Thursday, October 30, 2014

የፓርቲዎች ውስጣዊ ፈተና…


በአገራችን ኢትዮጵያ እታየ ያለው የመንግስት የአስተዳደር ሽባነት ለማጋለጥ እና አማራጭ መፍትሔ ለመስጠት፣ ከፍ ሲልም ለማስተዳደር በሰላማዊ መንገድ በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች መኖራቸው የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ ይሁን እንጂ እነኚኽ ፓርቲዎች በተለይ የሚያደርጓቸው ማናቸውም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴበገዥው መንግስት በኩል የሚደርስባቸው እስራት፣ግድያናእንግልት የአደባባይ ሚስጥር ከሆነ ዓመታ ተቆጥሯአል፡፡
በአገራችን የፖለቲካ ሥርዓት ሄደት ውስጥ ስልጣን በሰላማዊ መንገድ ከአንዱ ወደሌላው የተሸጋገረበት፣ለትምህርት እና ለምሳሌ የሚያገለግል፣ የቅርብ እንዲሁም የሩቅ ክስተት እጥረት ወይም ውስንነት የአገራችን የፖለቲካ ሂደት ዋንኛ ፈተና ነው፡፡ለዚህም ነው የስልጣን ሽግግር ጉልበትን መሠረት ያደረገ ብቻ የሆነው፡፡
እንዲህ ዓይነቱ የስልጣን ሽግግር ጉልበተኞች ሁሌም አሸናፊ የሚሆኑበት፣ ጉልበቱ አናሳ ከስልጣን የሚርቅበት ኋላ ቀር አስተሳሰብ ነው፡፡ይህ ደግሞ በአብዛኞቻችን ላይ ስነ-ልቦናዊ ተፅኖ ከመፍጠር አልፍ ተርፎ ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ ተግባሪዊ ለማድርግ ወደኋላ የማንል መብዛታችን ለጉድ ነው፡፡እንዲህ ዓይነቱ አስፈሪ ሥርዓት በቤተስብ አስተዳደር፣በጎደኝነት፣በተቋማት እና በማህበራዊ እንቅስቃሴችን ገና ዳዴ ብልን የምንጀምረው የበላይነትን ለማረጋገጥ የምንከተለው አይነተኛ ዘዴ ነው፡፡ይህ ደግሞበሃሳብ ፍጭት ለሚመጣ የተሸለ ሃሳብ ለውጥ ካለን ተገዥነት ይልቅ፣በጉልበቱ አሸናፊ ለሆነ ሃሳብ ያለን ተገዥነት በእጅግ የበዛነው ፡፡ 
ይሁን እንጂ አሁን አሁን ላይ እንዲህ አይነቱ አስተሳሰብ መለወጥ እና መሻሻል አለበት በማለት የተነሱ ፓርቲዎች አሉ፡፡በተለይ የመንግስት አስተዳደር ለውጥ መምጣት ያለበት “በሰላማዊ ትግል ነው” ፡፡ሰላማዊ ትግል ደግሞ ቢሮ ተቀምጦ መግለጫ ከመስጠጥና ከጋዜጣ ጀብደኝነት ተላቆ፣ መሬት የያዘ ዓለም አቀፍ ልምዶችን በመጠቀም፣የአገራችንን ነባራዊ ሁኔታ መሠረት በማድረግ፣የተለያዩ የሰላማዊ ትግል ዘዴዎችን በመጠቅም የሥርዓት ለውጥ መምጫው መንግድ ይሄ ነው ! የሚሉ ፓርቲዎች አሉ፤የዚህ ፁሑፍ አቅራቢ እምነትም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡
ባለፉት 23 ዓመታት የአንድ ፈላጭ ቆራጭ አምባገነናዊ አገዛዝ ሥርዓት ለመታገል እና ለውጥ ለማምጣት የተቋቋሙ ቁጥራቸው የበዛ ፓርቲዎች መኖራቸው እርግጥ ነው፡፡ከነዚህም መካካል ምን ያኸሉ ተሰካላቸው ለሚለው ትክክለኛው ምላሽ ምንም ነው! ይህን ለማለት የሚያስደፍረው ውጤቱ የሚለካ ስለሆነ ነው፡፡ ሆኖም ግን ከተደረጉና አሁንም በመደረግ ላይ ካሉ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ተሞክሮ በመውሰድ፣ በፖለቲካዊ እንድምታ በአግባቡ በመረዳት ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ነባር ፓርቲዎች አሁንም አሉ፡፡በእስከዛሬው ልምድና ተሞክሮ በተጨባጭ ነባራዊ ሃቅ ላይ በመመስረት በአዲስ መንፈስ እና አስተሳሰብ የተቃኘ፣ ለጋ የሆነ ፓርቲ በብዙ ጥረትና ድካማ ለማግኘት ተችሎአል፡፡ለዚህም የተለየ አማራጭ ኃይል እንድናገኝ ላበቁን ጀግና ወጣቶች ምስጋና ይድረሳቸው፡፡
ይህ ተስፋ ሰጪ የፓርቲዎች እንቅስቃሴ ውጤታማ እንዲሆን የሁሉም የነቃ ተሳትፎ የሚያስፈልግበት ደረጃ ላይ እንገኛለን፡፡ነገር ግን የሌላውን ሰው ወይም ተቋም ተሳትፎ እና ድጋፍ ከመሻት በፊት የራስ ጥንካሬ እና ድክመትን በቅጡ መለየት ዋንኛ ሥራ ሊሆን ይገባል፡፡አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ ውስጣዊ ጥንካሬው እና ድክመቱን የሚለይበት መንገድ እና ለደረሰበት ውጤት መሠረቱ ውስጣዊ ዴሞክራሳዊ አካሄድ ብቻ ነው፡፡ይሁን እንጂ የፓርቲዎች ውስጠ ዴሞክራሲ አካሄድ በአብዛኛው ጤናማ አይደለም፡፡“ከስእተቱ የማይማረው ፈንጂ አማካኝ ብቻ ነው” እንደሚባለው ሁሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ከፍንጂ አማካይ የተሸለ እድል እና ት/ት ማግኘት እየተቻላቸው ከፈንጂው አማካኝ በባሰ በራስ ላይ ጉዳት ማድረሳቸው ፣ምን ዓይነት ልክፍት ነው የሚያስብል የቁጭት አግራሞትን የሚፈጥር ነው፡፡በሰላማዊ መንገድ ተንቀሳቅሰን እናቀሳቅሳለን የሚሉ ፓርቲዎች“ውስጣዊ ፈተና” በወፍ በረር መቃኘት የዚህ ፁሁፍ አቅራቢ ዋንኛ ትኩረት ነው፡፡በእርግጥ የዚህ ፁሑፍ አቅራቢ ለችግሩም ሆነ ለመፍትሔው የጉዳዩ ባለቤት ከሆኑት ውስጥ አንዱ እንደሆንኩ ታሳቢ ማድረግ ይቻላል፡፡
በመሆኑም በተቃዋሚ ፓርቲዎች በአብዛኛው የሚታዩ ችግሮች መመልከት ይቻላል፡፡ ለዚህም እንደማሳያ የተወሰኑ እና ዋና ዋና ምሳሌዎችን መጥቀስ ተገቢ ይሆናል፡፡የተለየ አሳብና ተግባር ይዞ የሚመጣ የፓርቲ አባል በተቀሩት የፓርቲ አባላት ውግዘት እና መገለል ይደርስበታል፡፡ ቀድሞ ነገር የተለየ ሃሳብ መያዝ በራሱ ስእተት አይደለም፣ ይሁን እንጂ በአብዛኛው እንዲህ ዓይነቱ አስተሳሰብ የማዳመጥ እና የመፈተሸ የአቅም ማነስ ችግር ዋንኛ ምክንያት ነው፡፡ የዚህ ችግር ይበልጥ የሚጎላው ደግሞ የተለየ ሃሳብ አለኝ የሚለው ወገን፣ ይዞ የመጣውን ሃሳብ ተቀባይነት በአንድም ይሁን በሌላ መንገድ ሳያገኝ ሲቀር ለምን የእኔ ሃሳብ ተቀባይነት አጣ በማላት እራስን ከመመርመር ይልቅ አጎጉል አካሄድ መምረጥ ሌላው የውስጥ በሽታ ነው፡፡እንዲ አይነቱ ነገር እያደር ሲሄድ በአንድ ፓርቲ ውስጥ ቡድናዊነት ከመፍጠር ባለፈ ፓርቲ እስከ መፍረስ ይደርሳል፡፡ይህ ሁሉ ከመሆኑ በፊት ግን ውስጣዊ ሰላማዊ የትግል ሃሳባ በማካሄድ የተሻለው ሃሳብ ገዥ እንዲሆን ጥረት የማድረግ አቅም እጅግ በጣም ደከካማነት አለ፡፡ይህ ደግሞየአብዛኛው ፓርቲ ዋንኛ ችግር ነው ፡፡
ሌላው ደግሞ ለፓርቲ ደንብ እና መመሪያ ያለን ተገዥነት ውስንነት ነው፡፡የፓርቲ ደንብ አባላት በትክክል መብታቸው እና ግዴታቸው በመለየት እና በማወቅ ውል የሚፈፅሙበት አይነተኛ መንገድ ነው፡፡ከዚህም በተጨማሪ ፓርቲዎች አጠቃላይ የሥራ እንቅስቃሴዎቻቸው ደንብን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ይሁን እንጂ በደንብ እና በመመሪያ በግልፅ ተደንግጎ የሚገኝ የአሰራር አካሄድ በማወቅ እና ባለማወቅ ከሊቀመንበር ጅምሮ እስከታችኛው አባል ሲያዳልጠን እንገኛለን፡፡ይህን አይቶ ማለፍ ያልቻለ የየትኛውም የፓርቲ አባል በሚያነሳው ትችት እና ጥቆማ ውስጠ ዴሞክራሲያዊ አካሄድ በመጠቀም ችግሩን ከመፍታት ይልቅ፣ የደንብ እና የመመሪያ አስፈላጊነት ጥያቂ ውስጥ የሚያስገባ አይነት ምላሽ በመስጠት ችግሩ ይበልጥ እንዲሰፋ ይደረጋል፡፡በደንብ እና በመመሪያ ከተደነገገው ሃሳብ ይልቅ ሁሉም በየራሱ ፍላጎት “ደንብ ለማላት የፈለገው ይሄን ነው” በማላት የሚመስለውን ትርጉም በመስጠት የሚደረገው እንቅስቃሴ የፓርቲዎች ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ውስጣዊ ጦስ ነው፡፡በዚህም ምክንያት ደንብ እና መመሪያ የሚያከብር እንዲሁም የሚቃወም የሚመስል ውስጣዊ ትግል ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
ከምንም በላይ ደግሞ የአሰራር ግልፅነት እና ተጠያቂነት ማጣት ተጨማሪ የፓርቲዎች ውስጣዊ ችግር ነው፡፡የገንዘብ አሰባሰብ እና አወጣጥ፣ ውሳኔ አሰጣጥ፣የስልጣን መአከላዊነት ወይም ተዋረድ ማጣት እንዲሁም ለውሳኔ ተገዥ የመሆን እና የመሳሰሉት ግልፅ ያለመሆናቸው ነው ፡፡በተለይ ደግሞ አብዛኛው የፓርቲ ሥራዎች በተወሰኑ ሰዎች ጥብቅ ትስስር መከናወናቸው፣የአሰራር ግልፅነት እና ተጠያቂነት ከማሳጣቱ በተጨማሪ የተቀናጀ የጋራ ትግል በአንድ ልብ ለማከናወን የማያስችል እንቅፋት ነው፡፡በዚህም ምክንያት የመረጃ ክፍተት በአባላት፣በሥራ አስፈፃሚዎች፣በምክር ቤት እና በድጋፍ ሰጪዎች መካከል ጎልቶ ይታያል፡፡ይሄን ተከትሎ የሚመጣው ጥያቂ እና መልስ በፓርቲ አባላቶች እና የሥራ አስፈፃሚዎች መካከል ፣አባላት ከአባለት እንዲሁም ድጋፍ ሰጪዎች ጭምር ተያይዘው የሚገቡበት ችግር ከመሆን ባለፈ በጓዳዊ ግንኙነት አሉታዊ ተጽኖ ፈጣሪ ነው፡፡
ሌላው ደግሞ የስራ ድልድል እና ሃላፊነት በተመለከተ ነው፡፡የፓርቲዎች የሃላፊነት ቦታ እንዴት ማግኘት እንደሚቻል እና ከሃላፊነት እንዴት መነሳት እንዳለበት በአብዛኛው በፓርቲዎች ደንብ እና መመሪያ ላይ ይገኛል፡፡ይሁን እንጂ እንዴት እና በምን መልኩ እንደሆነ ሳይታወቅ ወይም ፓርቲን መሠረት ያላደረግ የግለሰቦችን ፍላጎት የሚያረካ ሹምት እናሽረት ይካሄዳል፡፡እንዲ አይነቱ ነገር በአብዛኛው በሃላፊዎች የሚከናወን ነው፡፡ይህ ደግሞ የተግባር እና የሃሳብ የበላይነትን መደበኛ ባልሆነ መንገድ፣ ድጋፍ ሰጪ ሰዎችን በማሰባሰብ አሸናፊ ለመሆን የሚኪድበት ተልካሻ መንግድ ነው፡፡ይህም በራሱ በፓርቲዎች ውስጥ አለመግባባትን ከመፈጠር ባለፈ ለፓርቱዎች እልውና አደጋ ጭምር እስከመሆን ይደርሳል፡፡
ዋንኛው እና ትልቁ ከላይ የተዘረዘሩት እና መሰል ችግሮች ለመፍታት የሚደረገው ጥረት ድምዳሜው የአባራሪ እና የተባራሪ መሆኑ ነው፡፡እነዚህ ከላይ የተገለፆት እና መሰል ችግሮች በፓርቲዎች ውስጥ መፈጠራቸው መቼም ቢሆን የሚቀር እንዳልሆነ ብዙ አመላካች ነገር አለ፡፡ሆኖም ግን ከባላፈው ሂደት ስእተታችን ምን ነበር ጠንካሪ ጎናችንስ ምድነው ብሎ በመጠየቅ እና በመለየት ት/ት በመውስድ ድክመትን ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት ባይቻልም ለመቀነስ ጥረት ማድረግ ተገቢነት ያለው አካሄድ ነው ፡፡ ነገር ግን ጤናማ የሆነውን ውስጠ ዴሞክራሲ የሃሳብ ፍጭት በማድረግ ለተሻለው እና ለሚበልጠው ሃሳብ ተገዥ ባለመሆን የአባራሪ እና የተባራሪ የልጅ ጨዋታ ውስጥ መግባት የፓርቲዎች ዋንኛ ሥራ መሆኑ፣ ነገሩ እንዴት ነው ያስብላል፡፡
ከላይ ዋና ዋና ችግሮችን ለማየት መጠነኛ ሙከራ ተደርጎአል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ ችግሮች ስም በመጥቀስ የዚህ ፓርቲ ችግሮች ናቸው አልተባለም፡፡ሆኖም ግን ይሄ ችግር እኔን ይመለከታል የሚል ካለ ሃላፊነቱ የሱ ይሆናል፣ችግሩ ባይመለከተኝም እንደ-መረጃ በመውሰድ ለግብዓትነት እጠቀምበታለው፣ የሚል ተቃዋሚ ፓርቲ ካለም እሰየው ከማለት የተሻለ ነገር ምን አለ ! የሆነው ሆኖ ሣላ የትኛውም ፓርቲ በውስጡ ያለው ሰው ነው ! ሰው ደግሞ ሲሰራ ይሳሳታል፣ስዕተት ደግሞ የሰው ልጅ ባህሪ ነው፡፡ከስዕተት በላይ ግን የመማር እና የመለወጥ እድሉ ለሰው ልጅ የተሰጠው ታላቅ ተፈጥሯዊ ፀጋ ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ ፈታኙን ሂደት አልፈው “የተቃዋሚ ፖለቲካ ጎራ የጋራ ትግል ውጤታማነት ፣ግምገማና ዳሰሳ”በማድረግ ከአይቻልም ወደ ይቻላል የአስተሳሰብ ለውጥ በመምጣት በትብብር ለመስራት የተደረገው ሂደት እና ስምምንነት አበረታች ውጤት ነው፡፡ይህም ትብብር በገዥው መንገስት የሚደርስብን አገራዊ ጥፋት ለመከላከል የሚኖረው አስተዋጽኦ ቀላል አይደልም፡፡ይህን በሚገባ በመገንዘብ በትብብር ለመስራት ለወሰኑት ለሁሉም ፓርቲዎች፣ ድጋፍ እና አጋርነት መግለፅ እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡ለሚያደርጉት ማናቸውም ጥሪ ለውጥ ፈላጊ የሆነ ሁሉ በንቃት መጠበቅ ፋይዳው የበዛ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!
from yidenekachew kebede

No comments:

Post a Comment