Monday, October 21, 2013

የተስፋዬ ገ/አብ በማር የተለወሱ መርዞች

በሙሉቀን ተስፋው 
ዛሬ እውነት ለመናገር ስለተስፋዬ /አብ ለመጻፍ ምንም ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ በርግጥ ወደ ፊት እንደምጽፍ እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ ሆኖም ባለፈው ሳምንትከላይፍ መጽሄትጋር ያደረገውን ቃለ መጠይቅ ሳነብ የግድ አሁኑ መልስ መስጠት አለብኝ ብዬ ተነሳሁ፡፡ ተስፋዬን የማውቀው በመጽሀፎቹ ነው፡፡ እንደ እድል ሆኖም መጀመሪያ ያነበብኩት የተስፋዬ መጽሀፍጥሩየሚባለውን ነው፡፡ ከስደት በኋላንስሃ ለመቀበልየሞከረበትን ድርሰቱን ማለቴ ነው፡፡
በጊዜው ይህ ሰው ማነው ብዬ ብዙ ጠየቅኩ፡፡ አንድ የወያኔ ባለስልጣን የነበረ ነግር ግንለሻቢያ ይሰልላል ተብሎ የተባረረ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ነውአሉኝ በዘመኑ ከኔ የተሻለ መረጃ አለን የሚሉ ሰዎች፡፡ ያም ሆነ ይህ ጎጋው ህዝብ በሀሜት የሚያወረውን ጉድ ተስፍሽ እውነት ነው አለን - በሁለቱ የስደት ማስታዎሻዎቹ፡፡ 

የጋዜጠኛው ማስታዎሻን በሶፍት ኮፒ እንዳገኘሁት በጽህፈት ስራ የተቀጠረች አንዲት ዘመዴን ፕሪንት እንድታደርግልኝ በስንት ግድ ለምኜ አነበብኩት፡፡ የቃላት አጠቃቀሙ፣ ሰዋሰዋዊ ፍሰቱ፣ ቀልቤን አስረስቶ በአንድ ቀን ሸመጠጥኩት፡፡ አልፎ አልፎ ያሉትን ግጥሞች በማስታዎሻዬ ገለበጥኳቸው፡፡ አድናቂው ሳይሆን አምላኪው የሆንኩ ሁሉ መሰለኝ፡፡
የተስፋዬን መጽሀፎች እየፈለግኩ ማንበብ ያስደስተኝ ነበር፡፡ በየቀኑ አንዳንድ መጽሀፍ ቢያሳትም ብዬም ተመኘሁለት፡፡ አንድ ቀን እንዲሁ አንድ ሌላ ወዳጄ የቡርቃ ዝምታን መጽሀፍ ላከልኝና አነበብኩት፡፡ ስለሰውየው የነበረኝ አመለካከት በአንድ አፍታ ተለወጠ፡፡ 
በተቻለኝ መጠን ከስሜት ለመጽዳት እየሞከርኩ የሰውዬውን ቀናነት ለማምጣት ታገልኩ፡፡ ከምርጫ 97 በኋላ (ቀኑን በትክክል አላስታውሰውም) ከአሜሪካ አማርኛ ድምጽ ሬዲዮ ጋር ቃለመጠይቅ ሲያደርግ ስለቡርቃ ዝምታ ድርሰቱ አንስተውለት ነበር፡፡ የጋዜጠኛውንና የተስፋዬን ንግግር ቃል በቃል ባላስታውሰውም መልዕክቱ ግን ይህ ነበር፡፡ 
የቪኦኤው ጋዜጠኛ ‹‹በቡርቃ ዝምታ መጽሀፍህ ሆን ብለህ በህወሓት ባለስልጣናት ታዘህ አማራውንና ኦሮሞውን ለማጋጨት ያዘጋጀኸው ነው ይባላል፡፡ ይኸው መጽሀፍ ለብዙ በተለያዩ ጊዜያት በአማራና በኦሮሞ ብሄረሰቦች መካከል ለተከሰቱ ግጭቶች መንስኤ ነው ተብሎ ይገመታል፡፡ አንተ ምን ትላልህ!›› አለው፡፡ ተስፋዬም መለሰ ‹‹በእውነት እንደዚያ ከሆነ የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ እጠይቃለሁ››፡፡ 
ይህ በገደምዳሜ የመለሰው መልስ ስሰማ ተስፋዬን ከልቡ የተጸጸተ መስሎኝ ነበር፡፡ አሁን በላይፍ መጽሄት ያደረገውን ቃለ መጠይቅ ሳነብ አሁንም ወደፊት በኢትዮጵያውያን ላይ እየቆየ የሚፈነዳፈንጅለማጥመድ ወደ ኋላ እንደማይል ያሳያል፡፡ እርግጥ ነው ይህን ተንኮሉን ከጡት አባቹ ሳይማረው የቀረ አይመስለኝም፡፡ 
ብዙዎቹ የህወሓት/ ኢህአዴግ ባለስልጣናት በጥቅም ተጋጭተው ከአገር ሲኮበልሉ ወይም ተቃዋሚ ፓርቲ ሲመሰርቱ ጠባቸው ከጓዶቻቸው እንጅ ከሀገሪቱ አሊያም ከህዝቡ ጋር ሆኖ አያውቅም፡፡ የተስፋዬን ጽዋ ብዙዎች ተግተውታል፡፡ በስልጣን ላይ ካሉት ውጭ ግን እንደተስፋዬ አገርን ለማቁሰል የተጋ ሰው የለም፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ሙሉ በሙሉ የሚያውቁት አንድም እግዚአብሄር አሊያም ራሱ ተስፋዬ ብቻ ናቸው፡፡ ተስፋዬም ላያውቀው ይችል ይሆናል፡፡ በርግጥም መሰሪነቱን ከተገነዘበ የሚያጠፋው አውቆ ስለሆነ አንድ ቀን ከዚህ ስህተቱ ጸድቶ ትክክለኛ ንስሃ ያገኝ ይሆናል፡፡ ካልሆነ ግን እድሜ ልኩን ለአንዳንድ የዋህ ኢትዮጵያውያንስኳር በመርዝ እየለወሰ መመገቡንአይተውም፡፡
የተስፋዬን መርዛማነት ለማወቅ ከዚሁ መጽሄት ጋር ያደረገው ቃለ መጠይቅ ብቻ በቂ ነው፡፡ ቢሆንም መጀመሪያ ንግግሮቹን እንመልከትና ሌሎች አባሪዎችን ይህ አስተሳሰቡ እንዴት እንዳመጣው መላ ምት እጨምራለሁ፡፡ ሰዎች ስለሱ ያሉትን ሳይሆን እርሱ ስለ ራሱ የተናገረውና የጻፈውን ብቻ ዋቢ አደርጋለሁ፡፡
በላይፍ መጽሄት ጋዜጠኛ ‹‹በቡርቃ ዝምታ እና በቢሾፍቱ ቆሪጦች መጽሃፍትህ የተጸጸትክበት አጋጣሚ አለ? አሁንም ያለህ አቋም የመጽሐፍቱ ነጸብራቅ ነው?›› ለቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ ‹‹በመፃህፍቱ የምፀፀትበት ምክንያት የለም።›› ብሎ በአራት ነጥብ ይደመድማል፡፡ የቢሾፍቱ ቆሪጦችን ሲጽፍ እድሜውም እውቀቱም ያልጎለበት በመሆኑ ስነ ጽሁፋዊ ደረጃው ወረድ ያለ ቢመስልም በእርሱ እንዳልተጀመረ እነ በዓሉ ግርማንና ብርሀኑ ዘሪሁንን በማነጻጸር ጥግ ሲፈልግ ይስተዋላል፡፡ በተረፈ ግን ‹‹የቡርቃ ዝምታን በመፃፌ እንደማልፀፀት ደጋግሜ ተናግሬያለሁ። የኦሮሞ ህዝብ ሰብእና ላይ የተፈፀመውን ግፍ የሚያሳዩ የጥበብ ስራዎች ወደፊትም መፃፍ አለባቸው። መሸፋፈን መፍትሄ አይሆንም። አብሮ ለመኖር ባለፈው ታሪክ ላይ መተማመን ይገባል። የቡርቃ ዝምታ የጭቆናውን ክብደት ለማሳየት የሞከረ መፅሃፍ ነው። የጭቆናውን ክብደት ማወቅ ተከባብሮ ለመኖር ያግዛል እንጅ የዘር ጦርነትን አይቀሰቅስም›› ብሎ ምንም ስህተት እንዳልሰራ ሰውና የኢትዮጵያ ታሪክ እና የኦሮሞ ባህል ምሁር መስሎ ይናገራል፡፡ 
ተስፋዬ በሰዓቱ ይህን የጻፈበት ምክንያት ግልጽ ነው - ለእንጀራ ሲል በዚሁ ድርሰቱ ህወሓቶችን ‹‹የእግዚአብሄር ቅዱሳንና ምርጦች›› አድርጎ ነው የገለጻቸው፡፡ ድርሰቱ በተለይየጭራቁን አማራ የኦሮሞ፣ የትግራይንና የኤርትራን ማህበረሰባት እንዲሁም የደርግን፣ የህወሓትንና የሻቢያን ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች አንሸዋሮ ያሳየናል፡፡ የኦሮሞውን ማህበረሰብየደጎች ሁሉ ቁንጮአድርጎ ሰይሟቸዋል፡፡ የኦሮሞ ማህበረሰብ እርግጥ ነው ደግ ነው፡፡ ማለት ግን ሌላው ኢትዮጵያዊ ጭራቅ ነው ማለት አይደለም፡፡ ተስፋዬ ግን ያደረገው ይህን ነው፡፡ ደግነቱም በተስፋዬ መነጸር አይደለም፡፡ ተስፋዬ ኦሮሞውን ማህበረሰብ በደግነታችሁ ጭራቆቹ አማራዎች ገብተው ተጫወቱባችህ፡፡ አጥብቆ ደግነት ለበግም አልበጃት፣ ተነስ ለምን ትፈራለህ! ዓይነት ነው ምክሩ፡፡ ይህን የሚለው ለኦሮሞው ተቆርቁሮ ሳይሆን አማራውን መበቀያ ዘዴ ስለሆነለት ነው፡፡ 
ከመጽሀፉ ከየትኛውም ገጽ ላይ በአጋጣሚ ብትገልጡ አማራውን ‹‹ሰወ በላ ጭራቅ›› አድርጎ የሚያሳይ አንድ አረፍተ ነገር አይጠፋም፡፡ ገና ክፍል አንድ ብሎ ሲጀምር ‹‹ነፍጠኞች ወዮላችሁ!›› ብሎ ያስፈራራል፡፡ መቼም ተስፋዬ ይህን ቃል የተጠቀምኩት አማራዎችን ለመግለጽ አይደለም ብሎየፖለቲካ ካሊፕሶመጨዋት አይፈልግም፡፡ ተስፋዬ በርግጥም እንደ ህወሓት ሎሌነቱ ጌቶቹን ለማስደሰት ፍላጎት ባይኖረው ኖሩ በህወሓት ዘመን የደረሱትን ግፎችና በደሎች በኋላ ላይ ወጥቶ ከሚለፈለፍ በዚሁ ድርሰቱ እንደ በዓሉ ግርማ በአገዛዙ ስር ሆኖ መናገር ይችል ነበር፡፡ ግን ተስፋዬ ያኔ የነበረው ልብና ኩላሊት ከጌቶች የተዋሰው ነበር፡፡ 
የተስፋዬ /አብ ድርሰቶች ከሁለቱ የስደት ማስታዎሻዎች ውጭ ተመጋጋቢ አይደሉም፡፡ አንዱ አንዱን ያፈርሰዋል፡፡ በቡርቃ ዝምታ እና ተራሮችን ያንቀጠቀጠ ትውልድ ላይ ያወደሳቸውን ህወሓቶች በስደት ማስታዎሻዎቹ ላይ ይቦጫጭቃቸዋል፡፡ ምን አልባትም ቀጥታም ቢሆን ከስድብ ያመለጠው የሞተው ሀየሎም አርዓያ ብቻ ነው፡፡ እርሱም በትንሹም ቢሆን ያደገበት ኢትዮጵያዊ ባህል ሙት አይወቀስም የሚለው ባህል ተጽዕኖ አሳድሮበት ይመስለኛል፡፡ 
የተስፋዬን መልስ ሁሉንም አንድ በአንድ ማዬት አታካች ብቻም ሳይሆን ጊዜም ስለማይበቃ ጎላ ጎላ ያሉትን ብቻ ለማየት እየሞከርኩ ነው፡፡ 
አንድ የተገነዘብኩት ነገር ቢኖር በህወሓት/ኢህአዴግ ፓለቲካ ስርዓት ውስጥ አልፈው በኋላ በጥቅም ተኳርፈው የሚወጡ ሰዎች ለመሳደብና ግለሰቦችን ለማብጠልጠል የሚሆናቸው የለም፡፡ ተስፋዬም ከነዚህ ሰዎች አንዱ ነው- ማለትም የመጀመሪያው፡፡ እናም ተስፋዬ ስለ ኦሮሞ ህዝብ መብት ለቀረበለት ጥያቄ ከመመለስ ዶክተር ነጋሶ አናት ላይ ፊጥ ማለት ፈለገ፡፡ ‹‹ነጋሶ›› አለ ‹‹ነጋሶ ጭንቅላታቸውን ተናግረው አያውቁም። ሌሎችን ለማስደሰት በማሰብ የመናገር ልማድ አዳብረዋል። ነጋሶ አሁን የአንድነት ሊቀመንበር ናቸው። አራተኛ ድርጅታቸው መሆኑ ነው። ከኦነግ ወደ ወያኔ፣ ከወያኔ ወደ አንድነት ሲዘሉ ምንም አልተደናቀፉም። መርህ ያለው ሰው እንዲህ በቀላሉ ከአንድ ጫፍ ወደ ሌላ ጫፍ መዝለል አይቻለውም። ጨለንቆ ላይ ጉድጓድ አስቆፍረው አፅም እየሰበሰቡነፍጠኛውንያወግዙ እንዳልነበር፣ አኖሌ ላይ ስለጡት መቆረጥታሪክ ሲያስተምሩ እንዳልነበር አሁን 180 ዲግሪ ተገልብጠው የራስ ጎበና ዳጪ ተከታይ ሆነዋል…››፡፡ 
ዶክተሩና ተስፋዬ መነጻጸር የሚችሉ ሰዎች አይደሉም፡፡ ነጋሶ መለስን ‹‹አሁንስ መንግሰቱ /ማርያምን መንግሰቱ /ማርያምን መሰልከኝ›› ብለው በድፍረት የተናገሩ ሰው ናቸው (ዳንዲ የነጋሶ መንገድ)፡፡ በመንግሰት የቀረበላቸውን አምሃ ትተው ወደ ሰላማዊ ትግሉ ገብተው ለህዝባቸው ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ናቸው፡፡ በተቃራነው ተስፋዬ ደግሞ ማንነቱን በደንብ (ወደ መጨረሻ እመጣበታለሁ) የማያውቅ ግራ የገባውና ሰዎችንም ግራ በማጋባት መቀጠል የሚፈልግ ከይሲ ግለሰብ ነው፡፡ ተስፋዬ መለስን ሳይሆን ከመለስ በታች ያሉ ባለስልጣኖችን ደፍሮ የተናገረው ካባረሩት በኋላ ባህር ማዶ ሆኖ ነው፡፡ ያኔ ደግሞ ላገር በማሰብ ሳይሆን አንድም በበቀል አሊያም አወቅኩሽ ናቅኩሽ በሚል ቀሽም ፈሊጥ ነው፡፡ የተስፋዬ መርህ ያለው ሰው ማለት እንግዲህ ይህ መሆኑ ነው፡፡ በእኔ እምነት አንድ ሰው ንጹህ እንቁላል የመሰለው የገማ መሆኑን ያወቀ እለት ከጣለው አብሮ ከመበላሸት ይድናል፡፡ ዶክተር ነጋሶም ያደረጉት ይህን ይመስለኛል፡፡ ስልጣን ያለውን ለማስደሰት የሚተጉ ቢሆን ኖሮ የነበራቸው ጥቅማጥቅም ተብትቦ ባስቀራቸው ነበር፡፡ ዶክተሩ 180 ዲግሪ ከዞሩ በተስፋዬ አስተያዬት እርሱ ራሱ ስንት ዲግሪ ዞረ ማለት ነው!! ተስፋዬ ነውሩን ሽጦ የበላ ሰው ስለሆነ ሰው ይታዘበኛል ብሎ እንኳ አያስብም፡፡
የተስፋዬ ድስኩር ይቀጥላል፡፡ ጋዜጠኛው ስለ ኢትዮጵያና ኤርትራ የወደፊት ተስፋ ሲጠይቀው ‹‹ሁለቱ ሀገሮች አብረው ለመኖር አይደለም መልካም ጎረቤት ከሆኑ በራሱ ትልቅ ስኬት ነው›› ሲል ተስፋ ያስቆርጠናል፡፡ ‹‹በመሰረቱ የኤርትራ ጥያቄ እኮ የነጻነት ጥያቄ ነው›› በማለት ይናገራል፡፡ ቅርብ ጊዜ ኢሳይያስ አፈወርቂ ካገራቸው ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ‹‹ኢትዮጵያ ኤርትራን ቅኝ ገዝታ አታውቅም›› ብለው አጋድመው የቀየሩትን ሀሳባቸውን ስላልሰማ ይመስለኛል ይህን የተናገረ፡፡ በዚህ ጥያቄ መልሱ የሁለቱን ሀገሮች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት መሻሻል ተስፋ ውሃ ደፋበት፡፡ 
ተስፋዬ /አብ በኢትዮጵያ ያለውን የትግል አካሄድ አዋጭ አይደለም በማለትም ሀገሪቱን ለማተራመስ ያለውን ምኞት ተናግሯልም፡፡ 
ተስፋዬ ይህን ያክል በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውን ላይ ለምን ጥላቻ አደረበት ብሎ የሚጠይቅ አንባቢ አይጠፋም፡፡ እኔምየቢሆን ምክንያቶችንእንደሚከተለው እገልጻለው፡፡ በስነ ልቦና ሙያ በተለይም እንደ ሳይኮአናሊስቶች (Psychoanalysts) እምነት ከውስጥ የተደበቀን ባህሪ ለማወቅ ሰዎችን በሚናገሩትና በሚጽፉት (Slip of tongue and slip of pen) ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህ መሰረት የተስፋዬን አንደበቶችና ድርሰቶች ስንዳስስ እንዲህ እናገኘዋለን፡፡ 
1. ተስፋዬ የማንነት (Identity Crisis) ቀውስ ተጠቂ ነው፡፡ በዚሁ መጽሄት ላይ ከኢትዮጵያና ከኤርትራ ስሜትህ ለየትኛው ነው ብሎ ሲጠይቀወው ቀጥታ መመለስ አልፈለገም፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ተወልጀባታለሁ፣ ኤርትራም ደሜ ናት፣ ማንነት የብዙ ነገሮች ግባዓት ውጤት ስለሆነ ለሁለቱም ሀገሮች ስሜት አለኝ፤ ጥያቄው ስለዜግነት ከሆነ ግን ሆላንድ የዜግነት ሀገሬ ሆናለች፣ ለቀሪው ጊዜዬ ሆላንዳዊነቴ በቂ ነው›› ይላል፡፡ ይህ መልሱ ከሁለት ወገኖች ጋር በሰላም ያኖረዋል፡፡ኢትዮጵያዊ ስሜት አለኝቢል የሻቢያ ባለስልጣናት ጥርስ ይገባል፣ ኤርትራዊ ስሜት አለኝ ቢል ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ በማር ለውሶ መርዝ የሚመግባቸው ሰዎች ሊነቁበት ነው፡፡ እናም ተስፍሽ ይህችን ጥያቄ አጋድሞ መለሳት፡፡ በሌላ በኩል ከሀገር እንደኮበለለ ሪፓርተር ጋዜጣ እንዲህ ሲል ጥያቄ አቀረበለት፡፡ ‹‹ኢትዮጵያዊ ነኝ ትላል!›› ተስፋዬ ሲመልስ ‹‹ኢትዮጵያዊ ነኝ ግን ግራ የገባው ኢትዮጵያዊ›› ሲል መለሰ፡፡ 

ተስፋዬ ከአስርት ዓመታት በኋላም ግራ እንደገባው እንደሆነ ከላይ በገለጽኩት አባባሉ አረጋገጠልን፡፡ በጋዜጠኛው ማስታወሻ ድርሰቱ ደቡብ አፍሪካ በረከት ስምኦን ሊታከም መጥቶ ያየችውን ሀኪም ጠየቅኳትና የአዕምሮ በሽተኛ (neurosis) እደሆነ ነገረችኝ ይላል፡፡ የስምዖን ልጅ በረከት የርሱ ተመሳሳይ ስለሆነ ለአዕምሮ በሽተኛ ሳይጋለጥ እንዳልቀረ ራሱ የህመሙን መነሻ አብራርቶ ነበር፡፡ በተጨማሪም እኔ ደግሞ ተስፋዬን የማንነት ቀውስ ውስጥ ሊከተው የሚችለው እድሜ ልኩን ለጥቅም ሲል ሲያደርገው የቆዬው ሩጫ ነው እላችኋለው፡፡ 

በጋዜጠኛው ማስታዎሻ ከደርግ ወደ ወያኒ ሊቀላል ሲል በየካቲት 1982 .. ደብረ ታቦር አካባቢ የነበረውን ሁኔታ እንዲህ ይገልጽልናል፡፡ አብሮት የነበረው አንድ አምዴ የሚባል የጎጃም ልጅ ነው ብሎናል፡፡
‹‹አምዴ ለምን እጃችን ለወያኔ አንሰጥም!››

‹‹አብደሀል!!›› አለ አምዴ በመደነቅ፡፡

‹‹እውነቴን ነው በዚህ መልኩ መሞት እኮ ቂልነት ነው!!››

አምዴ ዘግየት ብሎ ‹‹ዘመዶችህ ስለሆኑ ነው የተማመንክባቸው!!››
‹‹አምዴ እመነኝ እኔ የደብረ ዘይት ልጅ ነኝ!! እኔ እንደዚያ አስቤ አላውቅም ለማንመሰገንበት ነገር መሞት አልፈልግም››

‹‹‹አንተ እጅህ ስጥ እኔ ግን አላደርገውም›› ብሎ ፍጥነቱን ሲቀጥል እኔ እርምጃዬን ቀነስኩ፡፡ብሎ ይናዘዛል፡፡

ተስፋዬ ከዚሁ መጽሀፉ ላይ እንደገለጸው ወደ ውትድርና የገባሁት የጋዜጠኛነት እድል በአቋራጭ ለማግኘት ነው ብሎናል፡፡ እናም ተስፋዬ የሚፈልገውን ለማገኘት እንደ እስስት ቀለሙን ለመቀያየር አይቸግረውም፡፡ ይኸው ችግር ይመስለኛል የማንነት ቀውስ ውስጥ የጨመረው፡፡
2. ተስፋዬ ከፍተኛ የጥላቻ አራሙቻ የበቀለበት ሰው ነው፡፡ ጥላቻ በሀሳብ ብቻ ቢያዝ ሌላ ሰው ላይጎዳ ይችል ነበር - ግን የተስፋዬ የአረም መርዝ አልተረጨም- አሊያም አልታረመም፡፡ ደህናውን ማንነቱን አበላሸበት፡፡ ጥላቻው ደግሞ ከኢትዮጵያ እና ከኢትዮጵያውያን ጋር ነው፡፡ ጥላቻው የተጠነሰሰው በአማራዎቹ ላይ እንደሆነ ራሱም ተናዟል፡፡ ለዚህም ሳይሆን አይቀርም ከሟቹ ጠቅላይ ሚኒስተር እና በነ ሌንጮ ለታ አማካኝነት በርካታ አማራዎች በየቦታው ሲሰው እንዳልሰማ ለመሆን የወሰነው፡፡ በዚሁ በጋዜጠኛው ማስታወሻ ድርሰቱ ጋዜጠኛነት ስራ አመልክቶ ስላልተፈቀደለት ‹‹ልቤ በጥላቻ አራሙቻ መሞላቱን አውቅ ነበር - በተለይ ተፈሪ አሰፋ የነገረኝ የጎጃሞች ሰንሰለት ጥላቻዬን አባባሰው›› ብሎ አስቦትም ይሁን ሳያስበው ይናገራል፡፡ ተስፋዬ ደርግ ወድቆ አርሱ ተመሳሳይ መስሪያ ቤት ለይ ሀላፊ ሆኖ ‹‹ከአራት አመት በፊት ያን ህንጻ ለቅቄ ስወጣ በልቤ ቋጥሬው የነበረው ቂምና ጥላቻ አብሮኝ ስለመኖሩ ግን እርግጠኛ አልነበርኩም -በተቀላቀለ ስሜት ተውጫለው፡፡ በሹመት ደስታና በችሎታ ማነስ ቁልቁል አዲስ አበባን አየኋት›› ይለናል፡፡ መጀመሪያ ቂሙን እሸት ለመቁረጥ በአማራና በኦሮሞ መካከል የማይበርድ ፈንጅ እንዴት ማጥመድ እንዳለበት አሰበና ‹‹የቡርቃ ዝምታን›› ጸነሰው ወለደውም፡፡ አንበሳው በልጅነቱ የቢሾፍቱ ቆሪጥ ሰይጣናት ሰፍረውበት፣ ምናልባትም ዝቋላ የሚያስጠምቀወው ዘመድም ሳያገኝ በመቅረቱ ያዴቆመ ሰይጣን ሳያቀስ አይተውም እንዲሉ ጥላቻውን ከአማራነት ወደ ኢትዮጵያነት አሳደገው፡፡ 

በኋላ ለኤርትራ መንግስት ሲሰራ ወያኔ መበለጡን ነቅቶ ካገር አባረረው፡፡ ተስፋዬ ጥቅም ካገኘ እንደማይመለስ ከላይ ያየነው ስለሆነ ይህ የሚደንቅ አይደለም፡፡ አንዳንዴ ምቀኛ የሚደሰተው እርሱ በማገኘቱ ሳይሆን ሌላው በማጣቱ ነው እና አቻው በረከት ስምዖን ሀገሪቱን እንደፈለገ ሲነዳት ደበረው፡፡ ሁለቱም ጤና ማጣት ነበረባቸው፡፡ እናም ተስፋዬ የቀድሞ አለቃውንበረከተ መርገምእያለ እርሱም በተቻለው ሁሉ ኢትዮጵያውያንን እርስ በርሳቸው እንዲተላለቁሙያዬብሎ ያዘው፡፡ ከአገር አገር እየዞረ እስከመቼ መርዙን በስኳርና በማር ለውሶ እንካችሁ እንደሚል እራሱ ተስፋዬ ነው የሚያውቀው፡፡ 
እንደ አጠቃላይ ተስፋዬ በተፈጥሮው ግራ የገባው፣ የነፋስን ሀይል ተከትሎ የሚንቀሳቀስ አዕምሮው በተንኮልና በበቀል የተበከለ እኩይ ሰው መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሊረዳው የሚገባ ነው፡፡ ተስፋዬ ጥላቻውንና ሀገር ማኮላሸቱን ከህወሓትና ሻቢያ እግር ስር ተቀምጦ የበለጠ አዳብሮታል፡፡ ለነፍሱ ያደረ ጸበል እንዳያስጠምቀው ከአገር ወጥቷል፡፡ ምናልባት ወደ ኤርትራ ሲሄድማርያም አስመራይቲአሊያም ደብረ ቢዘን ገዳም መባ የሚያስገባለት ሰው ቢኖር ለጽድቅም ምክንያት መሆን ይችል ነበር፡፡ በተረፈ ግን ተስፋዬ ካደረበት የአዕምሮ ችግር ቢገላገል የሁልጊዜ ጸሎቴ ነው፡፡ 
ሰላም ለአገራችን!! 

No comments:

Post a Comment