Monday, October 21, 2013

ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ለሥራ መሄድ ሊታገድ ነው

ሳዑዲ ዓረቢያ በየወሩ እስከ 10 ሺሕ የቤት ሠራተኞችን ከኢትዮጵያ ትፈልጋለች
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ባለፈው ሐሙስ በተወካዮች ምክር ቤት አባላት አዲሱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ያደረጉትን ንግግር በማስመልከት ጥያቄ ቀርቦላቸው ባስረዱበት ወቅት፣ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ለሥራ የሚሄዱ ሰዎች ከመጪው ወር ጀምሮ ከመሄድ እንደሚታገዱ አስታውቀዋል፡፡ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት መግለጫ፣ ለሥራ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ በሄዱ ዜጎች ላይ የሚፈጸመው በደል ተባብሶ በመቀጠሉ ችግሮች እስኪሻሻሉ ድረስ ለስድስት ወር ያህል ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ መሄድ እንደሚከለከል አስታውቀዋል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት በሳዑዲ ዓረቢያ ጉብኝት ማድረጋቸውም የሚታወስ ነው፡፡

በሳዑዲ ዓረቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የቤት ሠራተኞች በአሠሪዎቻቸው የሚደርስባቸው ጥቃት ለከፍተኛ የጤና ችግር እያጋለጣቸው ሲሆን፣ አንዳንዶቹ የግድያ ወንጀል መፈጸማቸው ሲዘገብም ቆይቷል፡፡ በቅርቡ ሁለት ሕፃናት በኢትዮጵያውያን ተገድለዋል በሚል ምክንያት ኢትዮጵያውያውኑ ከአገራቸው እንዲባረሩላቸው በርካታ ሳዑዲዎች ሲወተውቱ ከርመዋል፡፡
በየወሩ እስከ አሥር ሺሕ ኢትዮጵያውያን የቤት ሠራተኞች የሚያስፈልጉት የሳዑዲ መንግሥት በኢትዮጵያውያቱ ላይ የተለያየ አቋም ሲያንፀባርቅ ቆይቷል፡፡ ሳዑዲ ጋዜት የተሰኘው ጋዜጣ ከሳምንታት በፊት እንዳስነበበው፣ ምንም እንኳ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ከአገር ይባረሩና ሌሎችም እንዳይመጡብን ቢባልም፣ ዕርምጃውን መውሰድ እንደማይቻል የሚገልጹ ኃላፊዎችን ጠቅሶ ዘግቦ ነበር፡፡
በሳዑዲ የጂዳ ንግድና ኢንዱስትሪ ምክር ቤት ውስጥ የሥራ ቅጥር ምልመላ የሚያካሂደው ኮሚቴ አባል ሙልታክ አል-ሐዝሚን ጠቅሶ ጋዜጣው እንደዘገበው፣ በአንድ ክስተት ላይ ተንተርሶ ሁሉንም ኢትዮጵያውን ከአገር አስወጡ ማለቱና ሌሎችም እንዳይመጡብን መባሉ ትክክል አይደለም በማለት ተከራክረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በወር እስከ አሥር ሺሕ የሚደርሱ ዜጎችን ለቤት ውስጥ ሠራተኛነት ለማቅረብ የምትችለው ብቸኛ አገር በመሆኗ፣ ሌላ አማራጭ እንደሌላቸው በመግለጽ ኢትዮጵያውያኑን ውጡ ማለቱ ተገቢ አይደለም ሲሉ ታቃውመዋል፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ ብሔራዊ የቅጥር ምልመላ ኮሚቴ ሊቀመንበር ሳዓድ አል-ባዳህ ግን ከኢትዮጵያ የቤት ሠራተኞችን መቀበሉ በአስቸኳይ መከልከል እንዳለበት አስጠንቅቀው ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የሳዑዲ ዓረቢያ አምባሳደር አብዱል ባኪ አጅላንን ጠቅሶ ሳዑዲ ጋዜት እንዳስነበበው፣ ኢትዮጵያውያኑ ሠራተኞች ወደ ሳዑዲ ከመጓዛቸው አስቀድሞ የሥነ ልቡና ምርመራ እንዲደረግላቸው አሳስበዋል፡፡
እንዲህ ያሉ መግለጫዎች ከሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ሲደመጡ ቢቆዩም መንግሥት በዝምታ መቆየቱ ስያስነቅፈው ቆይቷል፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን በአሠሪዎቻቸው ጥቃት ለሞትና ለአካል ጉዳት መዳረጋቸው ሲስተጋባ ሰንብቷል፡፡  ባለፈው ሐሙስ ፓርላማ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ለመጪዎቹ ስድስት ወራት ወደ ሳዑዲ መሄድ እንደሚቋረጥና ሁኔታው እየተጠና መሻሻል ሲኖር ሊፈቀድ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
በየወሩ እስከ 80 ሺሕ የሚደርሱ ወንዶችና ሴቶች ኢትዮጵያውያን ለጉልበትና ለሌላውም ዝቅተኛ ሥራ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ እንደሚያቀኑ ከሳዑዲ ዓረቢያ የተገኙ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ethiopian reporter

No comments:

Post a Comment