Tuesday, December 16, 2014

ቴዲ አፍሮ በድጋሚ ለማክሰኞ ጠዋት ተቀጠረ (ተጨማሪ አዳዲስ መረጃዎች ከዘ-ሐበሻ ምንጮች ይዘናል)

ዘ-ሐበሻ ታዋቂው ድምፃዊ ቴዲ አፍሮ ከሃገር እንዳይወጣ ከኤርፖርት ከተከለከለበት ጊዜ አንስቶ የተለያዩ መረጃዎችን እያቀረበችላችሁ ትገኛለች:: በየዕለቱ ከአንባቢዎቻችን የሚደርሱን “የቴዲ ጉዳይ ምን ላይ ደረሰ?” “ምን አዲስ ነገር አለ?” ጥያቄዎችም በርካታ ናቸው:: በዚህም መሠረት ለውድ አንባቢዎቻችን ለጉዳዩ ቅርበት እንዲኖራችሁ አዳዲስ ነገሮችን ከምንጮቻችን አሰባስበናል::
Teddy afro
የዘ-ሐበሻ የደህነንት ምንጮች እንደሚሉት ቴዲ አፍሮ ከሃገር እንዳይወጣ ፓስፖርቱን ያስቀማው ጉዳይ ከ11 ዓመት በፊት በአምስተርዳም ስለባንዲራ የዘፈነው ዘፈን ሰሞኑን ቴዲን ለመጉዳት ያሰቡ ሰዎች ከተቀመጠበት አውጥተው ዘፈኑን በሶሻል ሚዲያዎች ከለቀቁት በኋላ የስርዓቱን ሰዎች ስላናደዳቸው ነው:: ይህን ዘፈን ከ11 ዓመት በኋላ ማን ለቀቀው? የሚለው ጉዳይ እጅግ አነጋጋሪ ሲሆን ዘፈኑ ይበልጥ የነበረው በቴዲ ቅርብ ሰው እጅ ሰው ብቻ ስለነበር ሰውዪው ይህን ማድረግ የፈለገው ለበቀል እንደሆነ ብዙዎች ይጠረጥራሉ:: ይህ የቴዲ የቅርብ ሰው የነበረው ከድምፃዊው ጋር በአሁኑ ወቅት የማይሰራና የተለያየ በመሆኑ በንዴት ቴዲን እጎዳለሁ በሚል ከ11 ዓመት በፊት የተሠራን ሙዚቃ አዲስ በማስመሰል ለቆታል:: ይህ ሙዚቃም የሕወሓት/ኢሕ አዴግን አመራሮች በጣም አናዷቸዋል – እንደ ዘ-ሐበሻ የደህንነት ምንጮች::

ምንጮች እንደሚሉትና ዘ-ሐበሻ ባለፈው አርብ እንደዘገበችው ቴዲ ከፍርድ ቤት ከሃገር ቤት እንዳይወጣ የተሰጠ እግድ እንደሌለ የሚገልጽ ደብዳቤ ያወጣ ሲሆን ፓስፖርቱን የያዙበት ደህንነቶች ለዛሬ ሰኞ እንደሚሰጡት ቀጥረውት የነበረ ቢሆንም ዛሬም እንደተለመደው ሳይሰጠው ቀርቷል:: እንደለመዱትም ደህንነቶቹ ለነገ ማክሰኞ ቀጥረውታል:: ደህነንቶቹ ቴዲን በየጊዜው በማመላለስ ለማስቃየትና ለማማረር ቆርጠው እንደተነሱ የሚናገሩት የዘ-ሐበሻ ምንጮች በማን እንደታዘዙ የታወቀ ነገር አለመኖሩ ሃገሪቷን ከቤተመንግስት ሳይሆን ከቤቱ ቁጭ ብሎ የሚመራት ማን እንደሆነ ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆኗል::
በተለይ ሰሞኑን በቴዲ ይህ ጉዳይ ከደረሰ በኋላ በኢትዮጵያ መንግስት አለ ብለው በትንሹም ቢሆን እምነት የነበራቸው ሰዎች በህግ የሚመራ መንግስት አለ የሚል እምነታቸው ተሟጦ እንዳለቀ በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ሲገልጹ ሰንብተዋል::
ወደ ተጨማሪ መረጃዎች ስንመጣ ቴዲ ከዛሬ ነገ አውሮፓ ይመጣል ብለው የሚጠባበቁት የባንዱ አባላት በሆላንድ አምስተርዳም የሚገኙ ሲሆን ድምጻዊው የፊታችን ቅዳሜ በኖርዌይ ኮንሰርት እንደሚኖረው ፕሮግራም የተዘርጋ ቢሆንም የቴዲ ፓስፖርት ከአዲስ አበባ ካልተመለሰለት ወደ ኖርዌይ እንደማይንቀሳቀሱ ታውቋል:: ከባንዱ አካባቢ እንዳገኘነው መረጃም ቴዲ በትክክል ነገ ማክሰኞ ፓስፖርቱ የማይሰጠው ከሆነ በአውሮፓ ሊደረጉ ቀጠሮ የተያዘባቸው ሁሉም ኮንሰርቶች ይሰረዛሉ; የባንዱ አባላትም ወደአሜሪካ ይመለሳሉ ተብሏል::
ዘ-ሐበሻ ከዚህ ቀደም ብላ እንደዘገበችው ቴዲ በፊላንድ እና በሆላንድ ሊያደርጋቸው የነበሩት ኮንሰርቶች በፓስፖርቱ መቀማት የተነሳ ተሰርዘዋል::
ተጨማሪ መረጃዎች እንደተገኙ ዘ-ሐበሻ ለአንባቢዎቿ ለማካፈል ዝግጁ ነች::

No comments:

Post a Comment