Monday, October 13, 2014

በግልጽ እንነጋገር – (ይሉኝታ፣ ምሁራን፣ ትግልና ሀገር በኢትዮጵያ)

አንዱ ዓለም ተፈራ
የእስከመቼ አዘጋጅ
ጥቅምት ፫ ቀን ፳ ፻ ፯ ዓመተ ምህረት ( 10/13/2014 )
eskemecheበአሁኑ ሰዓት በሀገራችን በኢትዮጵያ ያለውን ተጨባጭ የፖለቲካ ሁኔታ የማያውቅ ኢትዮጵያዊ የለም። ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ላይ ሁላችንም አንድ ስምምነት ላይ ነን። በአንድነት ያልተገኘንበት፤ ምን ይደረግ? በሚለው መፍትሔ መሥጠቱ ላይ ነው። መፍትሔ ደግሞ ከመቅረቡ በፊት፤ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አልፎ፤ በግንዛቤያችን ደረጃ ያለንበትን መመርመሩ ግዴታ ይሆናል። እንግዲህ የዚህ ጽሑፍ ማጠንጠኛ ይኼው የግንዛቤያችን ጉዳይ ነው። በትግሉ ዙሪያ፤ ድርጅቶች፣ ምሁራን፣ ግለሰቦች ሞልተናል። እያንዳንዳችን የምንፈልገውን እናውቃለን። የሚያስማማን ደግሞ እያንዳንዳችን ከምንፈልገው መካከል ያለው የጋራ ፍላጎታችን ነው። ይህ የየግል ፍላጎታችን በሀገር ደረጃ ሲቀመጥና የጋራ የሆኑት ከመካከሉ ተጎልጉለው ሲወጡ፤  ሀገራዊ መታገያ ዕሴቶቻችን ነጥረው ብቅ ይላሉ። በዚህ ጽሑፍ፤ የሀገራችን፣ የትግላችን፣ የምሁራን ሚናና የይሉኝታችንን አስተዋፅዖ አጤናለሁ። እነኚህ፤ በያዝነው ትግል ያላቸውን ድርሻ ተንትነን ስንረዳ፤ ውጤታማ ወደ ሆነ መንገድ እናቀናለን።

በይሉኝታ ትግል አይካሄድም። ትግሉ የደረሰበትን ደረጃ መርምረን፤ ግስጋሴውን በማጥናት፤ በጎውን በመመዘገብና ችግሩን በመለየት እርማት አድርገን፤ መንገዱን የማቅናት ግዴታ አለብን። በየጓዳችን የምንናገረውና በአደባባይ የምናቀነቅነው አንድ ካልሆነ፤ አስመሳዮች ነን። በየጓዳችን፤ “አንድነት እኮ አንደያ ነው።” “መኢአድንማ ተወው።” “ግንቦት ሰባት እኮ እንዲህ ነው።” “ኢሕአፓ እኮ እንዲያ ነው።” “የሽግግር መንግሥት ባዮች ደሞ እንደዚህ ናቸው።” “የምን ሸንጎ አመጣህብኝ! ለመሆኑ እነሱ ማናቸው?” “የሚረባ ምን ድርጅት አለ ብለሽ ነው?” “አርፎ መቀመጥ ይሻላል።” “ሁሉም አይረቡም።” እያልን በአደባባይ ደግሞ፤ “ወያኔ ዛሬ ይወድቃል።” “ነገ ሕዝቡ ያቸንፋል።” “መተባበር አለብን።” “ሰላማዊ ሰልፍ እንውጣ!” “ለኦባማ ደብዳቤ እንጻፍ።” “ሀገሬን እወዳለሁ።” ብንል፤ ሌሎችን ሳይሆን ራሳችንን ነው ማታለል የያዝነው። ወይ አንድ ጊዜ ቅርጦ ከወያኔ መላተምና ለሆድ ማደር! አለያ ደግሞ፤ በቅጡ ሰፈር ለይቶ ከሕዝብ መወገን ነው። ይሉኝታ ቀን አይገፋም፤ አፍ ብቻ ነው የሚያለፋው። ራስን ብቻ ነው የሚያስገምተው። ድርጅት አለኝ ብሎ መንደላቀቅ፣ እየታገልኩ ነው ብሎ መኩራራት፣ ያለኔ ሁሉም አይሆንም ብሎ ማቅራራት፣ ታሪክ አለኝ ብሎ መደንፋት የትም አያደርስም። ለሕዝባዊ ትግሉ ጠብታ እንኳን አይረዳም። በግልጽ መነጋገሩና እውነተኛውን መንገድ መከተሉ ብቻ ነው የሚያዋጣው። በያንዳንዱ ድርጅት ጉድለት አለ። አዎ ጉድለት አለ። ባሁኗ ሰዓት መቶ በመቶ ትክክለኛ የሚባል ድርጅት የለም። እያንዳንዱ ድርጅት ደግሞ ጥሩ የሆነ ጎን አለው። ከያዝናቸው ሌላ ከሰማይ የሚመጣ የለም። ያሉትን በቀና መመርመርና አስተካክለን ወደፊት መጓዝ አለብን።ታዲያ ጥሩውን አጉልቶ፤ ለጎደለው ማስተካከያ አበጅቶ፤ አነፃጽሮ ቢያወጡት፤ ሁሉም ድርጅቶች አንድ ይሆናሉ።
ይህን ግልጽ ላድርገው። ሁሉም ድርጅቶች፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት መሆኑን ያውቃሉ። በሀገራችን ያለው መንግሥት፤ ፀረ-ኢትዮጵያ መሆኑን ይቀበላሉ። መወገድ እንዳለበት ያምናሉ። ሕዝቡ መብቱን አስከብሮ፤ የራሱን ምርጫ በትክክለኛ መንገድ በቦታው መተካት እንዳለበት ይቀበላሉ። እንግዲህ እነዚህ መሠረታዊ የሆኑ የጋራ የትግል ዕሴቶቻችን ናቸው። ዴሞክራሲያዊ አሠራርና የሕግ የበላይነት በሀገራችን እንዲሰፍን ሁሉም ይፈልጋሉ። ይህም በጣም ጠቃሚ ዕሴት ነው። በተጨማሪ፤ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ተሳትፎ መደረግ ያለበት፤ በኢትዮጵያዊ ዜግነት ላይ የተመሠረተ፤ እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊትና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በግለሰብ፤ የዴሞራሲያዊ መብቶች ተከብረውላቸው፤ በኢትዮጵያዊነታቸው ብቻ መሆን እንዳለበት ያምናሉ። ይህ እንግዲህ መታገያና የምንታገልለት ጉዳይ ነው። ታዲያ ለዚህ ነው ሁሉም ድርጅቶች አንድ ይሆናሉ ያልኩት። ይህን የማይቀበል ድርጅት ካለ፤ ፈርተን ወይንም በይሉኝታ፤ ሕልውናው እንዲቀጥል መንገድ መጥረግ የለብንም። ይህ ይሉኝታ ሳይሆን ልበ ቢስነትና ተልፈስፋሽነት ነው። ትግሉ የሚጠይቀውን መስዋዕትነት መክፈል ቢያቅተን፤ ቢያንስ እውነቱን ተናግረን ራሳችንን ነፃ ማሳደር አይኖርብንም? ትግል እኮ፤ ራሳችንን ለሌሎች ሕልውና አሳልፈን መሥጠት ማለት ነው። የዚህ ሀ ሁ ደግሞ መጀመሪያ ለምናምንበት መቆም ነው። ወደ ምሁራን!
በያዝነው ትግል፤ ምሁራን ከፍተኛ ሚና አላቸው። በኛ ሀገር ባሁኑ ሰዓት ምሁራን በያሉበት፤ ግዴታቸውን፤ ማለትም ታሪካዊ ተግባራቸውን እያከናወኑ አይደሉም። ታሪካዊ ግዴታቸውን ለመወጣት፤ የአንድ ድርጅት አባል መሆን ወይንም አለመሆን መለኪያው አይደለም። ትግሉንና ሂደቱን መርምሮ፤ ትክክለኛ መፍትሔ ብሎ የሚያምንበትን በግልጽ ለሕዝቡ በማቅረብ፤ ድርጅቶችም ሆኑ ግለሰቦች ትክክለኛ ግንዛቤ እንዲያገኙ ማድረግ የምሁራኑ ተግባር ነው። ትግሉን ከመመርመር ይልቅ ላሉበት ድርጅት ተገዥ በመሆን፤ ሁሉንም ጉዳይ በድርጅቶቻቸው ዓይን የሚመለከቱ ከሆነ፤ ምሁር የሚያስብላቸውን መለኪያ አያሟሉም። አስተዋፅዖም የላቸውም። የድርጅታቸው እንጂ የሀገራዊ ጉዳዩ መልስ ሠጪ ባለመሆናቸው፤ ትግሉን እየጎዱ ነው። ለአንድ ምሁር፤ ሀገራዊ ተጨባጭ ሁኔታውን መዝኖ መፍትሔ ማቅረቡ፤ ከፖለቲካ ድርጅት አባልነቱ ጋር የተያያዘ አይደለም። መሆንም የለበትም። ይህ ለተጨባጩ ሁኔታ የሚሠጥ ተጨባጭ መልስ ነው። በአቀራረብና በቅደም ተከተል፣ በዘዴና በስልት፣ ወይንም ትግሉ ሊወስድ በሚችለው አቅጣጫና የሂደቱ ፍጥነት ላይ የተለያየ አመለካከት ይኖራል። ይህ በርዕዩተ ዓለምና ውጤቱን ከማፋጠን ወይንም ጉዳቱን ከመቀነስ ድርጅታዊ መልክ ይይዛል። ይሁን። ያኔ ምሁራን ጎራ ሊለዩ ይችላሉ። መሠረታዊ በሆነው ተጨባጭ የሀገራችን የፖለቲካ ሀቅና አጠቃላይ መፍትሔው ላይ ግን ልዩነት ሊኖር አይገባም። ተጨባጩ የፖለቲካ ሀቅ አንድ ነው። ከመልሶቹ ሁሉ ደግሞ ትክክለኛው አንድ ነው። ወደዚያ ለመድረስ በሚወስደው መንገድ መለያየት ይቻላል። ምሁራን በተጨባጩ ሀቅና በትክክለኛው መልስ አይለያዩም። ታዲያ ይኼን የኛ ምሁራን አልተገበሩትም።
የምሁራን ትኩረት መሆን ያለበት፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባርን ተግባር መዘርዘርና ማውገዝ ሳይሆን፤ ወደፊት የሚያሳይ መፍትሔውን በመጠቆም፤ ምን መደረግ እንዳለብት ማሳየት ነው። እናም ለምን መተባበር አቃተን? ለምን ትግሉ ባለበት ይረግጣል? ድርጅቶች ትግሉን እየጠቀሙ ነው ወይንስ እየጎዱ? አደረጃጀታቸው ለያዝነው ትግል እየረዳ ነው ወይንስ እየጎዳ? ለምን የታጋዩ ጎራ ባንድነት አልተሰለፈም? ለአለመሰባሰባቸው አደረጃጀታቸው አስተዋፅዖ አያደረገ ነው ወይንስ አይደለም? የመታገያ ዕሴቶቻችን ምንድን ናቸው? ድርጅቶች ይሰባሰቡ ስንል በምን ዙሪያ ነው? መሰባሰቢያ ማዕከላዊ ጉዳይ ከሌላቸው ለምን ይሰባሰባሉ? ሀገራዊ ራዕያችን ምንድን ነው? የሚለውን፤ በየድርጅቶቹ መርኀ-ግብር ከሠፈረው ግባቸው በስተቀር፤ ሀገራዊ የሆነ መልስ የሠጡ ምሁራን አልተገኙበትም። እናም ምሁራን በምሁርነታቸው በቦታቸው አልተገኙም። አንድም ፈሪዎች በመሆንና በመደበቅ አንገታቸውን ደፍተዋል፣ ሌላም ለድርጅቶቻቸው አሽከር በመሆን በድርጅቶቻቸው መነፅር ብቻ ተመልካች ሆነዋል? አለያም ሌሎች ይሥሩት በማለት በየግል አጀንዳቸው ተጠምደዋል። ይህ ምሁራዊነት አይደለም። ምሁር ማለት፤ ጨለማውን ገልጦ የሚያጠራ፣ ያልተረገጠውን ዳስሶ የሚያሳይ፣ ያልተዳሰሰውን ደፍሮ የሚቃኝ፣ ማለት ነው። እናም ምሁራን በምሁርነታቸው በቦታቸው አልተገኙም።
ትግሉ የኛ እንጂ የመጪዎቹ ወይንም የሌሎች አይደለም። አንድነት ግዴታ ነው። ማድረግ ያለብንን እና የኛ የሆነውን ኃላፊነት፤ ለማንም ልናስተላልፈው አይገባም። ይህ በኛ ወቅት ያለና የኛ ሀገራዊ ግዴታ ነው። ሀገራችን አሁን ላለችበት የፖለቲካ ሁኔታ የትናንትኖችን መውቀስ ወይንም ለነገዎቹ ማስተላለፉ ተገቢ አይደለም። ይህ የራሳችን የአሁኑ ኢትዮጵያዊያን ኃላፊነት ነው። የያዝነውን ትግል በሚመለከት፤ ባሁኑ ሰዓት የታጋዩ ወገን አንድ ማዕከል የለውም። ባሁኑ ሰዓት የተጋዩ ወገን አንድነት የለውም። ባሁኑ ሰዓት የተጋዩ ወገን ትግሉን በትክክል አልተነተነውም። ባሁኑ ሰዓት የታጋዩ ወገን የአንድነት ሀገራዊ ራዕይ የለውም። ባሁኑ ሰዓት የተጋዩ ወገን በትክክል አልተደራጀም። ባሁኑ ሰዓት የተጋዩ ወገን በትክክል ትግሉን አልመራም፤ እየመራም አይደለም። ስለዚህ የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ የታጋዩን ወገን፤ ከትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር የተሻለ ብሎ እንዳማራጭ እንዲወሰደው አስተማማኝ ሆኖ አልተገኘም። በርግጥ በማይካድ ደረጃ ሀገር ቤት ውስጥ ወደፊት የመንቀሳቀስ ሂደት ይታያል። አጥጋቢ አይደለም። ነገር ግን አጥጋቢ ባይሆንም፤ ያለው አማራጭ ያ ብቻ ሆኗል። ከዚያ የተሻለ ማድረግ እንችላለን። ትግሉ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ምርጫ ሆኖ የቀረበ አይደለም። በመኖርና ባለመኖር መካከል ግብግብ ሆኖ ስለተጫነው ብቻ ነው። እናም በማንም ውዴታ ወይንም ፍላጎት የተመሠረተ አይደለም። እኛ አስተዋፅዖ ለማድረግ ከፈለግን፤ የምንችለው፤ ጠንካራ የሆነ “የኢትዮጵያዊያን የነፃነት ንቅናቄ” ማካሄድ ነው። ለዚህ ንቅናቄ ደግሞ መሠረታዊ የትግሉ ዕሴቶቻችን ከላይ የተጠቀሱት ናቸው። እኒህም፤
ሀ) የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነትና ሉዓላዊነት መረጋገጥ፤
ለ) የኢትዮጵያ አንድ ሀገርነትና አንድ ብሔርነት መጠበቅ፤
ሐ) የሕግ የበላይነት በኢትዮጵያ መስፈን፤
መ) የያንዳንዷ ኢትዮጵያዊትና የያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር፤ ናቸው።
ከዚህ በላይ የተዘረዘሩት ሁሉን የኢትዮጵያዊያንን ፍላጎትና አሁን ያሉትን ድርጅቶች በሙሉ ፍላጎት የሚያሟሉ የትግል ዕሴቶች ናቸው። በነዚህ ዙሪያ የሚደረገው ትግል፤ አስተማማኝ የሆነ የወደፊት እንዲኖረን ይረዳናል። በርግጥ አመራሩን የሚሠጡት ግለሰቦች ወሳኝነት አላቸው። በዙሪያቸው የሚኮለኮሉትም ወሳኝነት አላቸው። አቤት ወዴት ብሎ፤ ሎሌ ይመስል አብሮ የሚነጉድ ተከታይ አሽከር ነው፤ እንጂ የድርጅት አባል አይደለም። ዴሞክራሲያዊ አሠራር ባልዳበረበትና ለሕግ መገዛት ባልጠነከረበት ትግላችን ውስጥ፤ ግለሰቦች የሚጫወቱት ሚና ከባድ ነው። ይመለካሉ። እስኪ ተመልከቱ፤ በየድርጅቶቹ ውስጥ ያሉ መሪዎች፤ እንደግል ንብረታቸው፤ ድርጅታቸው ከተመሠረተ ዕለት ጀምሮ ብቻቸውን ሲያዙበት አንዳንዶቹ አስርታት አመታት፤ ሌሎቹ ደግሞ ድርጅታቸው ከተፈጠረ ጀምሮ ያለውን ዕድሜ አስቆጥረዋል። አንድም ተከፋፍለው፣ አለያም ተገደው ካልሆነ በቀር ለውጥ የለም። መወራረስና ወጣቶቹን ወደፊት ማምጣት ትልቁ ነውር ነው። ስም የማልጠቅሰው፤ ያልተጠቀሰ ይኖርና እኔ የለሁበትም እንዳይል፤ ሁሉም በሙሉ በዚህ የተዘፈቁ ስለሆነ ነው።
ለግለሰቦች ያለኝ መልዕክት፤ ትክክለኛ የሆነ ኢትዮጵያዊ መንግሥት በሀገራችን እንዲኖር ሁላችን እንፈልጋለን። በምንችለው ደግሞ እየጣርን ነው። በየጊዜው መስዋዕት እየተከፈለ ነው። ትግል የበኩሌን እስካደረግሁ ድረስ ሌላ ኃላፊነት የለብኝም ብለን የምንቀመጥበት ክስተት አይደለም። ትግል የኛን ጠንካራ አስተዋፅዖ ከሌሎች ጠንካራ አስተዋፅዖ ጋር በመደመር፤ ካለንበት ወደፊት የሚኬድበት ነው። ባለንበት ከረገጥን፤ መመርመር ያለብን ጉዳይ አለ ማለት ነው። አንድም ትክክለኛ ያልሆነ የትግል ግብ ነድፈናል አለያም ትግሉ ለሚጠይቀው ትክክለኛ ድርጅት ይዘን አልተገኘንም ማለት ነው። ይኼ መመርመር አለበት። እንዲህ ካላደረግን፤ እንዲያው የምናደርገውን የማናውቅ ነን ማለት ነው።
በታጋይ ድርጅቶቹ መሪዎች በኩል ለድርጅቶች ያለኝ መልዕክት፤ ስትታገሉበት ላለው መርኀ-ግብር፤ እስከዛሬ በአባላት ከፍተኛ መስዋዕትነት፤ የምትችሉትን እያደረጋችሁ ትግሉን አቆይታችሁታል። ከልባችሁ የሀገራችንን ነፃ መውጣት ፈልጋችሁ ጥራችኋል። በቂ ሆኖ አልተገኘም። እናም አንድም ትግሉን፤ አለያም አደረጃጀታችንን በጥያቄ ውስጥ ያስገባ ሀቅ በላያችን ላይ መጥቷል። አሁን ከሌሎች ጋር አንድ ሆናችሁ ብቻ ነው ወደፊት መቀጠል የሚቻለው። እናም መርኀ ግብራችሁ ላይ ከፍተኛ እምነት ካላችሁ፤ ለአሁኑ አቆዩትና፤ ሀገር ነፃ ሲወጣ ለሕዝብ ታቀርቡታላችሁ። አሁን መታገያ ዕሴቶቻችን ተቀይረው፤ መጀመሪያ ሀገር ብለናል። ስለዚህ፤ ሀገርን እናስቀድም። የየድርጅቶቻችሁ ንብረትም ሆነ ታሪክ ይቆያችኋል። ለአሁኑ ከሌሎች ጋር በመሆን ባንድ ሰፊ የኢትዮጵያዊያን የነፃነት ንቅናቄ ሥር እንሰለፍ። በሀገር ጉዳይ ተመሣሣይና ተቀራራቢ አመለካከት ያላቸው፤ ነገር ግን የተለያየ ርዕዩት በሚከተሉ ድርጅቶች መካከል፤ የእኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ውድድር የሚደረገው፤ ነፃ ሀገር ሲኖር፤ ሕዝቡ የመምረጥ መብቱ ሲከበርለትና፤ ሕግን የሚያከብር መንግሥት በሥልጣን ላይ ሲሆን ነው። አሁን ትግሉ ያን ለማስከበር ነው። ስለዚህ የሁሉም ባንድነት፣ ባንድ ላይ፣ ባንድ ድርጅት መሰባሰብ የግድ ነው።

No comments:

Post a Comment