Thursday, December 27, 2012

መተካካት አሉታዊ ጎንም አለው ።

የ‘ቦተሊካ’ ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…ትንሹ ልጅ አባቱን “አባዬ፣ ፖለቲካ ማለት ምን ማለት ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ አባትዬውም እንዲህ ሲል ይመልስለታል፡፡
“የእኔ ልጅ፣ ይህንን ለማስረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡ ግን እስቲ ልሞክር፡፡ ለምሳሌ ሠርቼ ገንዘብ የማመጣው እኔ ስለሆንኩ ካፒታሊዝም ነኝ እንበል፣ እናትህ የገንዘቡን ወጪ ስለምትቆጣጣር መንግሥት ነች እንበል፣ የእኛ ሀላፊነት ያንተን ፍላጎት መጠበቅ ስለሆነ አንተን ደግሞ ህዝብ ነህ እንበል፣ ሞግዚቷ የሠራተኛው መደብ ነች እንበል፣ ትንሹ ወንድምህን ደግሞ መጪው ጊዜ እንበለው፡፡ እስቲ ይሄን አስብና ስሜት ይሰጥ እንደሁ ተመልከት…” ይለዋል፡፡ ልጁ አባቱ ስለነገረው ነገር እያሰበ ሄደ፡፡ ያን ዕለት ሌሊት ትንሽ ወንድሙ ሲያለቅስ ሰማና ተነስቶ ወደ ክፍሉ ሄደ፡፡ ትንሹ ልጅ ሽንቱን ሸንቶ ስለነበር ዳይፐሩ በጣም እርሶ ያያል፡፡ ወደ ወላጆቹ ክፍል ሲሄድ እናቱ ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ወስዷታል፡፡ 

እሷን ላለመቀስቀስ ብሎም ወደ ሞግዚቷ ክፍል ይሄዳል፡፡ በሯ ተቆልፎ ስለነበር በቁልፍ ቀዳዳ አጮልቆ ሲያይ አባቱ ሆዬ ከሞግዚቷ ጋር ተኝቶ ፍቅር ሲሠራ ያያል፡፡ ተስፋ ይቆርጥና ወደ ክፍሉ ተመልሶ ይተኛል፡፡
በማግስቱ ልጅየው ለአባቱ “አባዬ፣ አሁን ፖለቲካ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ገብቶኛል፣” ይለዋል፡፡ አባትየው ደስ ይለውና “ጎሽ የእኔ ልጅ፣ እስቲ ፖለቲካ ምን እንደሆነ ንገረኝ” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ልጁ ምን አለው መሰላችሁ…“ፖለቲካ ማለት ካፒታሊዝም ከሠራተኛው መደብ ጋር ተኝቶ ፍቅር ሲሠራ፣ መንግሥት ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ወስዶታል፣ ህዝቡ ተረስቷል፣ መጪው ጊዜ ደግሞ በሽንት እርሷል” አለውና ቁጭ አለላችሁ፡፡
እንደ ወይኑ-ዛፍ ከመፎከር እንደ ባህር ዛፍ ረጅም መቆሚያን ማበጀት ይጠበቅብናል፡፡ የአዕምሮ ነፃነት፤ የተቋም ነፃነትም ሆነ ድርጅታዊ ነፃነት መላ ይፈልጋል፡፡ መላ የሌለው፣ ዕድሜ የለውም እንዲሉ! ባንድ ወገን ያለ ባህሪያችን ራሳችንን ችለን በነፃነት እንቆማለን ማለት ከንቱ ውዳሴ የሆነውን ያህል፤ በሌላ ወገን አበው እንደሚሉት “በአፍላ ጉልበታቸው ደብሩን ተክለው፣ ካህናትን ደልድለው፤ ሥራቱን አስተካክለው ያደራጁትን ሰዎች በአንድ ጀንበር ወግዱ ማለት እንዳይቻል እያወቃችሁ ስለምን ብልሃቱ ይጠፋችኋል?” ብሎ መጠያየቅ ዋና ነገር ነው፡፡ 
ጥያቄው፤ እንደማይክል አንጀሎ ጥበበኛ በመሆን ፍፁም ውስጣዊ ኃይል ቢኖረን ይሻላል (Intensive) ወይስ እንደ ኪሲንጀር ሁሉም ቦታ እጅን በማስገባትና አማካሪ በመሆን (Extensive እንዲሉ) ተፈላጊነት ማረጋገጥ (Indespensible) የሚለው ነው እንደየአገሩና እንደየዘመኑ አንዱ ወይም ሁለቱም ሊሠራ ይችላል፡፡
ማኪያ ቬሊ፤ ከመወደድ መፈራት ይሻላል ይላል፡፡ ፍርሃትን መቆጣጠር ይቻላል፤ ፍቅርን ግን በፍፁም! (Fear you can Control. Love, never.) ሌሎች እናጣሃለን ብለው በመፍራት ባንተ ቢመኩ እንጂ ወደውህ ወዳጅ ማድረጋቸውን/አጋርህ መሆናቸውን/አታፍቅር ነው ነገሩ! ዞሮ ዞሮ ምርጫው የራሳችን ነው - ወፍ እንደ አገሩ ይዘፍናል ነውና፡፡ አንድም፤ አገሬን በጣም እወዳታለሁ ማለትን በማብዛት እናቅፋታለን ብለን እንዳናንቃት እንጠንቀቅ እንደማለትም ነው፡፡ 
አገራችን የተያያዘችው ፖለቲካዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ውጣ-ውረድ ውስጥ፤ የፖለቲካ ሥልጣኑ ማህፈድ (Political Tower) አናት ላይ መገኘት ወይስ ግንድን ማጠንከር? ብሎ ራስን መጠየቅ ደግ ነው፡፡ “ቁልቋል የወደቀው ቅርንጫፍ ካበዛ በኋላ ነው” የሚለውን የትግሪኛ ተረት አንርሳ! 
እንደዕለት ፀሎት የማንዘነጋውን የሙስና ጉዳይ እናውጋ፡፡ “አታላይ ሰው አያሌ የሚያታልላቸው ሰዎች የሚያገኘው የሰው ልጅ በጊዜያዊ ጥቅሙ ተገዢ ስለሆነና አዕምሮውም የተወሳሰበ ስላልሆነ ነው” (ማክያቬሊ)፡፡ የሰው ልጅ ለሙስናና በሥልጣን ለመባለግ ቅርብ መሆኑን ሲነግረን ነው! በየዓይነቱ ሌብነትና ዘረፋ እንዳለ ቢታወቅም የሙስና ዶቃ የለውም፡፡ አዘለም አንጠለጠለም ያው ተሸከመ ነው - ቀልቀሎ ስልቻ፣ ስልቻ ቀልቀሎ፤ ነው! 
“በሉ እኔ ልሰናበት ምቀኛዬ መጣ!” ይላል የባህር ዳር አዝማሪ፤ ሌላ አዝማሪ ሲተካው፡፡ ቃሉን በቁሙ ከወሰድነው መተካካት አሉታዊ ጎንም አለው እንደማለት ነው፡፡ ቀና ቀናውን ያሳየንና ሂያጁም መጪውም በፍቅርና በዕድገት አኳያ ይተያዩ ዘንድ ተግተን እንፀልይ፡፡ ራዕይ ቅን ልቡና ይፈልጋልና “ልብና ልቦና ይስጠን” ብለን እናሳርግ እንደሰባኪው ካህን! 
አገራችን “ልጓም የሚጠብቀውን፣ ሜዳ የማይበቃውን ጮሌ ሠንጋ ፈረስ እንደ እንዝርት የሚያሾር ምርጥ ፈረሰኛ - መሪ፣ ምርጥ ኃላፊ፣ ምርጥ ባለሙያ፣ ምርጥ ካህን ወዘተ ትሻለች፡፡ አዲሱ አሮጌውን በሚተካበት ሂደት፤ ጉዳይ የሥልጣን - ሽግሽግ - ተኮር ሳይሆን ምርጥ አመራር የመፍጠር መሆን ይኖርበታል፡፡ አህያይቱን የመከራት ውሻ “ተይ ወይዘሮ አህያ አታናፊ:- የፊተኛው መቀስቀሺያ፣ ሁለተኛው መቅረቢያ፣ ይሄኛው መበያ ነው” እንዳለው ቀና አመራር ከዚህ ነፃ መሆን ይገባዋል፡፡ አለበለዚያ የዲሞክራሲም፣ የፍትሕም፣ የልማትም፣ የመልካም አስተዳደርም ተስፋ ያገሬ ባላገር አለ እንደሚባለው፡- “የፖለቲካ ነገር፣ መጀመሪያ ዘርዛራ ወንፊት፣ ቀጥሎ ጠቅጣቃ ወንፊት፣ በፍፃሜው መሹለኪያ የሌለው ድፍን ወንፊት” እንዳይሆን መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡
                                       ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!

No comments:

Post a Comment