Monday, December 24, 2012

ኢትዮጵያ ላይ ላዩን ስትታይ፤ የተረጋጋች ሰላማዊ አገር ትመስላለች።

                       ክፍል ሁለት
የአፈና ፕሮፓጋንዳ ለሃይማኖት አክራሪነት ያመቻል
የአገራችን የሃይማኖት ተቋማትና ቡድኖች፣ ከአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ ጋር በጥብቅ የተሳሰሩ ናቸው። ለዚህም ነው፤ የፖለቲካ ለውጥና አለመረጋጋት በሚፈጠርበት ወቅት፤ በሃይማኖት ተቋማትና ቡድኖች ውስጥም የተለያዩ ቀውሶችና አዳዲስ እንቅስቃሴቶች የሚቀጣጠሉት። ኢህአዴግ ስልጣን ሲይዝ፣ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሲኖዶስ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ከመነከሩም በተጨማሪ አወዛጋቢ ሹም ሽር እንደተካሄደበት ይታወሳል። በየአካባቢው ግጭት፣ እስርና ግድያ ሲፈጠሩ መቆየታቸውም አይዘነጋም። ከስልጣን የተሻሩት ፓትሪያርክ ከአገር ወጥተው በአሜሪካ ከሌሎች የሃይማኖት ተቋም መሪዎች ጋር ስደተኛ ሲኖዶስ አቋቁመዋል፤ ጳጳሳትን ሾመዋል። ውዝግቡ ለ20 አመታት መፍትሄ ባለማግኘቱ እርቅ አልወረደም። የአገር ቤቱ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ባለፈው ነሃሴ ወር ህይወታቸው ቢያልፍም፣ እስካሁን ሲኖዶሱ አዲስ ፓትሪያርክ ሳይመርጥ ወራት ተቆጥረዋል። 
ኢህአዴግ ስልጣን ሲይዝ ጀምሮ ከውዝግብ ያላመለጠው የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤትም እንዲሁ፣ በየጊዜው አወዛጋቢ በርካታ ሹም ሽሮችን እንዳካሄደ፣ ከዚሁም ጋር በየጊዜ ግጭት፣ እስር፣ ግድያ እንደተከሰተ ይታወቃል። የካቲት 1987 ዓ.ም በአዲስ አበባ የዘጠኝ ሕይወት ያለፈበትን ግጭት መጥቀስ ይቻላል። የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት በዘንድሮው ምርጫም ከውዝግብ አልዳነም። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአዲስ አበባና በተለያዩ ክልሎች ግጭቶች ተከስተዋል። የፕሮቴስታንት ቤተክርስትያናት ውስጥ የፖለቲካ መልክ ያላቸው እንቅስቃሴዎች አነስተኛ ቢመስሉም፤ ከፖለቲካው አየር ጋር በውዝግብና በክፍፍል እንደሚታመሱ፣ ኢህአዴግ ስልጣን በያዘበት ወቅት ታይቷል። 

በእርግጥ፣ ኢህአዴግ ላዩን ስትታይ ገናና ፓርቲ ይመስላል ግን ውስጡ ቅል ነው፣ በየጊዜው የሚከሰቱ ግጭቶችን እየገደለ፣ ደም እያፈሰሰ እድሜውን ለማራዘም ችሏል እስከመቼ? ነገር ግን፣ በሃይማኖት ተቋማት ውስጥም ሆነ፣ ሃይማኖትን ሰበብ አድርገው በተሰባሰቡ ቡድኖች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶች በጣም አስቸጋሪ እንደሆኑ አይካድም። በጂማ በርካታ ሰዎች ሕይወታቸውን ያጡበት ግጭት አንድ ምሳሌ ነው። የግጭቶቹ መነሻና መድረሻ አስቀድሞ ለመገመት ያስቸግራል። ግን ለመቀጣጠል ዝግጁ የሆነ ቤንዚን በአንዳች ምክንያት መቀጣጠሉ አይቀርም። ከወልቃይት ስኳር ፋብሪካና ከዋልድባ ገዳም ጋር በተያያዘ ምን ያህል ግርግር እንደተፈጠረ አይታችኋል። የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ምርጫና ከአወልያ ትምህርት ቤት ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባና በተለያዩ የክልል ከተሞች የተከሰተውን ግጭት ታዝባችኋል። አንዳንዱ ከሃይማኖት ነፃነት ጋር የተያያዘ ነው። 
በሃይማኖት ሰበብ የሚፈጠር ውዝግብና እና የአክራሪነት ግጭት በቀላሉ ከቁጥጥር ውጭ ሊሆን የሚችል ከፍተኛ የፖለቲካ አደጋ ነው። በጣም አሳሳቢው ነገር፣ የሃይማኖት ነፃነትንና የሃይማኖት አክራሪነት ለይቶ ለግለሰብ ነፃነት በፅናት የሚቆም ብዙ ሰው የለም። የሃይማኖት ነፃነትን መደገፍና የሃይማኖት አክራሪነትን መከላከል የሚቻለው፣ ለሃሳብ ነፃነት (ለግለሰብ ነፃነት) ከፍተኛ ክብር ሲኖረን ነው። ነገር ግን የሃሳብ ነፃነትን በሚጥስ የመንግስት ፕሮፓጋንዳ ተጥለቅልቀን እየኖርን፤ ለሃሳብ ነፃነት በፅናት የመቆም ብርታት እንዴት ሊኖረን ይችላል? 
ከላይ እንደጠቀስኩት፤ መሰረታዊው የፖለቲካ ጥያቄ፤ እያንዳንዱ ሰው፣ የማሰብ፣ የመደራጀትና የመምረጥ ነፃነት ሊኖረው ይገባል ወይ?” የሚል ነው። “የግለሰብን ነፃነት የመጣስ ስልጣን የያዘ አካል መኖር አለበት ወይ?” ነው ጥያቄው። የመንግስት ስልጣን የያዙ ሰዎች የግለሰብን ነፃነት (የሃሳብ ነፃነት) የመጣስ መብት አላቸው የምንል ከሆነ፤ አክራሪዎችም መብት አለን ይላሉ።
ስልጣን የያዙ ሰዎች፣ ለነሱ የማጥማቸውን ሃሳብ በማፈን አገሬውን በፕሮፓጋንዳ የሚያጥለቀልቁት ለምንድነው? “ለአገር እድገትና ለህዝብ ጥቅም የሚበጅ ልማታዊ አስተሳሰብ እንዲሰፍን እንፈልጋለን” ይላሉ። ... ይህንንም አገራዊ መግባባት (national consensus) ይሉታል። እያንዳንዱ ሰው የማሰብና ሃሳቡን የመግለፅ ነፃነት ተከብሮለት፤ ተወያይቶና ተከራክሮ... አብዛኛው ሰው ተቀራራቢ አስተሳሰብ ቢይዝ ችግር የለውም። የተለያዩ ሃሳቦች እንዳይገለፁ በማፈን፣ ሁሉም ሰው በባለስልጣን የተነገረውን ሃሳብ እንዲይዝ በፕሮፓጋንዳ መጠዝጠዝ ግን ሌላ ጉዳይ ነው። የሃይማኖት አክራሪዎችምኮ ከዚህ የተለየ ብዙም ክፋት የለባቸውም። “ለሰው ልጅ ፅድቅ የሚበጅ፣ ገነት ለመውረስ የሚያስችል የፈጣሪ መንገድ እንዲሰፍን እንፈልጋለን” ይላሉ። ... ይህንንም “የሃይማኖት እምነት” ይሉታል። የመንግስት ፕሮፖጋንዳን በዝምታ የሚቀበል ስርዓት፤ አክራሪዎችን የመከላከል አቅምና መከራከሪያ መርህ አይኖረውም። ብቸኛው መከላከያ የግለሰብ የሃሳብ ነፃነት እንዲከበር ማድረግ ነውና። 

የብሄር ብሄረሰብ ፓለቲካ፣ ለዘረኝነት ቅስቀሳ ይመቻል
የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከሲዳማ ዞን ተነጥሎ ይዋቀራል በሚል ወሬ ሰበብ በከተማዋና በዙሪያዋ ተፈጥሮ የነበረውን ስጋት ታስታውሳላችሁ - ከተማዋ የእገሌ ብሄር ነች፤ የእነእከሌ ነች በሚል። 
ከጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ህልፈት በኋላ ኢህአዴግ ሶስት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችን ለመፍጠር ወራት ፈጅቶበታል - የብሄር ተዋፅኦ ለመቀመር። ለነገሩ፤ ኢህአዴግ አንጋፋ መሪዎችን በአዳዲስ መተካት ሲጀምር ጎልቶ የተነሳው የመጀመሪያ ጥያቄ ከብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካ ጋር የተያያዘ ነው - የእገሌ ብሄረሰብ ስልጣን አላገኘም፤ የእንቶኔ ተጎዳ በሚል። ለነገሩ፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ወሬ በተነሳ ቁጥር፤ ወዲያውኑ ብቅ የሚለው ጉዳይ የዘርና የብሄር ብሄረሰብ ተወላጅነት ሆኗል - ከሙስና ጋር ተቆራኝቶ። በብሄር ብሄረሰብ ስም በመቧደን የሚፈጠር የስልጣን ሽኩቻና ግጭት አገሪቱን ሊያናውጥ የሚችል ሌላኛው የፖለቲካ አጀንዳ ነው። የግለሰብ የመደራጀት ነፃነትን የሚጥስ የብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካ፤ የግለሰብ ነፃነትን ለሚጥስ የዘረኝነት ቅስቀሳ ያጋልጣል።
ገናና መንግስትና የፖለቲካ ሸባሪነት ይመቻል
ሶስተኛው የፖለቲካ አጀንዳ የመንግስትን ስልጣን ሙሉ ለሙሉ ጠቅልሎ እድሜ ልክ እንደ ርስት የመቆጣጠር አባዜ ነው። ኢህአዴግ ቢያንስ ለሚቀጥሉት ሃያ አመታታ ያለ ተቀናቃኝ ስልጣንን በብቸኝነት ይዞ ለመቆየት ቆርጧል። ብዙ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ኢህአዴግን በማስወገድ ስልጣን ለመያዝ የሚመኙ ናቸው። የጠላትነትን መንፈስ ያሰፍናል - አሁን የምናየውን አይነት። ለምሳሌ ከ2002 ዓ.ም ወዲህ ኢህአዴግ በፌደራልና በክልል፤ በወረዳና በቀበሌ ከ99.5% በላይ በማሸነፍ ሙሉ ለሙሉ ስልጣን መቆጣጠሩ አገሪቱን ወደ አለመረጋጋት ይወስዳታል ብለው እንደሚያስቡ የአሜሪካ እና የአውሮፓ መንግስታት በተደጋጋሚ ገልፀዋል። 
የስልጣን ጉዳይ ውስጥ ከመግባት በእጅጉ የሚጠነቀቀው የአለም ባንክ ሳይቀር ሰሞኑን ይፋ ባደረገው ሪፖርት ውስጥ፤ ኢህአዴግ ከላይ እስከ ታች ስልጣኑን አስፋፍቶ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ቦታ ማጣታቸውን መዳከማቸው፤ ውጥረትን አስከትሏል ሲል ፅፏል። የፓርቲዎች የምርጫ ፉክክር ሲጠፋ፤ ስልጣን ለመሻማት የፓርቲዎች መቆራቆስና መጋጨት ስለሚከተል፤ ትልቅ አጀንዳ መሆን ይገባዋል። ነገር ግን የፓርቲዎች ፉክክር ከዜጎች የመምረጥ መብት ውጭ ትርጉም የለውም። ነገር ግን ዋናው ጥያቄ የፓርቲዎች ቦታ ማጣት ሳይሆን፤ ዜጎችን አማራጭ የማሳጣትና የመምረጥ መብታቸውን ያለማክበር ገዳይ ነው። አድራጊ ፈጣሪ ፈላጭ ቆራጭ ገናና መንግስት የመሆን ጉዳይ ነው። ግለሰቦች የራሳቸውን ሕይወት በራሳቸው ምርጫ የመምረጥ ነፃነታቸውን እንዲያጡ የሚያደርግ ገናና መንግስት ሊፈጠር የሚችለው፤ የዜጎችን የሃሳብ ነፃነትና የመደራጀት ነፃነት በመርገጥ ነው። የፖለቲካ አሸባሪነትም ተመሳሳይ መንገድ የሚከተል ነው። በሌላ አነጋገር፤ ሶስቱ የፖለቲካ አጀንዳዎች እርስ በርስ የተሳሰሩ የግለሰብ ነፃነት አጀንዳዎች ናቸው። ለማንኛውም የህዝብ መብት ይከበር !!! የአምባገነን መጨረሻው ሞት ነው !!
                                                ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!
                                                                     ከዘካሪያስ

No comments:

Post a Comment