Wednesday, December 17, 2014

‹‹የኢትዮጵያና የጂቡቲ ሕዝቦች ፍላጎት ከሆነ ውህደትን ተግባራዊ ማድረግ አለብን›› የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ዑመር ጌሌ

የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ዑመር ጌሌ
የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ዑመር ጌሌ

ረፖርተር

የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ዑመር ጌሌ፣ ጥንታዊና ታሪካዊ የሆነው የኢትዮጵያና የጂቡቲ ግንኙነት በአሁኑ ጊዜ ጥልቅ እየሆነ መምጣቱንና አንዱ አገር ለአንዱ አስፈላጊ የሆነበት ደረጃ ላይ መድረሱን ገለጹ፡፡
የሁለቱ አገሮች ሕዝቦች የውህደት ፍላጎት ካላቸውም ይህንኑ ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ከኢትዮጵያ የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን የተወጣጡ ባለሙያዎች ባለፈው ሳምንት  ጂቡቲን በጎበኙበት ወቅት፣ ፕሬዚዳንቱ ከጋዜጠኞቹ ጋር አጭር ቆይታ አድርገው ነበር፡፡
በጂቡቲ መንግሥት ግብዣ ወደ አገሪቱ የተጓዙት ጋዜጠኞች ለአምስት ቀናት በነበራቸው ቆይታ ከተለያዩ የመንግሥት ኃላፊዎች የተገነዘቡትን የጂቡቲና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቁርኝት ፕሬዚዳንቱ በድጋሚ አረጋግጠዋል፡፡

‹‹የባቡር መስመር ሳይዘረጋ በፊት የኢትዮጵያና የጂቡቲ ሕዝቦች የተቆራኙ ናቸው፤›› ያሉት ፕሬዚዳንት ጌሌ፣ ከኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ጂቡቲን ለመጎብኘት የመጣ ሰው ይህንን ቁርኝት ማንም ሳይነግረው መረዳት እንደሚችል አስገንዝበዋል፡፡
‹‹ሁለቱ አገሮች ሽርክ ናቸው፡፡ ያልተባበሩበት ዘርፍ የለም፤›› የሚሉት ፕሬዚዳንቱ፣ ‹‹በኢትዮጵያና በጂቡቲ መካከል ልዩነት አይሰማንም፤›› ብለዋል፡፡
አሁን በየደረጃው የሚታየው ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር መጨረሻው ምን ይሆናል? ሁለቱ አገሮች ተዋህደው አንድ አገር የመሆን ዕድል አላቸው ወይ? ይኼንንስ እርስዎ እውን ሆኖ ማየት ይፈልጋሉ ወይ? በሚል ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹የኢትዮጵያና የጂቡቲ ሕዝቦች ፍላጎት ከሆነ ውህደትን ተግባራዊ ማድረግ አለብን፤›› ብለዋል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዚህ ዓመት ባፀቀደው አዋጅ የጂቡቲ መንግሥት 103,000 ሜትር ኪዮብ ውኃ ከኢትዮጵያ በየቀኑ በነፃ እንዲያገኝ መፍቀዱ ይታወሳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የኤሌክትሪክ ኃይል በዝቅተኛ ታሪፍ ለጂቡቲ መንግሥት መቅረቡና አሁን እየተሸጠ ካለው የኤሌክትሪክ አቅርቦት በተጨማሪ፣ በአፋር በኩል ተጨማሪ ማስተላለፊያ መስመር ለመዘርጋት የመጨረሻው ዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሁለቱን አገሮች በባቡር ለማገናኘት በጂቡቲ በኩል 98 ኪሎ ሜትር የባቡር ሐዲዱ የመዘርጋቱ ሥራ 60 በመቶ መድረሱን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡
በጂቡቲ በኩል ደግሞ ለአፋር ክልል ቅርብ በሆነ ታጁራ በሚባል አካባቢ ለኢትዮጵያ የፖታሽ ማዕድን ኤክስፖርት ማድረጊያ ወደብ በ160 ሚሊዮን ዶላር እየተገነባ ነው፡፡ ይኼንን ወደብ ምክንያት በማድረግም ከመቐለ ታጁራ የሚደርስ የባቡር መስመር ለመዘርጋት በኢትዮጵያ በኩል እየተሠራ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ጂቡቲ በወደብ ግንባታ ረገድ ለኢትዮጵያ የኤክስፖርት ዓይነቶች ልዩ ወደቦችን በመገንባት ቅድሚያ ሰጥታ እየሠራች እንደሆነ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ ከላይ እንደተገለጸው ለፖታሽ ኤክስፖርት ግንባታው ከተጀመረው የታጁራ ወደብ በተጨማሪ የኢትዮጵያ የቁም እንስሳት ኤክስፖርት ማድረጊያ ወደብ በዕቅድ ተይዟል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በረዥም ጊዜ ዕቅድ ግሬት ሆርንስ የተባለ የመርከብ ድርጅትና ወደብ ለማቋቋምና ለደቡብ ሱዳን፣ ለኢትዮጵያና አካባቢው አማራጭ ወደብ የመፍጠር ዕቅድ ተይዟል፡፡
‹‹ለመድረስ ከምንፈልግበት በጣም ብዙ ሩቅ ነን፤›› የሚሉት ደግሞ የአገሪቱ የገንዘብና ኢኮኖሚ ሚኒስትር ኤልያስ ሞሳ ዳዋሌ ናቸው፡፡ ሚኒስትሩ አክለውም፣ ‹‹ያለ ኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት የጂቡቲ እንቅስቃሴ ጣዕም የለውም፤›› ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ለጂቡቲ የኃይል አቅርቦት በርካሽ ዋጋ በማቅረቡም 30 በመቶ የኃይል ግዥ ዋጋ መቀነሱን ተናግረዋል፡፡
የመንግሥት ለመንግሥት ግንኙነት ከሞላ ጎደል በየቀኑ መሆኑን የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ በሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ግን ክፍተት መኖሩን ተናግረዋል፡፡ በጂቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሱሌይማን ደደፎ በበኩላቸው፣ ‹‹የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ከዲፕሎማሲያዊ ቋንቋ ባለፈ የሚገለጽ ነው፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ሁለቱ አገሮች እየፈጠሩ ያሉት የኢኮኖሚ ውህደት ነው፤›› ያሉት አምባሳደሩ፣ የኢኮኖሚ ውህደት ካለ ደግሞ የፖለቲካ ውህደት እንደሚመጣ ዕምነታቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment