Tuesday, December 9, 2014

ብሔራዊ ደዌአችን በፈውስ ዋዜማ ላይ ይሆን?

ከሚካኤል ዲኖ
ይህ ፅሁፍ በጥልቅ ጨለማ ውስጥ ከወደቀ መንፈስ የፈለቀ ነው፡፡ በዓለሙ ሁሉ የሚከናወነው ግፍና በደል እንዲሁም የሰብዓዊነት መጣጣል እለት በእለት ወደ ጥልቁ ከሚደቀፅቃት መድረሻ ቢስ ስንኩል ነፍስ በጣር ወደህዋው የተወነጨ በህቅታ የታጀበ እውነት ነው፡፡
hana and sayat
ምስኪኗ ሀና
አንቺ የዓፉዐን ናሙና
ወግቶኛል ህመምሽ
ቆጥቀቁጦኛል እንባሽ
አምናለሁ
ፍርድ ከላይ ነው
ግምድል ነው ከታች ያለው
አምናለሁ
አካልሽ ቢዝልም በርኩሳን ሥራ
ነፍስሽ ግን ታርፋለች በቅዱሳን ስፍራ›

በርትራንድ ረስል «ማኅበረሰብ ያለሴተኛ አዳሪ መኖር አይችልም» ይላል አስቀያሚ እውነት ነው፤ በሌላ መልኩ ሰው ሀጥያት ሳይሰራ ሊኖር አይችልም ማለትም ነው፡፡ የኛ ማህበራዊ ተራክቦም ከዚህ እውነታ አያፈነግጥም፡፡ በአስፈሪ ሁኔታ እየተንኮታኮተ ለሚገኘው የስነ- ምግባር ምሰሷችን አይነተኛ ማሳያ ለመሆኑ ምስክር የሚያሻው አይመስለኝም፡፡
‹‹ሀይማኖተኛ ነኝ›› እያለ በሚመፃደቀው ሕዝባችን መሃል በስውር ህልውና ይንሳፈፍ የነበረው የዝሙት ተግባር ጨለማን ተተግኖ መሬት ከመርገጥ አልፎ በቀን ብርሃን በተለያየ ሽፋን ቢሮዎችን ከፍቶ፣ ከግዜ ወደግዜ ቁጥራቸው እየናረ የሚሄደውን ደንበኞቹን በትጋት እያገለገለ ይገኛል፡፡ ባሳለፍነው እሁድ ረፋድ በሸገር ካፌ በርቀት ታድሜ በዚህች ታዳጊ ቅጭት ዙሪያ የሬዲዮ ጣቢያው ጭንቅላት የሆነችው መዐዛ ብሩና ዶ/ር ምህረት ደበበ ያደረጉትን ውይይት አዳምጫለሁ፡፡
በውይይት ጠረጴዛው ከውጤቱ ይልቅ ወደፍንጩ ለማተኮር መሞከሩ ተገቢ ነው፡፡ከጭካኔና ከኋላቀርነት ጋር የተላቆጠውን ባህላችንን በርህራሄና በዕውቀት እያነጠሩ መልካሙን አጥልሎ ዝቃጩን በማስወገድ ፈንታ ሌላ ወገን ላይ ለመደፍደፍ ሲሞከር ይታያል፡፡ ከነጮቹ አለም በርካታ በካይ ነገሮች ወደ ውስጣችን መዝለቃቸው አያጠያይቅም፡፡ ይህም ሆኖ በገዛ ድንቁርናችን ያዛነፍነውንና በስንፍና ያስቀጠልነውን ባዕድ ላይ መላከክ አይጠቅምም፡፡ በዚህ መሠሉ የእሮሮ አውድ ከሚቀርቡ ልጠፋዎች አንዱ ሴተኛ አዳሪነትን ያመጣብን ጣልያን ነው የሚለው አንደኛው ነው፡፡ እንደ እውነቱ ግን ከጣልያን ወረራ በፊትም በንፅህና የኖርን ሕዝቦች አይደለንም፤ ከወረራው በፊት በነበረው ባህላችን የሰው ሚስት መወሸም፣ ባለትዳር ቢኮንም ተጨማሪ ሴትን በተጠባባቂነት ማስቀመጥ፣ የጭን ገረድ፣ በተገኘው አጋጣሚ መወስለት እንደነበር አያጠያይቅም፡፡ጣልያን በአምስት አመቱ ያልተረጋጋች ህልውናው ያደረገው ነገር ቢኖር እንዲህ ተበጣጥሶና መልክ አልባ ሆኖ የከረመውን ሀጢያት ተቋማዊነት ማላበስ ብቻ ነው፡፡
አምላኩን ከሰርክ ተግባሩ አባሮ በሃይማኖት ለበስ ድግሱ እንዲሁም በምላሱ ብቻ ቦታ የሰጠ ማህበረሰብ ሀጥያተኛ እንጂ ወንጀለኛ መሆን አልነበረበትም፤ ነገር ግን በሚያሳዝን ሁኔታ ድርብ ውድቀትን ተላብሷል፡፡ አሳዛኙ እውነታም ይኼው ነው፡፡ ከእምነትም፣ ከህሊናም በመለስ ስናስብ ሴተኛ አዳሪዎች ለማህበረሰቡ ደህንነት እጅግ አስፈላጊ ናቸው፡፡ ነውሩ የወጠረውን ክልፍልፍ በተረገመው መንገድ ተደራድረው ሃጥያቱን በማስፈሰስ፤ ይሄ አማራጭ ባይኖርለት ኖሮ በማህበረሰቡ ውስጥ ይፈጥር ከነበረው ትርምስ ራሱንም መንጋውንም ይታደጉታል፡፡ ይሄ ያልተጠና ድንበር፣ በሚያስደነግጥ መልኩ የሌለ ያህል እየተጣሰ ቀሪውም ማህበረሰብ ከማንና መቼ እንደሚከፈትበት የማያውቀውን ጥቃት እያሰበ በፍርሃት ይማቅቃል፡፡ አምላኩን ቸል ያለ ሃጥያተኛ፣ ህሊናውን ያዳፈነ ነውረኛ፣ ሕግን ያልፈራ ወንጀለኛ ….. የዛሬው ማንነታችን እውነተኛ መልክ ነው፡፡ ዛሬ በየትኛው ዝምድና
መተማመን ይቻላል? አባት ልጁን ይተኛል… ወንድም እህቱን ይጎዳኛል…. አያት የልጅ ልጁን ያስረግዛል … ልጅ እናቱን ይቃብዛል… በሰቀቀን እየኖርን ነው፡፡ ሁላችንም ለሰለባነት ታጭተናል፡፡ ወንድ መሆን ከጥቃት እንደማያድን አይተናል፡፡ ዳዴ ማለት በሰይጣን ክንፎች ከሚበረው ንስር እይታ
ውጪ እንዳልሆነ ሰምተናል፡፡ በእርጅና ዝሎ በዱላ ለመራድ መንገታገትም መስፈርት ሆኖ ከመቅሰፍቱ አላዳነም፡፡ በአንድ ማንነት ውስጥ ካለው ሁለትነት ጋር ተስማምቶ ለመተግበር የሚከብደውን ነውር፣ ሁለት ሶስት ሆነን በመመካከር ሰውን በቁሙ ወደ መብላት ተሸጋግረናል፡፡
በዚች ምስኪን ላይ የደረሰው ግፍ ይፋ ከሆነ በኋላ በወንጀለኞቹ ላይ ከማህበረሰቡ ከፍተኛ ውግዘት የፍርድ ሀሳብ ጭምር እየተሰነዘረ ይገኛል፡፡ የአስተያየቶቹ መግፍኤ የድርጊቱ ዘግናኝነት እና የልጅቷ ፍፃሜ አሳዛኝነት እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ መረሳት የሌለበት ነገር ግን ሕግ አለ፡፡ የትኛውም ወንጀል፣ ምንም አስከፊ ቢሆን ሕጉ ካስቀመጠው የቅጣት ጣራ በላይ ሊያስቀጣ አይገባም፡፡ በስሜት ለተፈፀመ ጭካኔ የስሜት ቅጣት ለመስጠት መሞከር ለነገ አንዳች ትርፍ አይኖረውም፡፡ ለዚህም በምሳሌነት በቅርቡ ኖርዌይ ውስጥ አንድ አውቶማቲክ መሣሪያ የያዘ ወፈፌ ወደ አውራ መንገድ ብቅ ብሎ ወደሰባ አካባቢ ሰዎች የጨፈጨፈበትን ታሪክ ማንሳት ይቻላል፡፡ የሀገሪቱ ህግ ከፍተኛ የቅጣት ዘመን ሀያ ሁለት አመት በመሆኑ የተፈረደበት ይኸው ነው፡፡ ይህን ተከትሎ ግን ህጉን በመከለስ ቅጣቱን ከፍ አድርገውታል፡፡ በሌላ መልኩ በዚህ የወል ኩነኔ ውስጥ ራስን የማፅደቅ፣ እጅን በ “ከደሙ
ንጹህ ነኝ” ዘይቤ የመታጠብ ውስጣዊ አላማም ይታየኛል፡፡ “ከናንተ መሀል ንፁህ ነኝ ብሎ . . .” የሚል ተጋፋጭ እንደሌለ ተገንዝቦ ለወገራ ማሰፍሰፍም ይስተዋላል፡፡
እኛስ ግን ማን ነን? ወንድን በንጉስነት ሴትን በባርነት የበየነ ባህል ባለቤቶች አይደለንም እንዴ? ሴት ልጅን አናንቀን ወንድን ልጅ አተልቀን የምናሣድግ ቤተሰቦች አይደለንምን? ንቀት እና ጭካኔ መግበን እንዲህ ያሉ አረመኔዎችን አብቅለን ስናበቃ፣ መሠቀያቸውን ለማዋቀር ደፋ ቀና ማለት እኛን ያነፃናልን? ደፍረን መድፈር ባንችል በትዳራችን ላይ አንወሰልትም? በስሜት ተነድተን በጓደኛችን ላይ አንሄድም? ዝምድናን አንሰብርም? “በጨለማ ያደረከውን በብርሃን አወጣዋለሁ” መባሉን ዘንግተን በምሽት ሴተኛ አዳሪ አልጎበኘንም? ሌላው ቢቀር በመንገድ በምኞት ተሞልተን የቆንጆ ሴት ቀሚስን በምናብ ገልጠን አልቃዥንም? ታዲያ እኛ . . . ? ? ? ደፍሮ ከደፈረው፣ ያኮበኮበው እጅግ ይበልጣል፡፡ ዛሬም ሀናዎች እልፍ ናቸው፡፡ በእርግብ ንፅህና ገላጣ ሜዳ ላይ ይርመሰመሣሉ . . . ቁራዎችም አመቺ ወቅት ፍለጋ በላያቸው ያንዣብባሉ፡፡ በብዙ መልኩ እየዘቀጥን ነው፡፡ ይሄ
አንደኛው መልክ ብቻ ነው፡፡ ምናልባትም ለራሱ ክብር የማይሰማው፣ አምላኩ መኖሩንም ከጭርታው ይሻላል በማለት የተቀበለ ሰዋዊነቱንም ከእንስሳዊ እውነታው አሻግሮ መመልከት የማይሻ መንጋን አኗኗር በማሳያ ለማስደገፍ ሲባል ብቻ የሚጠቀስ አይነት ብቻ ነው፡፡
በሚደንቅ ሁኔታ በመገናኛ ብዙሃን ስለዚህ ጉዳይ በተነገረ መጠን ውግዘቱና እርግማኑ ተገልብጦ አንደማስታወቂያ እያገለገለ ይገኛል፡፡ መሻቱ ተዳፍኖ ለሚግለፈለፍበት ያገነፍልለታል፡፡ ጭራሽ ውጥኑ የሌለው ላይ ደግሞ ሃሳብ ያጭርበታል፡፡ በየመስኩ ያለውን የኢትዮጵያውያን ሁኔታ ጠቅለል አድርጌ ስመለከተው እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ነው፡፡ በተስፋ ለማፍጠጥ የምሞክረው ድቅድቅ ያለ ጨለማማ ዋሻ ውስጥ ሆኜ ነው፡፡ በጨለማው ከማልቀስ ብዬ የምለኩሳት ሻማም ዙሪዬን በሚርመሰመሱት ዞምቢዎች ትንፋሽ ትጠፋለች፡፡ አንዳንዴ አንደውም በማይገፉት የተንሰራፋ ጨለማ ምስኪን ብርሃን መለኮስ ራስን ኢላማ ውስጥ መክተት ይመስለኛል፡፡ ሰው በመሆን መሰልቸት፣ በኢትዮጵያዊነት ችግር ሃዲድ ላይ ለዘመናት መንኳተት ሳቢያ ሙትትት እያለ ካለው መንፈሴ ውስጥ በልብ ትርታ ምት የምትመሰል ስልምልም ተስፋ ግን አንዲህ ትለኛለች . . . “ግን ምልባት ድቅድቅ ያለው ጨለማ
በንጋት ድንበር ላይ እንደሆነስ? ምናልባት ድንዛዜው ከንቃት ጥቂት ርቀት ላይ እንደሆነስ? ብሔራዊው ደዌ በፈውስ ዋዜማ እንደሆነስ….? ምናልባት …..” ትርታው ወደ ድለቃ ሲያድግ ይሰማኛል፡፡ ማን ያውቃል ለመኖር ያለኝን የፍላጎት እስትንፋስ አፍኖ ሊገድላት የደረሰው ተስፋ መቁረጥ እየተምዘገዘገ ከነበረበት የገደል መሬት ሳይላተም ነጥሮ ዳርቻው ላይ በማረፍ የህይወትን ዙሪያ ገባ በተስፋ አይን ይማትር ይሆናል፡፡ ማን ያውቃል???

No comments:

Post a Comment