Friday, December 5, 2014

ለንግዱ ማህበረሰብ የቀረበ ጥሪ – ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር

የንግድ ማህበረሰብ ለአንድ አገር ምሰሶ ነው፡፡ በዴሞክራሲ በበለጸጉ አገራት የንግዱ ማህበረሰብ ለራሱ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ብቻ ሳይሆን ያለውን ፈርጣማ የኢኮኖሚያዊ አቅምና ኢኮኖሚያዊ አቅሙ የሚፈጥርለትን የተሻለ ንቃተ ህሊና በመጠቀም ለጭቁኖች መከታ ሲሆን ታይቷል፡፡ ለዚህም ነው የንግዱ ማህበረሰብ ዴሞክራሲን በመገንባት ትልቅ ሚና እንዳለው የሚነገርለት፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ እስካሁን ባለው ሁኔታ የንግዱ ማህበረሰብ በነጻነት ሰርቶ የሚበለጽግበት፣ ወገኑንና አገሩን በተለያየ መንገድ የሚያግዝበት መንገድ በመዘጋቱ የሚገባውን ያህል አስተዋጽኦ አበርክቷል ለማለት ይከብዳል፡፡
ኢህአዴግ ወደ ስልጣን በመጣበት ጊዜ ነጻ ገበያን እንደሚከተል በመግለጹ የንግዱ ማህበረሰብ በነጻ ገበያ መርህ ተወዳድሮ ራሱንም አገሩንም ይጠቅማል የሚል ተስፋ የነበረ ቢሆንም ይህ ተስፋ እውን ሳይሆን ቀርቷል፡፡ ይልቁንም ገዥው ፓርቲ የራሱን የኢኮኖሚ ኢምፓየር በመመስረት የአገሪቱን ኢኮኖሚያዊ ስርዓት አበላሽቶታል፡፡
በራሳቸው ነግደው የሚያድሩ ኢትዮጵያውያን መካከል ግልጽነት በጎደለው መንገድ የአገሪቱን አንጡራ ሀብት እየተጠቀሙ ከሚገኙት የገዥው ፓርቲ ግዙፍ ኩባንያዎች ጋር መወዳደር አቅቷቸው የከሰሩት በርካቶች ናቸው፡፡ በተለያየ መንገድ አሁንም ድረስ የቀጠሉትም ቢሆን ከገዥው ፓርቲ ተቋማት ጋር መወዳደር ተስኗቸው ለራሳቸውም ሆነ ለአገራቸው ማበርከት የነበረባቸውን አስተዋጽኦ እንዳያበረክቱ ተደርገዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለገዥው ፓርቲ ባለማደራቸው ምክንያት አግባብ ያልሆነ ቀረጥና ሌሎች ጫናዎች እየተጣሉባቸው አንድም ከገበያ ወጥተዋል፡፡ አሊያም የሚገባቸውን ጥቅም ማግኘትና አገራቸውን መጥቀስ ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ለገዥው ፓርቲ መዋጮ እንዲከፍሉ ከመጠየቃቸውም በላይ ስርዓቱ ባነገሰው ሙስና ምክንያት እጅ ተወርች ተይዘው ራሳቸውን፣ ህዝባቸውንና ለአገራችን ዴሞክራሲ ግንባታ ያበረክቱትን የነበረው አስተዋጽኦም ተገድቧል፡፡
በሌላ በኩል በገበያው ላይ የሚቆየው ለስርዓቱ ያደረ ብቻ በመሆኑ በርካቶች ለአገር ከመስራት ይልቅ ለገዥው ፓርቲ ማደር መርጠዋል፡፡ በዚህም አንድ የንግድ ማህበረሰብ ለአገሩ ያበረክት የነበረውን አስተዋጽኦ ረስተው የተሳሳተ መንገድ ይዘዋል ብለን እናምናለን፡፡ ራሳቸውን ለገዥው ፓርቲ አሳልፈው በመስጠታቸውም ታሪካዊ ግዴታቸውን ሳይወጡ ቀርተዋል፡፡ ይህን ስንል ግን ከገዥው ፓርቲ ተጠግተው ከሚያገኙት ጥቅም ይልቅ ከህዝብ ጋር ቆመውና ግዴታቸውን እየተወጡ መስዋዕትነት የሚከፍሉ የሉም ማለት አይደለም፡፡ ሆኖም በአሁኑ ወቅት የንግዱ ማህበረሰብ የሚጠበቅበትን ያህል እየሰራ እንዳልሆነ ለመጠቆም እንወዳለን፡፡

የንግዱ ማህበረሰብ ስርዓቱ በራሱም ሆነ በአገሩ ላይ የሚፈጽመውን ህገወጥነት በየግሉ ከመቃወምም ባሻገር ትግሉን በማገዙ ወደፊት ለራሱም ሆነ ለአገሩ የሚያሰራ ስርዓት መፍጠር ይችላል ብለን እናምናለን፡፡ በመሆኑም ስርዓቱ በራሱና በአገራችን ላይ የሚፈጽመውን በደል በመቃወም ላይ የሚገኙትን ተቃዋሚዎች ትግል በሞራል፣ በገንዘብና በሌሎችም ድጋፎች በማገዝና ትግሉን በመቀላቀል ለንግዱ ማህበረሰብና ለኢትዮጵያ የሚያዋጣትን ስርዓት እንድንመሰርት ጥሪ እናደርጋለን፡፡
የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ለንግዱ ማህበረሰብና በአጠቃላይም ለኢትዮጵያ የሚመች ስርዓት ለመፍጠር በጋራ እየሰራ ይገኛል፡፡ ከዚህም መካከል ‹‹ነጻነት ለፍትሓዊ ምርጫ›› በሚል መርሃ ግብር ቀርጾ በመንቀሳቀስ ላይ ሲሆን ህዳር 27/28 2007 ዓ.ም የአዳር ሰላማዊ ሰልፍ ያደርጋል፡፡ ይህ ሰላማዊ ሰልፍ ኢትዮጵያውያን መብታቸው ተከብሮ የሚኖሩባት ዴሞክራሲያዊ ኢትዮጵያን ለመፍጠር ጮራ የሚፈነጥቅ ነው ብለን እናምናለን፡፡ በመሆኑም የራሱንም መብት በማስከበርና የአገሩን ዴሞክራሲ በመገንባት ታሪካዊ ሚና ያለው የንግዱ ማህበረሰብ ትግላችን በመቀላቀል፣ በገንዘብና በሞራል በመደገፍ የዚህ ታሪካዊ ትግል አካል እንዲሆን ጥሪ እናቀርባለን፡፡
ያለ መስዋዕትነት ድል የለም!
ታሪካዊ ግዴታችን በመወጣት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንገንባ!

No comments:

Post a Comment