Wednesday, October 15, 2014

ብፁዕ አባታችን ሊበርድዎ ነው መሰል – ከመኳንንት ታዬ(ደ እና ፀ)

ከመኳንንት ታዬ(ደ እና ፀ)
የአንድ ሃገር እድገት የሚመጣው በብዙ ምክንያት ነው ።ለዚህም ብዙ ብዙ ነገሮች ይጠቀሳሉ።በተግባር ውለው ለሚተገብር የሚተላለፍትን እንኳን ትተን በአባባል ደረጃ የሚነገሩትን እንኳን የወሰድን እንደሆነ እነሱ እየታሰቡ ሃገሬው ለአንዳች ነገር መጠቀሙ በሃገራችን ለብልፅግና ሲውሉ ይታያል።ለአብነት ያህል”ቀልደኛ ገበሬ በሰኔ ይሞታል”የምትለውን የወሰድን እንደሆነ፤ ገበሬው ሰኔ ግም ሲል ጨርቄን ማቔን እንዳይል ያግደዋል። በዚህ ምክንያት ለቤቱ ብልፅግና እንዲሆን ተግቶ ይሰራል።ይሁንና ይህን ለመንደርደሪያ ያህል ስል ቤተክርስቲያንስ እንዴታ ለማለት ቃል እንዲሳብልኝ ከመፈለግ አንፃር ነውና ወደዛው ልጓዝ።እርግጥ ነው የዚህችን የሲኦል ደጆች እንኳን አይችሏትም ስለተባለላት እናት እና አንዲት ቤታችን ለመተየብ እኔ ጨዋ ስለሆንኩ ብዙ አይጠበቀብኝም።

abune matias
ግንሳ ሰው ያለውን ከወረወረ ንፉግ አይባልምና በልቤ የሚንቀዋለለውን አንዲት ሃሳብ ለመሰንዘር እንዲህ ልበል ስል ቀለም ከወረቀት ጋር አገናኘሁ።ሰሞኑን ብፁነታቸው(ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘ አትዮጲያ ማለቴ ነው) በመስከረም በዚሁ ባሳለፍነው ወር መስከረም 27-28 ከየ አድባራቱ የመጡትን ካህናትና አስተዳደሪዎች ሰብስበው ሲያወያዩ እንደ ከረሙ በየ ድህረ ገፆች ላይ ስናይ ሰነበትን ።አንዴም እሰየው አባታችን ወደታች ውረደው ማዳመጥ አወቁበት ስንል አንዴም እሳቸውም ሊበርዳቸው ነው መሰል ብርድል ብሳቸውን ያለቅጥ ሞቀ ሲሉ ተስተዋለ ብለን ሲከፋን ሰነበተ።እሲቲ ወደ ነበረው ልጓዝ ።የ ኢትዮጲያ አርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክ በአይነቱ እጅግ አስከፊ የሚባሉ ፈተናዎችን አሳልፋለች።ይሁንና በገዛ ልጆቿ ስትፈተን የአለፉት 20 አመታት እንደምሳሌ ለማስተማሪያነት የሚነሳ እንደሚሆን እሙን ነው ።ግን ጠባቂዋ እግዚያሐብሔር ከጎኗ አለና ዘመናትን ሁሉ እንዲሁ ያሻግራታል። እርግጥ ነው ለክፉ ምክንያት የሆነው ባለቦታ አልፎ ሌላ ሲተካ የተሻለ መመኘት ይሆናልም ብሎ መጠርጠር ደግ ነውና። እርሶ ብፁዕ አባታችን አቡነ ማትያስ ሲመጡልን “የጥፋት ምንቸት ውጣ የስራ መንፈስ ግባ”ማለታችን ከስሜታችን በላይ ሆኖብን ከርሞአል።አሁንም ተስፋችን እንዳለ ነው።

እርግጠኝነታችን ደግሞ አሳድጎን እናት ቤ/ክ ስንል እና ልጆቸዎ ከያለንበት ሆነን ተማፅኖአችንን አሰምተናል።ይህም ውጤት አልባ ትረት እንዳልሆነ ይገባናል። ይሁንና አሁን ሰሞኑን ቅር ወዳሰኘን መልክት ልጓዝ።እርሶን የመሰለ አባት ወደታች ወርዶ ሲያዳምጥ ከመስማት ያለፈ ማለፊያ ደስታ ነገር አልነበረም ።የለምም። ነገር ግን ሲያዳምጡ እነማንን ሰብስበው ነው ያዳመጡት ? ስለ ምንስ ተወያያችሁ? በውኑ ሲኖዶሱ ያውቀዋልን ? ገንቢስ ሃሳብ ለቤተክርስቲያን የሚጠቅማት ነበርን? ለማለት ነበር ።ከሆነ ድግ ነው ።ነገር ግን አንድ ቀር ስላሰኘን እና ይህቺን መጣጥፍ እንድፅፍ ካነሳሳኝ ጉዳይ ልግባ።በመጀመሪያ እኔ የማህበረ ቅዱሳን አባል አደለሁም።ማህበሩን ግን ቀንም ለሊትም ከሚያገለግሉት ወገኖች አንዱ ነኝ።ይህን ስለራሴ ካልኩኝ በአንኳርነት ብፁዕነቶዎ ከተሰብሳቢዎቹ ጋር ካነሷቸው ነጥቦች አንዱ ማህበሩ ስለደረሰበት ደረጃ ነው።ይሁንና ከዚህ በፊት መቅደም ያለባቸውን፦
1. በገጠር ያሉ አባያተ ክርስቲያኖች መቀዳሻ ስለማጣታቸው
2.የቤ/ክ ይዞታ እየፈረሰ የሌሎች መደራጃ ስፍራ እንደሆነ
3.በ አክራሪ እስላሞች ወገኖቻችን ስለመታረዳቸውና ከዚህ በሓላ ጥቃት እንዳይደርስባቸው ምን መደረግ ስላለበት
4.ቤ/ክ ዘግተው ከተማ ስለሚመጡ ካህናትና መፍትሄው
5.የ አብነት ት/ቤቶች መዳከማቸውና ብሎም መዘጋታቸው ወደፊት ይህ እንዳይሆን ምን መደረግ እንዳለበት
6.በከተማ ባሉ እና በዘር በጎሳ ደራጅተው ቤ/ክ ስለሚዘርፏት ካህናትና አስተዳደሪዎች
7.በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አካብተው የገጠር አብያተ ክርስቲያናት
ሀ.በደሳሳ ጎጆ ስለመቀመጣቸው
ለ. መቀደሻ ነዋየ ቅድሳት አጥተው በወር አንዴ ብቻ ስለመቀደሳቸውና ይህ ችግር እንዴት እንደሚወገድ።
ሐ . ጣራቸው አፍስሶ እግዚያብሔር የሚከብርበት ቤት ለመግለፅ በሚያሳዝን ሁኔታ ውስጥ ሲሆን እነኚ ሓብታም ቤተ ክርስቲያንት ካላቸው ላይ አውጥተው የውዴታ ግዴታ እንዴት ችግርዩን ቀርፈው ቤተ ክርስቲያኒቱ እና ካህናቱ ከችግር እንደሚወጡ እና የመሳሰሉትን
8. ከግዜ ርዝመት መጪው ትውልድም ሆነ አሁን ያለው ማህተቡን እንዳይ በጥስ ምን መደረግ እንዳለበት ፤ ብቻ ብዙ ነው እንዲህ ብለነው አያበቃም ።እንኳን ለ እኔ ለደካማው ለእናንተም ለአባቶች እንኳን ብዙ የሆነውን ችግር አወያይተዋቸው በሆነ፤ እኛም እሰየው ባልን።ቅዱስነቶዎ አሁንም እንደትላንቱ በብቸንነት መስራት ከጀመሩ መካሪዎችዎት ሁሉ የንጉስ ሰለሞን ልጅ የሮብዓም ይሆኑና እንደገና ሌላ ደረባ መናድ እንዳይሆን ስለቤተክርስቲያንና በአጠገበዎ ላሉት ቅዱሳን አባቶች እንደገና ጫንቃቸው ላይ ሌላ ሸክም እንዳይሆን በሚል ፍርሃት ውስጥ መሆናችንን ልናሳስቦዎ እንወዳለን።
በመቀጠልም ምን አልባት አንዳንድ ግለሰቦች በማሕበሩ ታቅፈው የሚያሳዩት የግል ባሕሪ አስቆጥዎት ከሆናና እነኛን የክርስቲያን አንደበት የሌላቸውን ሰዎች በተባ ምላሳቸው ያሰማሩአቸው ፤እነርሱ እንደው ነገም እርሶ ዘረፋቸውን፤ጎጠኝነታቸውን ፤ለማስጣል ከሞከሩ ከዚሁ ያልተናነሰ ወቀሳና ከሰሳ ሊያደርስቦዎ እንደሚችል አይዘንጉ።አልያም አፍ ላለው የቀን ጅብ አሳልፈው ሊሰጡአቸው ፈልገው ከሆነም ታሪክ ይቅር የማይለው ስራ ሊሰሩ እንደሆን እንዲታወቆዎ የኢትዮጲያ ክርስቲያንም “ያም መጣ ያም መጣ ለእኔ እናት እንደሆን የበጃት የለም ሁሉም አፈር ጫነባት”ብሎ እንዳይወቅሶዎ ፍርሃቴ ነው።በተረፈው ጥፋት ሊኖር ይችላል ቁጣም የሚሰሙ ልጆቾዎ ስለሆኑ ጠርተው ይሄን በምን እናድርገው ቢሉ የማይፈታ ነገር የለም ።”እርሶ እኮ የቅድስት ሃገር አትዮጲያ ክርስቲያን አባትና ፓትርያርክ ነዎት።ታዲያ እንዴታ አባታችን።
በስተመጨረሻው “ቅዱስ ዳዊት የሰው ልጅ እድሜው ቢበዛ 60 ቢበዛ ሰማኒያ ነው ከዛ ካለፈ ግን ትርፉ ድካም ነው ” እንዳለ ሁሉ እርሶስ በቀረ እድሜዎ ለቤተከርስቲያን የበለጠውን እንዲሰሩላት የዘመናት ባለቤት ሁሉን ቻይ እግዚያብሔር እድሜና ጤና ይስጥልን ዘንድ የህዝበ ክርስቲያኑ ፀሎት ነውና ፊትዎን ከቤተ መንግስት በፊት ወደ ቤተከርስቲያንና ህዝቦቾዎ እንዲያዞሩ የምንግዜም ፀሎቴ ነው።
ቸር እንሰንብት

No comments:

Post a Comment