላ ቀርና መቆም ያለበት ነው። ትንሽና ብዙ ጉዳት የማያስከትሉ ተቃውሞ ያሰሙና ትችት የሰነዘሩ ሰዎችን ሁሉ ማሰር ማዋከብና መጉዳት የሚመጣው በዚህ ብልሹ አስተሳሰብ ምክንያት ነው። ችግራችንን ለመቋቋም ከልብ ከወሰንን የማንስማማ ሰዎች ሆነንም እዚች አገር ላይ ሳንጠፋፋ አብረን ለመኖር ፈቃደኞች መሆን ይኖርብናል።
አሁን ይታያል የሚባለው መንግስትም የሚመካበት የኢኮኖሚ እድገት ብዙሃኑን ተጠቃሚ ማድረግ ቀርቶ ተስፋ እንኳን መፍጠር አልቻለም። የምንሰደድበት ቁጥርና አይነት የሚመሰክረው ይህንን ነው። አልጀዚራ ድረ ገጽ ላይ በቅርቡ ይህን የታዘበ ጽሁፍ አይቼ ነበር። እንዲህ ይላል – “If Ethiopia is so vibrant, why are young people leaving? “ኢትዮጵያ በጥሩ ሁኔታ እየለማች ከሆነ ወጣቶቿ ለምን የሰደዳሉ? ዝርዝሩንና የሰጠውን መልስ (እዚህ ይመልከቱት)። ያሁኑ የኢኮኖሚ ዕድገት መጠንና ፍጥነት የሚባለውን ያህል ይሁንም አይሁን ካለብን ችግር ጋር የሚመጣጠን ካለመሆኑም በላይ ቀጣይ (sustainable) መሆኑ አጠራጣሪ ነው። አሁንም በብዙ መንገድ በርዳታ ከመኖር ያልተላቀቅን ሀገር ነን። ይህ ርዳታም ቀጣይ መሆኑ አጠራጣሪ ነው። ሀገሪቱ ላይ በስፋት የሚካሄዱት እንደ መንገድና ህንጻ ኮንስትራክሽን ያሉት ኢንቨስትሜንቶች በራሳቸው ሌላ ሀብት ፈጣሪ (wealth creator) አይደሉም። ሀብት ፈጣሪ ኢንዱስትሪ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የሚያዋጣው ድርሻ ገና 12% አካባቢ ነው። ማዕድን ማውጣትና ጥሬ ሀብትን ወደ ሸቀጥነት የሚለውጡ ኢንቨስትሜንቶች በችግራችን መጠን እያደጉ አይደለም። አሁን እየተመዘገበ ነው የሚባለው እድገት ፍጥነቱም ብዛቱም በዝቅተኛ የኢኮኖሚ ወለል ላይ ከመሆናችን ጋር እየተለካ እንጂ የምናፈራው ሀብት ብዙ ስለሆነ አይደለም። እንደ ኢትዮጵያ ያለ ድሀ አገር በ 10% አድጎ የሚያገኘው ሀብት ትንሽ የዳበሩ ሀገሮች በ 1% እደገት የሚያገኙት ሀብት መጠን አጠገብ በሩቁ እንኳን የሚጠጋ አይደለም። የእድገት አሀዝ እየጠቀሱ ራስንም ሌሎችንም ረጅም ጊዜ ማታለል አይቻልም። በያመቱ ብዙ ተማሪዎች ከኮሌጅ ማስመረቅን እንደ ጥሩ ነገር ማውራት ይቻላል። ጥሩ ነገርም ነው። ምሩቃኑ ራሳቸውንም ሀገርንም የሚጠቅም ስራ ካልሰሩ የወጣባቸው ገንዘብ ሁሉ የሀገር ኪሳራ ነው። በዚህ ቁጥር መኩራራት ከግርጌው የተሸነቆረን በርሜል ውሀ ለመሙላት ስንት ጣሳ ውሀ እንደተጠቀምን ከመቁጠር አይለይም። ስደትን ማቆሚያው ዋና ዘዴ ሰዎችን በበቂ የሚያኖር ስራ መፍጠር ነው። ባለሞያዎች እንደሚነግሩን ባለንበት እንኳን ለመሄድ በየዓመቱ ከሁለት ሚሊዮን ተኩል ያላነሱ ስራዎች ሀገሪቱ ውስጥ መፈጠር አለባቸው። ባጭር አነጋገር ብዙ የሀገሪቱ ሶሺዎ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ሁኔታዎች ዙሪያቸው አያምርም።
የስደታችን መሰረታዊ መንስዔዎች ምንድን ናቸው?
መፍትሔ ፍለጋ ላይ ብዙ ጊዜ የምንሳሳተው የችግሩን መንስዔ አንድ ብቸኛ ምክንያት ላይ ልንደፈድፈው ስንሞክር የመስለኛል። ብዙ ይህን ጥያቄ የማነሳላቸው ወንድም እህቶች የችግሩ ምክንያት መንግስታችን የሚከተለው አካሄድና ፖሊሲ ነው ይላሉ። በኔ እምነት ይህ ከችግሩ አንዱ ምናልባትም ዋነኛው ቢሆን እንጂ ሁሉም አይመስለኝም። የስደት ችግራችን ባለብዙ ምክንያት (multivariate) ይመስለኛል። ችግሩን የምንረዳውም የምንቀይረውም ክፍት አእምሮ ይዞ በመመርመርና እንደማህበረሰብ ውስጣችን የተዋቀሩ የኑሮ ዘይቤዎችን በመረዳት ነው።
ስለስደት ስንነጋገር ስለየትኛው አይነት ስደት እንደምንነጋገር መለየት ይኖርብናል። ስደት አለም አቀፍ ጉዳይ ከሆነ ስለቆየ ሙሉ ለሙሉ ማስቆም አይቻልም። እንዲቆም የምንፈልገው በወረርሽኝ (Epidemic) ደረጃ ያለውንና ዛሬ በኛ ሀገር ያለውን አይነት አደገኛውንና አዋራጁን ብቻ ነው። ሀገሪቱ በድህነቷ ለፍታ ያፈራችውንና ለወደፊቱ በዓለም ተወዳዳሪ ሊያደርጋት የሚችለውን የተማረ የሰው ሀይል እንዳይሰደድ ማድረግም ለዕድል የማይተው ነገር ነው።
ለስደት “ገፊ” ና “ሳቢ” ምክንያቶች (Push and Pull factors) አሉት። ችግሩን የምናገኘው እነዚህን ገፊና ሳቢ የስደት ምክንያቶቻችና ሁለቱ በኢትዮጵያ ያላቸውን መስተጋብር ጠንቅቀን ስናውቅ ነው። ይህ ጠለቅ ባለ ጥናት ብቻ ሊተነተን የሚችል ነው። እኔ እዚህ የምሰጠው አስተያየት ለመነሻ የሚሆን ግርድፍ ዕይት ብቻ ነው።
በግርድፉ የሚከተሉት ነገሮች ከኛ ሀገር ጋር የተያያዙ ዋና የስደት ምክንያቶች ተብለው ይቆጠራሉ።
1. አሀዛዊ መለኪያ አስቀምጠን መመጠን ባንችልም ትልቁ የሀገራችን ገፊ የስደት ምክንያት ድህነት ነው። ድህነትም ከተስፋ ጋር ካለ በራሱ ገፊ ምክንያት ላይሆን ይችላል። ሰዎች ቀያቸውን ትተው የሚሰደዱት ተስፋ ሲቆርጡ ነው። ነገ የተሻለ ቀን የሚመጣ ከመሰላቸው ላይሰደዱ ይችላሉ ማለት ነው። በኛ ሀገር ለብዙሃኑ በተለይ ለወጣቶች የተስፋ ጭላንጭል የማይታይበት የድህነት ጨለማ ነግሷል። ስራ አጥነት በተለይ በወጣቶች ዘንድ ትልቁ የስደት ምክንያት መሆኑን ብዙዎቻችን እናውቃለን። ለአመታት ተምረው ስራ ያጡ ወጣቶች ስራ ማጣት ብቻ ሳይሆን ምንም ሰርተው ያልፍልናል ብለው መገመት ሲያቅታቸው ስደቱ የሚያመጣውን አደጋ ሁሉ ለመቀበል ተዘጋጅተው የሚገቡበት ብዙ ናቸው። ሞትና ህይወትን አማራጭ አስቀምጠው የሚሰደዱት ወገኖቻችን በሀገራቸው ፍጹም ተስፋ የቆረጡት ናቸው። በቅርቡ በሊቢያ ለአሰቃቂ አደጋ የተዳረጉት ውንድሞቻችንና እሁን በሞትና ህይወት መሀል የሚገኙት ሊቢያና የመን ያሉት ስደተኞች ብዙዎቹ እነዚህ ይመስሉኛል።
2. የህግ የበላይነት ባልሰፈነበትና ህግ መከታ ይሆነኛል ብሎ የማይተማመን የፖለቲካ ተቃዋሚም ሆነ ከመንግስት የተለየ አስተያየት ስላለኝ በመንግስት እጠቃለሁ ብሎ የሚፈራ ሰው አንዱ ዋና ምርጫው ስደት ነው። ህግ ሊያስጥለኝ ይችላል ብለው ባለመተማመን ብቻ ሀገርም ህዝብም ባልጎዱበት ምክንያት የተሰደዱ ብዙ ኢትዮጵያውያን እናውቃለን።
3. አንዳንድ ወጣቶች ምንም ብንማር እንኳን መንግስት የሚያካሂደውን ለፖለቲካ ታማኞቹ ቅድሚያ የመስጠት መድሎ ማለፍ አስቸጋሪ ነው እያሉ ሲናገሩ በተደጋጋሚ ይሰማል። መጠኑን ባላውቀውም እንዲህ አይነት አሰራር ለብዙ ወጣቶች ተስፋ መቁረጥ ምክንያት እንደሚሆን ጥርጥር የለውም። እንዲህ አይነት መድሎ የሀገር ባለቤትነት ስሜትን ያጠፋል። እንደኛ ሀገር መንግስት ዋናው ስራ ቀጣሪ በሆነበትና የግል ከፍለ ኢኮኖሚ ድርሻ በጣም ዝቅተኛ በሆነበት ሀገር ደግሞ ይህ ከባድ ገፊ የስደት ምክንያት ነው።
4. ሀገራችን በብሄረሰቦች ክልል መከፋፈሏና ከሱ ጋር ተያይዞ የዳበረው ክልሉ ያካባቢው ቋንቋ ተናጋሪ ብቻ ነው የሚለው አስተሳሰብ ዜጎች ሀገራቸው ውስጥ እንደልባቸው ተዘዋውረው የተሻለ ህይወት ለመፈለግ አይበረታቱም። እንደምንሰማው እንዱ ሌላ ክልል ሲገባ ብዙ የዜግነት መብቶቹን ሁሉ ማጣት ብቻ ሳይሆን ባዕድ ነኝ የሚል ፍርሀትና ሀብት አፍርቶ ተረጋግቶ መኖር የማይቻል ስለሚመስለው ከዚህ ሁሉ ከሀገር ወጥቼ እድሌን ልሞክር ወደሚል አስተሳሰብ ይገፋፋል።
5. በሀገራችን ብዙውን ሰው በሚያስተዳድረው የሚታረስ መሬት ላይ በየጊዜው በሚጨምረው የህዝብ ቁጥር ምክንያት ያንድ ሰው ይዞታ እያነሰ በመሄድ ላይ ይገኛል። ይህም ብዙ የገጠር ነዋሪዎች ወደ ተጣበበው ከተማና ከዚያም አልፈው ወደ ውጭ መሰደድን እንዲመርጡ አድርጓቸዋል። በዚህ ላይ የመሬት ይዞታ ባለቤትነት ርግጠኝነት ስለሌለ ብዙ ገበሬዎች የመሬቱ ይዞታ ቢያንስም ምርታማ ለማድረግ እንዲበረቱ አያደፋፍራቸውም።
6. ሌላው ገፊ ምክንያት ባካባቢ እርስ በርስ ግጭት ወይም ከመንግስት ጋር በሚደረግ የታጠቀ ግጭት በሚደርስ ህይወትና ንብረት ውድመት የአካባቢ ለመኖሪያ አለመመቸት ወይም አደገኛነት የሚከሰተው ነው። ኦጋዴን አካባቢ ያለው ይህ ይመስለኛል።
7. የመንግስት የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ሌላ ምክንያቶች መሆናቸውንም እንሰማለን። ለምሳሌ ከጋምቤላ አካባቢ መንግስት በተከተላቸው መሬት አፈናቃይ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ምክንያት ያካባቢው ነዋሪዎች ከቀያቸው መፈናቀላቸውንና ወደ ጎረቤት ሀገር መሰደዳቸውንም እንሰማለን።
8. ብዙ ሰዎች ለወደፊቱ ረጅም ዘመን ሀገሪቱ አስተማማኝ መሰረት ላይ ነች ብለው አያምኑም። ነገ አለመረጋጋትና ችግር ሊመጣ ይችላል ብለው የሚፈሩ ሀብታሞች ሳይቀሩ ልጆቻቸውን ስደት ይልካሉ። ልጆቻቸው የሌላ ሀገር ዜግነት እንዲያገኙ ሚስቶቻቸውን ሌላ ሀገር እንዲወልዱ ያደርጋሉ። ገንዘባቸውንም ወደ ውጭ ያሸሻሉ። ይህ ስልጣን ላይ ያሉ ሰዎችንም የሚጨምር የስደት ዓይነት እንደሆነ በሰፊው ይነገራል።
9. በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ባንጻራዊ ደረጃ ያገኙት የተሻለ ኑሮና ሀብት ለብዙዎች ላልተሰደዱ ወገኖች በሞዴልነት ያገለግላል። ውጭ ሀገር በመኖር ባገኙት ዕድል ወዳጅ ዘመድ ሲረዱ የሚታዩ ወጣቶች ለብዙ ችግሩ ላልባሰባቸው ወጣቶች ሁሉ ሳይቀር አርዓያ የመሆን ባህሪ እንዳላቸው ይገመታል። ይህ የስደት “ሳቢ” ምክንያት ካልነው ውስጥ የሚመደብ ነው።
10. ብዙ ወጣቶች በደፈናው ፈረንጅ ሀገር ተሰዶ መኖር የላቀ ስብዕና የሚጨምርላቸው ይመስላቸዋል። ምዕራብ ሀገር ተሰዶ መኖርን እንደ ህይወት ስኬት ይመለከቱታል። ሀገር ቤት ቢያንስ ጀማሪ የንግድ ተቋም ለማስጀመር የሚችል ወጭ እያወጡ የሚሰደዱ አሉ። የነዚህ የስደት ምክንያት ችግር የፈጠረው ነው ማለት አይቻልም።
በኔ አተያይ እነዚህ ከላይ ያነሳኋቸው ምክንያቶች በተናጠል ወይም ተደራርበው የስደት ችግራችንን መጠንና አደገኝነት ያገዘፉት ይመስለኛል።
የችግሩ የመፍትሄ መጀመሪያ ሀገሪቱ ውስጥ ፖለቲካዊ ዕርቅና መረጋጋት ማስፈን ነው
ከላይ እንዳነሳሁት ብዙዎቹ የመፍትሔ መንገዶች ቁርጠኛ የፖለቲካ ፈቃደኝነትና ውሳኔ የሚጠይቁ ናቸው። በተለይ የሰላምና ዕርቅ መንገድ ከራስ በላይ ለሀገራዊ ጥቅም ቅድሚያ መስጠትን ይጠይቃል። ዕርቅ የሚያጓጓና የሚፈለግ እንዲሆን የፖለቲካ ተቀናቃኝና ታራቂ ወገኖች የሚያገኙት ጥቅምም መኖሩን ማረጋገጥ ያሻል። ከሁሉ በላይ ደግሞ የሰላምና ዕርቅን አካሄድ መከተል አደገኛ ከሆነ የሀይል መፍትሄ አካሄድ ሊመጣ የሚችለውን አደጋ ማስቀረት መሆኑ ሊገባን ይገባል። በህዝባዊና የታጠቀ አመጽ ከሚመጣ ለውጥ በተለይ ገዥዎች ሁሉንም ነገር ነው የሚያጡት። ስልጡኑና አውሬያዊ ያልሆነው መንገድ ስልጣን ላይ ያሉትም ተቃዋሚዎቹም ያልለመዱትን ትብብር ለመፍጠር ማግባቢያ (Incentive) የሚሆን ለሁሉም ወገን እንዲኖር ማድረግ ይመስለኛል። ለመንግስትም ለህዝብም እንድ ቀን ብዙ ሂሳብ የሚያስከፍለውን አስገዳጅ መፍትሄ በግድ ከመቀበል የተወሰኑ ነገሮችን እጥቶ ዋናውን ነገር ማስቀረት በጅጉ ይመረጣል። የሰሜን አፍሪካና እንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች መሪዎችና ልሂቃን ይህን በጊዜ ባለማድረጋቸው ነው ራሳቸውንም ሀገራቸውንም ቀውስ ላይ የጣሉት።
እዚህ እንደ መፍትሔ የማቀርበው ሀሳብ የየዋህ ሀሳብ ሊመስል ይችላል። ራስ ወዳድነትን ፣ ስልጣን ወዳድነትንና ለስልጣን መግደልንና መሞትን ማየት የለመደ ህብረተሰብ ውስጥ ይህ ሀሳብ የዋህነት መምሰሉ አያስገርምም። ችግሩን እንደ ህልውና ችግር አድርጎ ለሚመለከትና ሁሉም ወገን አሸናፊ የሚሆንበትን መንገድ ጠቁሞ መፍትሔ ማበጀት የዋህነት አይደለም። የዋሆቹ ችግሩ የማይደርስ መስሏቸው ራሳቸውን የሚያታልሉት ናቸው። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሀይሎች አሁን ባሉበት መንገድ ከቀጠሉ ችግሩ እየባሰ መሄዱ የሚቀር አይመስለኝም። በመሸናነፍና መንግስትን በሀይል በመለወጥ ችግሩ የሚሻሻል ከሆነም መጀመሪያ ተባብሶና ብዙ ቀውስ ፈጥሮ ነው የሚሆነው። ከሁላችንም ወገን በተለይ መንግስት ከሚመራው ኢሕአዴግ በኩል ችግሩን ለመፍታት የሚበጅ የፖለቲካ ፈቃደኝነት ከሌለ ሁላችንም አደገኛ ጥግ ውስጥ ነን።
መንግስት ስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ ቢያንስ ስልጣኔን በሐይል ለመቀናቀን በቂ አቅም ያለው የፖለቲካ ድርጅትም ሆነ ስብስብ በሌለበት ሁኔታ ወደ እርቅና ሰላም ድርድር ውስጥ መግባት አያስፈልገኝም ብሎ ሊያስብ እንደሚችል መገመት አያደግትም። እስካሁንም የቀረቡ የሰላምና ዕርቅ ጥያቄዎችን ያልተቀበለው አቀበላለሁ ሲልም በኔ መንገድ ብቻ የሚለው በዚህ ምክንያት ይመስለኛል። የመጀመሪያ የሰላምና ዕርቅ ሙከራ ከተደረገባቸው አመታት ይልቅ አሁን ጥያቄውን ትልቅ ቦታ የሚሰጡት የተለዩ ሁኔታዎች የተፈጠሩ ይመስለኛል። ዛሬ ገዥው ሀይል ሊፈራቸውም የሚገባ ሁኔታዎች ይበልጥ ይታያሉ። ከዚህ አካሄድ ብዙ እንደሚጠቀም የሚያሳዩት ምልክቶችም ብዙ ናቸው። የሰላምና ዕርቅ መንገድ በታሪክ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው ተግባር ከመሆን በዘለለ በሀይል ከስልጣን ከመውረድ ጋር ተያይዞ ከሚመጣው እስከ ልጆችና የልጅ ልጆች ድረስ ከሚጎዳ ነገርም ይታደጋል። መንግስትን የሚመሩና የሚደግፉ ሁሉ የሚከተሉትን ልብ ሊሉ ይገባል።
1. አሁን ያለው የድህነትና የሩሮ ውድነት ሁኔታ እየተባባሰ እንደሚሄድ የሚያመለክቱ ጠቋሚዎች በብዛት አሉ። ኢኮኖሚው አሁን ያለበት አቅጣጫ የሚያሳየው ይህንን ነው። የሚቆጣ ህዝብ ብዛት በአይነትም በቁጥርም እየጨመረ መሄዱ አይቀርም። ይህ ቁጣ በማንኛውም ማህበረሰብ ውስጥ እንደምናየው ዓይነት ሀገር ለመናጥና መንግስት ለማናወጥ የሚችል ሀይል (critical mass) አንድ ወቅት ላይ ማፍራቱ አይቀርም። የዛሬው ዝምታ ያቺ ወሳኝ ምዕረፍ መድረሻዋን እየጠበቀች መሆኑን ብቻ ነው ሊነግረን የሚችለው። ይህን ሰፊ የህዝብ መነሳሳት በጉልበት ለማቆም ከባድ ይሆናል። ቢሞከርም ትርፉ ታሪክ ይቅር የማይለው ጥፋት ማድረስ ብቻ ነው።
2. ዘመኑ የኢንፎርሜሽን ዘመን ነው። ህዝቡን ለማነሳሳትና ለማደራጀት እያንዳንዱ ቤት ሊገባ የሚችል ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክ መሳሪያ በብዛት አለ። የሳትላይት ቴሌቪዥኖች ሬዲዮዎችና የኢንተርኔት መስመሮች ህዝብ መቀስቀሻም ማደራጃም መሆናቸው የማይቀር ነው። እነዚህ ነገሮች ህዝቡን ከማነሳሳት አልፈው ጉልበት ሊፈጥሩለት (Empower ሊያደርጉት) ሁሉ ይችላሉ።
3. ገዥው ፓርቲ አሁን በፍጥነት እያደገ ነው በሚባለው ኢኮኖሚ ህዝቡን አማልላለሁ ብሎ አስቦም ከሆነ እንደማይቻል ካሁኑ እየታየ መሆኑ ግልጽ ነው። አንደኛ ነገር የኢኮኖሚ እድገት ፍጥነትና መጠን አንድ አይነት ነገር አይደለም። ስለዕድገት ብዙ እየተወራ ቢሆንም የኢኮኖሚውን እድገት ውጤት ባብዛኛው ህዝብ የቤት ውስጥ ኑሮ ላይ ሊንጸባረቅ አለመቻሉ የሚፈጥረው የምሬት ስሜት እየጨመረ በመሄድ ላይ ነው። ሐገሪቱ ላይ ለውጥ እንዳለ ቢመለከትም ብዙው ራሱን የጥቂት በዪዎች ተመልካች አድርጎ ነው የሚቆጥረው። ይህ ዛሬ እያየነው ያለና በፕሮፓጋንዳና የህዝብ ግንኙነት ስራ ሊለወጥ የማይችል ነው።
4. በሀገራችን ሙስናና ንቅዘት በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ላይ መሆኑን ብዙ ሰዎች የሚመሰክሩት ነው። በቅርቡ እንድ ወዳጄ የመንግስት ግብር በሰአቱ ለማስገባት ግለሰቦች ጉቦ አስከመስጠት መድረሳቸውን አጫውቶኛል። ይህ ከመንግስት አሰራር ቅልጥፍና ተፈጥሮአዊ ጉድለት (ineficiency) ጋር ተያይዞ በህዝቡ ውስጥ ምሬት እየፈጠረ በመሄድ ላይ መሆኑን ልብ ይሏል። የህዝቡ ማጉረምረም ጮክ ብሎ አልተሰማ ከሆነ በፍርሀት ምክንያት እንጂ ችግር ስለሌለ አለመሆኑን ማወቅ ብልህነት ነው።
5. በብዙ መረጃና አንዳንድ ጊዜም በምናበ እይታ (perception) ደረጃ ሀገሪቱን ያንድ ብሄረሰብ ልሂቅ መጠቀሚያ ሆናለች ሲባል የምንሰማው ያደባባይ ሀሜት አንድምታውም መዘዙም ቀላል አይደለም። በየማህበራዊ መገናኛ ብዙሃኑ የጥላቻ የመጠቃትና ይቁጭት አስተያየት ሲሰነዘር መስማት የተለመደ ሆኗል። ይህንን ጥላቻ መጥፎ ነገር ነው በማለት ብቻ ወይም ይህ አመለካከት ያላቸውን ሰዎች በማናናቅ እንዲቆም ማድረግ አይቻልም። ይህን የሚሉት ደግሞ ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆኑ አለማቀፍ ተደማጭነት ያላቸው ተቋሞች ሁሉ ናቸው። ፍሪደም ሀውስ የተባለው ተቋም ለምሳሌ በዘንድሮው ሪፖርቱ እንዲህ ይላል። “The government tends to favor Tigrayan ethnic interests in economic and political matters, and the EPRDF is dominated by the Tigrayan People’s Liberation Front”. ለዝርዝሩ (ይህን ይመልከቱ)። ዘ ኢኮኖሚስት የሚባለው ታዋቂ መጽሄትም በቅርብ ጊዜ እትሙ እንዲህ ብሎ ነበር። “.. ethnic Tigrayans, of whom Meles was one, still control the army, security services, telecoms and foreign affairs”. (ይህን ይመልከቱ)። በእንደኛ አይነት ሀገሮች እንዲህ አይነት አስተሳሰብ የሚያመጣውን መዘዝ አይተናል። ይህን ሁላችንም በተለይ የመንግስት ስልጣን የሚያክልን ነገር የያዙ ሰዎች ሊፈሩና ሊጨነቁ ይገባል።
6. ብዙ ጠቋሚዎች እንደሚያመለክቱት በሀገራችን የመንግስት ፍራቻና ጥላቻ እየጨመረ ነው። የህግ አስተዳደር (Rule of law) ላይ ብዙ ሰው ተስፋ እየቆረጠ ነው። የመከፋቱ ደረጃ የሰላማዊም ይሁን የሀይል አማራጭ ለመረጡ የፖለቲክ ሀይሎች ትልቅ ድጋፍ መሰብሰቢያ መሳሪያ ሆኖ ማገልገሉ የማይቀር ነው። ጋዜጠኞችን በማሰር ከአፍሪካ አንደኛ ሆናችኋል ሲባልና በእስር ላይ ባሉ ዜጎች ላይ ይፈጸማል እየተባለ ስለምንሰማው ስቃይ (ቶርቸር) ሲሰሙ የመንግስት ባለስልጣኖች ብዙ የጥፋት ርቀት እንደተጓዙ የተገነዘቡ አይመስሉም። በዚህ ዓመት (2015) የወጣው የፍሪደም ሀውስ ሪፖርት ኢትዮጵያ ከሰሃራ በታች ካሉ 49 ያፍሪካ ሀገሮች በሰብዓዊ መብት ይዞታዋና በሲቪል ነጻነት 43ኛ ሆና ተመዝግባለች። አለማቀፍ መህበረሰብም ይህን ስዕል እያየ ትዕግስት እያጣ በመሄድ ላይ ያለ ይመስላል። ይህ አስተያየት የኢትዮጵያን መንግስት ገላጭ አስተያየት (narative) እየሆነ በመሄድ ላይ ይገኛል።
7. በየጎረቤት ሀገሩ ያሉ ችግሩን በሀይል እንፈታለን ብለው የተነሱ ሀይሎች በቀላሉ ድጋፍ ሊፈጥርላቸው የሚችል ምሬትና ሊደግፋቸው ወይም ሊቀላቀላቸው የሚፈልግ ህዝብ በተለይ ወጣት በብዛት መኖሩን መንግስት እንደ አደጋ ሊያየው ይገባል። ሞትና ህይወት እኩል ዕድል ባለበት ሁኔታ ውስጥ ስደትን የሚመርጥ ወጣት መንግስትን ተዋግቼ አውርጄ የተሻለ ቀን አመጣለሁ ብሎ እንዲያምን ከተደረገ አይኑን ሳያሽ ሊገባበት ይችላል። ከ 30 ዓመት ዕድሜ በታች ያለው ወጣት ከሀገሪቱ ሕዝብ 70 በመቶ መሆኑን ደሞ ልብ ይሏል። ጥያቄው በዚህ ፍልሚያ ማን ያሸንፋል የሚል አይደለም። ይልቁን በግጭት መጠመድ በራሱ የሚያስከትለውን ድቀት ነው አብዝቶ ማጤን።
8. ኢሕአዴግ ስልጣን ላይ ሩብ ምዕተ ዓመት ቆይቷል። ይህ ረጅም የስልጣን ዘመን ነው። አሁን ያሉት ባለስልጣኖች የሰሯትን ስራ ሁሉ ከቀድሞ ገዥዎች ጋር እያወዳደሩ ለመመጻደቅ የሚመች አይደለም። አብዛኛው አሁን በኢትዮጵያ የሚኖረው ህዝብ የደርግን ዘመን እንኩዋን በቅጡ አያውቅም። የኢሕአዴግ አካሔድ አስቀድሞ የሚታወቅ (predictable) ሆኗል። ካሁን በኋላ እያደገ ሳይሆን እየደከመና እየተሰለቸ ለውጥና አዲስ ነገር ለመሞከር የሚፈልገው ህዝብ ቁጥር እየጨመረ መሄዱ አይቀርም። ፍጹም ነጻ የሆነ ምርጫ በኢትዮጵያ ዛሬ ቢካሄድ ኢህአዴግ ማሸነፍ የሚችልበት ሁኔታ የለም።
ሰሞኑን የተካሄደው አይነት ፍጹም አሳፋሪና አግላይ (Exclusionary) ምርጫ ለጊዜው ለገዥው ፓርቲ ጊዜያዊ የቁጥጥር ጉልበት ያሳይ እንደሆን እንጂ የህዝብን ዘላቂ ፈቃደኝነት የሚያሳይ አይደለም። የምርጫው አሰራርና ውጤቱ በተለይ አንድ ላምስት የሚባለው ቀፋፊ አሰራር ከመካከለኛው ዘመን የባሪያ ፍንገላ ዘዴዎች ብዙም አይለይም። የዘንድሮ ምርጫ በተለይ ውጤቱ የጠቀመው ካለ ይህን መንግስት በሀይል ከማስወገድ ውጭ አማራጭ የለም ለሚሉ ሀይሎች ነው። በዚህ የምርጫ ውጤት ብዙ ነገር ያጣ ካለ አሸነፍኩ ያለን ገዥ ፓርቲ እንጂ ሌላ ማንም አይደለም። ሌላው ቀርቶ ወዳጅና ለጋሽ ተባባሪ ሀገሮች አፍንጫቸውን ይዘው እንኳን ለመቀበል እያንገዳገዳቸው መሆኑን እያየን ነው።
በነዚህና በሌሎችም ብዙ ምክንያቶች ገዥው ፓርቲ አስካሁን የያዝኩት መንገድ የጎላ ማሻሻያ ሳላደርግ ካለእክልና አደጋ መቀጠል እችላለሁ ብሎ ካሰበ ራሱንም የሚጎዳ ትልቅ ስህተት ነው የሚሰራው። በተለይ መሪዎቹ ለልጅ የልጅ ልጆቻቸው የሚተርፍ ችግር ነው ትተው የሚሄዱት። በመሆኑም በሰላምና ዕርቅ መንገድ ብዙ ነገሮችን የሚያተርፍ ካለ በስልጣን ላይ ያሉት ናቸው። ከላይ ባነሳኋቸው ምክንያቶች እንዴውም ገዥው የፖለቲካ ሀይል ለዕርቅና ዕርቅ ለሚፈጥራቸው ሪፎርሞች ከተቃዋሚዎቹ ያልተናነሰ ፍላጎት ሊኖረው ይገባል። ፖለቲካዊ አቅማቸው ምን ያህል እንደሆነ ባይታወቅም ቢያንስ ይህን ለማሰብ የሚችሉ ሰዎች ኢህአዴግ ውስጥ የሉም ለማለት ይከብዳል።
ስላምና ዕርቅን የሚፈጥሩ ሁኔታዎችን መፍጠር
የችግሩ መፍቻ ማስተር ቁልፍ ያለው በሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ወሳኝ ሀይል በመያዙ ምክንያት መንግስትን የሚመራው የፖለቲካ ሀይል ህወሀት/ኢህአዴግ ጋ ነው። እስካሁን ያለው አግላይ ፖለቲካ የሀገሪቱን አቅም አሰባስቦ ዘላቂ የኢኮኖሚ ለውጥ ለማምጣት አልረዳም። ይዋል ይደር እንጂ ሰፊ አለመረጋጋትም መፈጠሩም አይቀርም። በውጭም ሀገር ውስጥም ያለው የኢትዮጵያውያን ሀብት በገፍ ተሰብስቦ ሀገሪቱ ውስጥ ያለውን ችግር ለመመከቻ የሚውልበትን አስቸኳይ መንገድ መፈለግ ትልቁ የመንግስት ስራ ሊሆን ይገባል። ይህ ማለት ሀገሪቱን ከባዕዳን ይልቅ ለራሷ ተወላጆች የምታጓጓ (attractive) ማድረግ ያስፈልጋል ማለት ነው። መንግስትም ተቃዋሚም ህዝብም ይህንን ችግር እንደ አስቸኳይ ጊዜ (emergency) ችግር አድርገን መቁጥርም ይኖርብናል። ቀጠሮ ከሰጠነው በጥፋቱ ላይ መቀጠልን የመስማማት ያህል አደረግነው ማለት ነው። ለዚህ የሚከተሉት ዋና ዋና እምነቶችና ርምጃዎች ጠቃሚ ይመስሉኛል።
1. የኢሕአዴግ መንግስት በተለያየ መንገድ ተጣልቶ የወነጀላቸውንና ከሀገር የወጡትን የፖለቲካ መሪዎችና ድርጅቶች እንዲሁም ባንድ ምክንያት ወይም በሌላ መንግስት ይተናኮለኛል ብለው ለሚያስቡ ግለሰቦች ሁሉ አጠቃላይ ምህረት (Comprehansive Amnesty) ማወጅ ይኖርበታል። ይህ በሀገር ውስጥ የታሰሩ የፖለቲካ አስረኞችን ጋዜጠኞችንና የሀይማኖት መሪዎችን መፍታትን ይጨምራል። ይህ ውሳኔ የዜግነትን ወይም የኢትዮጵያ ተወላጅነትን ስሜት የሚያነሳሳ ይሆናል። በሁላችንም ዘንድ የይቅር ባይነት ስሜትንም ይፈጥራል። መንግስት ይህን ሲያደርግ የተሸናፊነት ሳይሆን የትልቅነት ስሜት ሊሰማው ይገባል። ይህን እንዴውም ለችግር መፍቻው እንደወሰደው ተቃዋሚዎቹን መገዳደሪያ ርምጃ አድርጎ ሊቆጥረው ይገባል።
2. ከላይ ባንደኛ ተራ ቁጥር ከተጠቀሰው ውሳኔ ጎን ከፖለቲካ ድርጀቶች ጋር ተገቢ የሆነ የፖለቲካ ድባብ (Environment) ለመፍጠር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይትና ድርድር መጀመር ያስፈልጋል። ድርድሩ ሁሉን አቀፍ (Comprehansive) ሆኖ ሁሉንም ወገን አሸናፊ የሚያደርግና የህዝቡና የሀገር ጥቅምን መሰረት ያደረገ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል።
3. ማህበረሰቦች የሚጠነክሩትና መንግስትና ጉልበተኞችን የሚቆጣጠሩት የሲቢል ማህበረሰቦች ሲያብቡና ሲበዙ ነው። መንግስት የሲቪል ማህበራትን ደብዛ እንዲያጠፋ አድርጎ ያወጀውን አዋጅ ማንሳት ይኖርበታል። ይህ ለብዙ በጎ ስራዎችና ለዜግነት ክብር ማበብ በር ይከፍታል።
4. የድርድሩ ሂደትና ውጤት ዋስትና እንዲኖረው ከሀገር ሽማግሌዎች በተጨማሪ ወዳጅና ለጋሽ መንግስታትና ተቋሞች ድርድሩን እንዲያግዙ እንዲታዘቡና እንዲዳኙም ማድረግ ይጠቅማል።
5. በብዙ ምክንያት በተለይም ብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካ ጋር በተያያዘ አይን ለአይን መተያየት የማይችሉ የፖለቲካ ሀይሎች ውይይት መጀመርና የሀገሪቱን ዋና የድህነት ችግር ለመፍታት ልዩነታቸውን ማቀራረብ ይኖርባቸዋል። ይህን ችግር ልንፈታ ስንነሳ ድህነት የሚያሰቃያቸውና ተስፋ ያስቆረጣቸው ወገኖቻችን አንድ ጉድጓድ ውስጥ እንዳሉ ቆጥረን መሆን ይኖርበታል። ሁሉም ነገር ላይ ባንስማማ ምንም አይደለም። ቀሪውን ችግር ለወደፊቱ በውይይት በህግና በህዝብ ፍርድ ለመፍታት መወስን ነው ትልቁ ነገር።
6. ሀገሪቱን የሚመሩት የፖለቲካ ሰዎችና ቡድኖች (ህወሀት/ኢህአዴግ) እንደማንኛውም ሰው የራሳቸው ህልውና ሰጋትና ፍርሀት እንዳላቸው ሁላችንም ልንገነዘብ ይገባል። ስልጣን ላይ ያሉት ሰዎች ተቃዋሚዎቼ ያጠፉኛል ብለው ካሰቡ አካሄዳቸው መዘዝ ያለው መሆኑን እያወቁ እንኳን እስከመጨረሻ ለመከላከል ቆርጠው እንደሚቀመጡ ልንገነዘብ ይገባል። ትልቁም ስራ ከዚህ ስጋት እንዲላቀቁ ማድረግ ስለሆነ ከፍተኛ የቅንነት ስራ መስራት ያስፈልጋል። ተቃዋሚ ሀይሎች ሀገሪቱን የሚመራውን የፖለቲካ ሀይል ሙሉ ለሙሉ መወገድ አለበት የሚል አቋማቸውን ትተው በራሳቸውም ላይ ይሁን በህዝብ ላይ ተፈጽመዋል የሚሏቸውን የመንግስትና ግለሰብ መሪዎች ጥፋቶች ይቅርታ ለማድረግ መዘጋጀትና በስምምነት በሚወሰን ጊዜ ውስጥ ስልጣን በምርጫና በምርጫ ብቻ የሚያዝበት መንገድ ላይ ዋስትና ያለው ድርድር ለማድረግና ለመስማማት ፈቃደኛ መሆን ይኖርባቸዋል።
7. በሁሉም ወገን ያሉ ጥፋቶችን በይቅርታ ለመፍታት ቆርጦ ሁሉም የሚተማመንበት ኮሚሺን አጣርቶ በሚወስናቸው የጥፋት ዝርዝሮች ላይ ተወያይቶ ጥፋቶችን ከመቀበልና (Acknowledgement) መማሪያ ከማድረግ ባለፈ በማንም እንዳይደረግ አስቀድሞ መወሰን ይጠቅማል። ከሌሎች ልምድ ሲጠቅም አይተናል። በደል ደረሰብን የሚሉና ፍርድ የሚጠይቁ ዜጎች ሲኖሩም ጉዳታቸውን ግለሰቦች ሳይሆኑ መንግስት የሚክስበትን ሁኔታ ማመቻቸት ይቻላል።
8. በተቃዋሚዎች በኩል አሁን በስልጣን ላይ ያሉ ግለሰቦች ያፈሩትን ሀብትና ጥሪት ካለምንም ጥያቄ እንዲጠቀሙበትና ለቤተሰባቸውም እንዲያወርሱት ዋስትና በሚሰጥ ሁኔታ ማረጋገጥ ትልቅ ወደ እርቅ መንገድ መሳቢያ ዘዴ አድርጎ መውሰድ ያስፈልጋል።
9. ከዚህ ጎን ለጎን በውጭም በሀገርም ያሉ ኢትዮጵያውያን እንዳመቻቸው በግልና በህብረት በኢንቨስትመንት ስራ ላይ የሚሰማሩበት ሁኔታ እንዲመቻች ማድረግና መጋበዝ ማበረታቻም መስጠት ያስፈልጋል። በርካታ ሰራተኛ ለመቅጠር ለቻሉ የኢንቨስትመንት ተቋማት የታክስና ሌላም ማበረታቻ የሚሰጥ ፖሊሲ ማዘጋጀት ያስፈልጋል። በዚህ ጊዜ ሁላችንም ከስደት ወደሀገራችን መመለስና ስራ መስራት እንመርጣለን። ራሱን ጠቅሞ ወገንን እንደመጥቀም የሚያስደስት ምንም ነገር የለም። ከዚያ በላይ ደግሞ ከህግ በላይ የሚፈራ ነገር በሌለበት ሀገር መኖርን የሚጠላ የለም።
10. ከላይ በተነሱትና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ መግባባት ከተፈጠረ በኋላ ፍጹም ነጻ የሆነ ምርጫ የሚከናወንበትን ጊዜና ሁኔታ አመቻችቶ ባለማቀፍ ታዛቢዎች ፊት ማንም ወገን የማይገለልበት ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ለማድረግ ውጤቱንም በጸጋ ለመቀበል መወሰን ያስፈልጋል።
ከላይ ካነሳኋቸው ውጭ ብዙ ዝርዝር አከራካሪ ጉዳዮችና ችግሮች መኖራቸው ይገባኛል። እነዚህን ያነሳሁት ይዕርቁ መንፈስ ውቅር ምን መምሰል እንዳለበት ለማሳየት ያህል ነው። የተጠቀሱት የመፍትሄ ሃሳቦች ከመንግስት ቅን ምላሽ የሚያገኙት ቀደም ሲል እንዳነሳሁት በቅንነት ወይም በበጎ ፈቃደኝነት ብቻ አይደለም። የፖለቲካ ተቃዋሚዎች መንግስት ላይ ከፍተኛ ግፊት የሚፈጥር ትግል ማድረግና ያቀረቡለትን የመግባቢያ ሀሳብ እንዲቀበል ከማስገደድ ያልተናነሰ ተጽዕኖ መፍጠር አለባቸው። ተቃዋሚዎች ልዩነታቸውን አጥብበው ባንድ ላይ መሰለፍ ቢችሉ ትልቅ የተጽዕኖ ሀይል ይፈጥራሉ። ለዚህ የሚሆን መሰረታዊ የመስማሚያ ሀሳብ ማፍለቅ አንድ ትልቅ ጊዜ የማይሰጠው ስራ አድርገው ሊያዩት የሚገባ ይመስለኛል። እንዴውም ከቀዳሚዎቹ ነገሮች እንዱና ዋነኛው በተቃውሞው ጎራ የተሰለፉ የፖለቲካ ሀይሎች ያግድሞሽ ትግል ከማድረግ ወጥተው በእንድ ላይ የመሰለፋቸው ጉዳይ ነው።
ማጠቃለያ፥
ሁሉም ወገን አሸናፊ ሆኖ ፣ ሰላምና እርቅ ሰፍኖ ካለፈው ይልቅ መጭው ጊዜ ወሳኝነት ላይ ያተኮረ አመለካከት እንዲዳብር ማድረግ የችግራችን አይነተኛ መፍትሄ ነው። እንደ ሀገራችን ልማድ ይዋል ይደር እንጂ መንግስትን በሰፊ የህዝብ አመጽ ማስወገድ ይቻላል። ኪሳራው ግን ቀላል እይሆንም። ብዙ ህይወትና ንብረት ያስከፍላል። የኢትዮጵያን ድህነት ልብ ብሎ ለሚያይ ሰው የመጀመሪያው ምርጫው አብዮት ሊሆን አይችልም። በዚህ መንገድ ዛሬ ካሉብን የድህነት ችግሮች ለመላቀቃችንም ሆነ የሚቀጥለው ስርዓት ዴሞክራሲያዊ ስለመሆኑ ዋስትናም እናገኝም። በሰላምና ዕርቁ መንገድ ከሄድን ካለብዙ ኪሳራ ሁላችንም በተለይ መጭው ትውልድ የምንፈልገውን አገኘን ማለት ነው። የሰላምና ዕርቅ መንገድ ብዙ ለመቀበል የሚያስቸግሩ ይቅር መባባሎችንና ምህረተኛነትን ይጠይቃል። ይህ እንዳንድ ጊዜ ፍትሐዊም ላይሆን ይችላል። ይህንም ለተሻለ መጭ ጊዜ ስንል እንደምንከፍለው ሂሳብ ልንቆጥረው ይገባል።
እዚህ የሰጠሁት ሀሳብ በግብር እንዲውል ሰፋ ያለ ደጋፊ ህዝብ (Constituency) ያስፈልገዋል። የተባበረና በመንግስት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ መፍጠር የሚችል የተቃውሞ ሀይልም አስፈላጊ ነው። ሌላው አስፈላጊ ነገር ከፖለቲካ ፉክክር ውጭ ያሉ ተደማጭነት ያላቸው ሽማግሌዎች በበቂ ማግኘትና በመንግስትና በተቃዋሚዎች መሀል እንደልብ እየተመላለሱ ድልድይ እንዲሆኑ መፍቀድ ነው። ሁላችንም ሀገራችን የበደልናት አንድ ትልቅ ነገር ተደማጭነትና የሞራል የበላይነት ያላቸው ሽማግሌዎች (Statesmen) እንዳይኖራት ማድረጋችን ነው። ከኔ ጋር ካልሆንክ ጠላቴ ነህ የሚለው የአርባ ዐመት ፖለቲካችን ይህን በነገስታቱ ዘመን በመጠኑም ቢሆን የነበረንን የባህል ቅርስ አጥፍቶብናል። ነገር ግን አሁንም ብዙ ጥሩ ሽማግሌዎች ሊወጣቸው የሚችል ቅን ሰዎች የምናጣ አይመስለኝም። እዚህ ካነሳሁት የመነሻ ሀሳብ የበለጠ ሀሳብ ያላቸው ሰዎች እንዳሉም አውቃለሁ። ይህ በግርደፉ የሰነዘርኩት ሀሳብ ይበልጥ ተዘርዝሮ ሊዳብር ይችላል። በሀገሪቱ ፖለቲካ ላይ ተዋናይ የሆኑ ሀይሎች ሁሉ ውረድ እንውረድ ከሚል ዛቻ ወጥተን ዘመናዊ ሰዎችና ሀገሮች እንደሚያደርጉት አጥፊ ጉዳት ለሌለው መፍትሔ ከተዘጋጀን ከዚህ ከገባንበት ውርደት መውጣት ብቻ ሳይሆን ሀገራችን ለራሷ ቀርቶ ለብዙ እንድትተርፍ ማድረግ እንችላለን። ኢትዮጵያም ህዝብ ጥያቄ ባነሳ ቁጥር ጠመንጃና ታንክ የማይጎተትበትን ዘመናዊውን ስልጡን ዓለም ተቀላቀለች ማለት ነው። መንግስትም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ የሀይለኞች ንብረት ከመሆን ተላቆ የዜጎች ማገልገያ ሆነ ማለት ነው። ያን ጊዜም በገፍ መሰደድና መዋረድ ይቀርና የተሰደድነውም ወደሀገራችን ተመልሰን የየአቅማችንን ማዋጣት እንጀምራለን።
Fekadeshewakena@yahoo.com

No comments:

Post a Comment