Wednesday, October 15, 2014

ለሕገ መንግስቱ መቆም ሽብርተኝነት ሲባል (ዞን ዘጠኞችን በተመለከተ) ግርማ ካሳ

የተማሩ ናቸው። አገራቸውን የሚወዱ። በሕዝባቸውና በአገራቸው ዉስጥ የሚደረገዉ ግፍ እንዲቆም በጽሁፋቸው የሚመክሩ። ማንም ላይ ጥላቻ የሌላቸው። ኢፍትሃዊነትን የሚጠሉ ። አምባገነንነትን እንጂ ማንንም የማይጸየፉ።
Haile Mariamበጽሁፋቸው ፍቅርን ሰብከዋል። ነጻነትን አውጀዋል። «ዜጎች እንደ እንስሳ ታስረዉና ታፍነው መኖር የለባቸውም። ነጻነታቸውና ስብእናቸው ሊጠበቅላቸው ይገባል» እያሉ ተከራክረዋል። ለሰብአዊነት ተሟግተዋል።  ሰው ሲከብር እንጂ ሲዋረድ፣ ሲነሳ እንጂ ሲወድቅ፣ ሲድን እንጂ ሲሞት፣ ሲበለጸግ እንጂ ሲደኸይ ማየት አልፈለጉም።
በቢሯቸው፣ በቤታቸው፣ ሴቶቹ በቦርሳቸው፣ ወንዶቹ ደግሞ በኪሳቸው ቦምብ ወይም ፈንጂ አልተገኘባቸው። በድብቅ የዶለቱት ወይንም የሰሩት ነገር የለም። የተወሰኑቱ ካምፓላ ኡጋንዳ ሄዱ እንጂ በድብቅ አስመራ የሄደ ከነርሱ መካከል የለም።  የጻፉትና የተናገሩት ሁሉም በግልጽና በአደባባይ ነው። የተወሰኑቱ አርቲክል ዘጠኝ ከሚባል ድርጅት ጋር ግንኙነት አላቸው።

አርቲል ዘጠኝ እንደ አይሰስ፣ ወይም አልካይዳ ያለ ደርጅት አይደለም። የአርቲክል 19 ድርጅት አመጣጥ እንደዚህ ነው፡
የተባበሩት መንግስታት የሰባአዊ መብት ድንጋጌ (THE UNIVERSAL DECLARATION OF HUMAN RIGHTS የሚባል አለ። የዚህ ድንጋጌ አንቀጽ 19 ( አርቲክል 19) እንዲህ ይላል ፡
«Everyone has the right to freedom of opinion and expression; this right includes freedom to hold opinions without interference and to seek, receive and impart information and ideas through any media and regardless of frontiers.»
በዚህ አንቀጽ ላይ የተጻፈው ነጻነት በአለም ዙሪያ ሁሉ እንዲከበር ለመርዳት (አድቮኬት ለማድረግ)  የተቋቋመ የሲቪክ ማህበር ነው፣  አርቲክል ዘጠኝ። ይህ ማህበር አርቲክል 19 የሚል ስያሜ ይዞ፣ በአሜሪካ፣ በአዉሮፓ ባሉ በርካታ አገሮች፣ በኬንያ፣ በቱኒዚያ ፣ በባንግላዲሽ ሳይቀር እውቅና አግኝቶ የሚንቀሳቀስ ነው። በአገራችን ዉስጥ በኢሕአዴግ መንግስት ተጋብዞ በምርጫ ዙሪያ ስልጠናዎች የሰጠ ድርጅት ነው።
ይህ የተባበሩት መንግስታት አንቀጽ 19 ድንጋጌ  በኢትዮጵያ ፌዴራል ሕገ መንግስት አንቀጽ 29፣ ን ኡስ አንቀጽ 1 እና 2 ላይ በግልጽ ተቀምቷል። «Everyone shall have the right to hold opinions without any interference.Everyone shall have the right to freedom of expression without interference. This right shall include freedom to seek, receive and impart information and ideas of all kinds, regardless of frontiers, either orally, in writing or in print, in the form of art, or through other media of his choice.» ይላል የሕገ መንግስቱ አንቀጽ 29።
በተባበሩት መንግስታት የሰባአዊ መብት ድንጋጌ አንቀጽ ( አርቲክል 19) ወይንም የኢትዮጵያ መንግስት አንቀጽ 29፣  በኢትዮጵያ ተግባራዊ እንዲሆን የሚጽፉ፣ የተደራጁ ሰላማዊ ዜጎች ናቸው። ለሕገ መንግስቱ ፣ ለሕግ ከበሬታ ያላቸው ናቸው።
ነገር ግን ከዘመናዊት ፍጹም የራቁ፣ በሚድል ኤጅ ይኖሩ ከነበሩ በአስተሳሰብ የማይተናነሱ፣ አዲስ አበባ ያሉ ገዢዎች ግን፣  ራሳቸው ያወጡትን ሕገ መንግስት ረጋግጠው ፣ ሽብርተኞች ናቸው በሚል ክስ ከሰዋቸው ከፍተኛ መከራና እንግልት እየፈጸሙባቸው ነው። ይኸው ነገ ለዘጠነኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ፣  የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን !!!
እንግዲህ አገራችን የምንላት ኢትዮጵያ እንዲህ አይነት አሳዛኛ አሳፋሪ ግፎች የሚፈጸምባት አገር ናት። ኢትዮጵያ ለጥቂቶች ገነት፣ በአሥር ሚሊዮን ለሚቆጠሩ ልጆቿ ግን ሲኦል የሆነች አገር ናት።  ይሄ መለወጥ አለበት። ይሄ መቆም አለበት።  ይህን አይነት ግፍ አይቶ ዝም የማለት ሕሊና ሊኖረን አይገባም። ሁላችንም የድርሻችንን በመወጣት፣ የሚሊዮኖች ንቅናቄ አካል በመሆን፣  ለነጻነት፣ ለፍትህ ለእኩልነት መቆም ይኖርብናል። ዞን ዘጠኞችን በማሰሩ አገዛዙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዞን ዘጠኞች መፈጠራቸውን ልናሳየው ይገባል።

No comments:

Post a Comment