Tuesday, December 18, 2012

ተጠያቂዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ እንሆናለን፡፡


መንግሥት ሕዝብን የማሳመን፣ የማሳተፍ፣ የማቀፍና የማሰለፍ ግዴታ አለበት፡፡ የግል ዘርፉን የማበረታታት፣ የማጠናከር፣ የማሳተፍና ድርሻውን እንዲጫወት የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡ ሲቪል ማኅበረሰቡን የማጠናከር፣ በልማት እንዲሳተፍ የማድረግና የማገዝ ግዴታ አለበት፡፡ በመሆኑም እከሌ እምቢ አለኝ፣ እከሌ አደናቀፈኝ ብሎ መንግሥት ምክንያት ማቅረብ አይችልም፡፡ የልማት አካላትን በሙሉ የማያሳትፍ መንግሥት አገርን የማልማትና ከድህነት የማላቀቅ ብቃትና አቅም የሚኖረው መንግሥት ነውና፡፡ ግን በአገራችን የምናየው መንግስት ትልቁን የንግድ ዘርፍ ተቆጣጥሮ ወደ ኪሱ በመጨመር እራሱን በማጠናከር እድሜውን ለማርዘም ፓርቲውን ህውአት እያጠናከረ እንደሚገኝ የአደባባይ ሚስጥር ነው።
ደሃ እንድንሆን የፈረደብን የለም፡፡ ሀብታም እንዳንሆን የተጣለብን ክልከላና እገዳ የለም፡፡ ደሃ ወይም የበለፀገ ሕዝብ ለመሆን ምርጫው የራሳችን ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ምርጫ፡፡ ግልጽና የማያሻማ ምርጫ 
በአሁኑ ጊዜ ከድህነት እንዳንላቀቅ የውጭ ኃይሎች አደናቅፈውናል ብለን መውቀስ አንችልም፡፡ የውጭ እንቅፋትን አስወግደው ከድህነት የሚላቀቁ አገሮችና ሕዝቦችን እያየን ነውና፡፡ ላለመበልፀጋችን ምክንያቱ ሀብት ስለሌለን ነው ብለን ማመካኘትም አንችልም፡፡ ሕዝብ ራሱ ሀብት ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ ለብልፅግና የሚረዳ በጣም ሰፊ የእርሻ መሬት፣ ማዕድናት፣ የቱሪዝም መስህቦች፣ የኃይል ማመንጫዎች፣ ወዘተ አሉን፡፡  ዕውቀት ያለው ሰው ስላልተገኘ ነው እንዳንልም በአገር ውስጥም በውጭ አገሮችም በርካታ ባለዕውቀትና ባለሙያ ኢትዮጵያዊያን አሉ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች›› የሚል መጽሐፍ ቅዱስና ‹‹ኢትዮጵያን አትንኩ›› የሚል ቅዱስ ቁርዓን ይዘን ደግሞ የተረገመች አገር ስለሆነች ነው ብለን ማሳበብ አንችልም፡፡

ስለዚህ ካልለማን፣ ካላደግን፣ ካልበለፀግን፣ በድህነት ከቆረቆዝን፣ በረሃብና በእርዛት ካለቅን፣ ከተሰደድን፣ ከለመንንና ከተዋረድን ጥፋቱ የራሳችንና የራሳችን ብቻ ነው፡፡  በአጠቃላይ ተጠያቂዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ እንሆናለን፡፡ ትክክለኛ ምርጫ አልመረጥንምና፡፡ 


ከበለፀግንና ካደግን ደግሞ የምንከበረውና የምናስከብረው መላው አገሪቱንና መላው ሕዝብን ነው፡፡ በታሪክ ስንወሳ በቀጣዩ ትውልድም ስንመሰገን እንኖራ

በእርግጥ እዚህ ላይ በግልጽ መቀመጥ ያለበት ጥያቄ አለ፡፡ ምርጫው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? መንግሥት አለ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሉ፣ የግሉ ዘርፍ አለ፣ ሲቪል ማኅበረሰቡ አለ፣ ሕዝብ እንደ ሕዝብ ዜጋ እንደ ዜጋ አለ፡፡ ምረጥ ስንል እነዚህ ሁሉ አንድ ዓይነት ምርጫ መምረጥ አለባቸው ማለት ነው ወይ? አዎን ሕዝብ ስንል አገር ስንል እነዚህን ሁሉ በጋራ ማለታችን ነው፡፡ መንግሥት ለብቻው ከድህነት አያላቅቅም፡፡ መንግሥት ያለሕዝብ ድህነትን አያስወግድም፡፡ የግሉ ዘርፍና ሲቪል ማኅበረሰቡ ያለሕዝብና ያለመንግሥት የትም አይደርሱም፡፡

መንግሥት ሕዝብን መርቶና አገርን በሚገባ አስተዳድሮ ኢትዮጵያን ከድህነት የማላቀቅና የማሳደግ ግዴታ አለበት፡፡ መንግሥት የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አውጥቼ የነበረ ቢሆንም ሕዝብ፣ የግሉ ዘርፍና ሲቪል ማኅበረሰቡ አልከተል እያሉ አደናቀፉኝ የሚል ምክንያትና ሰበብ ማቅረብ አይችልም፡፡

መንግስት እንደዚሁ ልማትና ዕድገት እፈልግ ነበር፣ ከድህነት መላቀቅ እፈልግ ነበር፣ ነገር ግን ሕዝብ እምቢ አለኝ እንጂ ብሎ ማሳበብ አይችልም፡፡ ሥልጣን መያዝ ያለበትን የፖለቲካ ፓርቲ የምወስነው እኔ ነኝ ብሎ ሕዝብ ጠንክሮ መታገል አለበት፡፡ ከድህነት የማያላቅቅ መንግሥትን ጠንክሮ መቃወም አለበት፡፡ ሙስና፣ ስርቆትና ዘረፋን ሲያይ የራሴን ሀብት ነው የምትዘርፉት ብሎ መቃወም አለበት እስከ መቼ የአገር ሀብት ሲዘረፍ ዝም ብሎ ይታያል፡፡ ሕዝብ ካልተሳተፈ ልማት እንደሌለ ማወቅ አለበት፡፡ ሁሉንም ነገር መንግሥት ይሠራዋል ብሎ በመተው ሳይሆን ለልማት ከሚንቀሳቀስ ከውስጥ ከውጪ ካሉት የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር እጅና ጓንት ሆኖ መሥራት እንዳለበት ሕዝብ ማመንና የድርሻውን መጫወት አለበት፡፡


የግል ዘርፉ ካልተሳተፈ ልማት የለም፡፡ ነገር ግን ደግሞ የግል ዘርፉ ራሱም የድርሻዬን መጫወት አለብኝ ብሎ ማመን አለበት፡፡ ሕግን ማክበር፣ ከሙስናና ከሕገወጥነት መራቅ፣ ከመንግሥት የሚጠበቅ ግብር፣ ቀረጥና ሌላም ሌላም ግዴታውን መወጣት ይኖርበታል፡፡ መንግሥት ሲሳሳትና መስመር ሲለቅ መውቀስና ትክክለኛውን መንገድ ማሳየት ከግል ዘርፉ ይጠበቃል፡፡

ሲቪል ማኅበረሰቡም የልማት ጉዳይን ለመንግሥት ትቶ የአገርን ልማትና ከድህነት መላቀቅ ትግል ከሩቅ የሚመለከት መሆን የለበትም፡፡ እኔም ድርሻና ግዴታ አለብኝ በማለት ሕግን ተከትሎ፣ ከሙስና ርቆ፣ ግዴታውን ፈጽሞ የድርሻውን የሚጫወት ሲቪል ማኅበረሰብ መሆን አለበት፡፡ የድርሻውን ሚና እየተጫወተ፣ መንግሥት ትክክለኛ ጉዞ ሲጓዝ እየደገፈ፣ ሲሳሳት እየወቀሰና መንገድ እየጠቆመ ግዴታውን የሚወጣ ሲቪል ማኅበረሰብ መሆን አለበት፡፡

በአገር ውስጥ የሚኖሩም ሆኑ ዳያስፖራ ኢትዮጵያውያን ወገኖች በገንዘባቸው፣ በዕውቀታቸው፣ በልምዳቸውና በሙያቸው አገር ከድህነት ተላቃ የበለፀገች እንድትሆን የድርሻቸውን መጫወት አለባቸው፡፡ የሩቅ ተመልካች ሆነው የሚተኙ መሆን የለባቸውም፡፡ ‹‹ክቡር ትሪቢዩን›› ተቀምጠው ‹‹ካታንጋ›› ባለው ላይ የሚያፌዙ መሆን የለባቸውም፡፡ የድርሻቸውን ይጫወቱ፡፡ ጉድለት ሲያዩ ማረሚያና ማስተካከያ ይሰንዝሩ፡፡

 በአጠቃላይ ስናየው ሁሉም ኢትዮጵያዊ መንግሥትም፣ ሕዝብም፣ ፖለቲከኛውም፣ የግሉ ዘርፍም፣ ሲቪል ማኅበረሰቡም፣ ምሁሩም፣ ዳያስፖራውም ባለው አቅም ሁሉ የሚጠበቅበትን ካበረከተ ውጤቱ ዕድገትና ብልፅግና ነው፡፡ ምርጫውም በተግባር ሀብትና አዲስ ሕይወት ሆነ ማለት ነው፡፡ 
በተግባር ከዓለም እንማር፡፡ እነብራዚል በአጭር ጊዜ ውስጥ ከድህነት ተላቀው ከበለፀጉት አገሮች ተርታ ተሰልፈዋል፡፡ የዲሞክራሲና የልማት አርዓያ እየሆኑ ናቸው፡፡ ደቡብ ኮሪያ ከሃምሳ ዓመታት በፊት ደሃ አገር ነበረች፡፡ አሁን የበለፀገች ናት፡፡ በጦርነት የምትታወቀው ቬትናም አሁን በዕድገቷ እየታወቀች መጥታለች፡፡ ዕድገት እንደሚቻል፣ ከድህነት መላቀቅ እውን ሊሆን እንደሚችል በአፍሪካም  በጋና በኩል ጭላንጭል እየታየ ነው፡፡ ይቻላል፡፡

ይሁንና ቆራጥ ዕርምጃ ያስፈልጋል፡፡ ሕዝብና መንግሥት እጅ ለእጅ ተያይዘው መጓዝ አለባቸው፡፡ የግሉ ዘርፍ ተጠናክሮና ተከብሮ የሚጓዝ መሆን አለበት፡፡ የሲቪል ማኅበረሰቡም ሚናውን የሚጫወትበት ጉዞ መኖር አለበት፡፡ ባለዕውቀትና ባለሙያ የሚከበርበትና የሚሳተፍበት ጉዞ ሊኖር የግድ ነው፡፡ ተነጣጥሎና ተጠላልፎ ውጤት የለም፡፡ 
ይህ ሁሉ የሚሆነው ግን መንግስት እኔ ብቻ ነኝ ከሰማይ በታች የማስተዳድው እያለ ያለውን ዲስኩር መተውና ሕዝቡ ያስተዳድረኛል ብሎ የመረጠውንና ተቀብሎ ሲኖር ብቻ ነውና መንግስት ይህን ተገንዝቦ አውቆ መኖር ግድ ይላልና ያለበለዚያ ዋጋ ከፋዮች መሆን አይቀርምና !መጠንቀቁ ተገቢ ነው።የምንፈልገውን አቆይተን የማንፈልገውን አስወግደን የራሳችንን ሕዝብ መታደግ የምንችለው እራሳችን ብቻ ነን ይህ ካልሆነ ግን ተጠያቂዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ እንሆናለን፡፡
በአንድ ላይ ካልተጓዝን ጉዞው ውድቀት ነው፡፡ አማራጩም ድህነትና እርዛት ነው፡፡ እጅ ለእጅ ተያይዘን ከተጓዝን አማራጩ ዕድገትና ልማት ነው፡፡ ከድህነት መላቀቅ ነው፡፡ በታሪክ ተመስግኖ ተከብሮ መኖር ነው፡፡ ዲሞክራሲና ብልፅግና ነው፡፡ የአገርና የሕዝብ የጋራ ድል ነው፡፡ 
                                                            ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!
                                                                       ከዘካሪያስ      

No comments:

Post a Comment