Thursday, December 11, 2014

የአህመዲን ጀበል የማዕከላዊ ሰቆቃ (የምስክር ቃል)

ኡስታዝ ሃሰን ዓሊ የአህመዲን ጀበልን የማዕከላዊ ሰቆቃ ያስረዳ ሲሆን አ/ቶ አህመድ ሰዒድ ለኡስታዝ አቡበክር አህመድና ለኡስታዝ ካሚል ሸምሱ የመከላከያ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።
★የቂሊንጦ ልሳን
ክርስትያን እህቶቻችን በችሎት ታድመው ኮሚቴዎቻን ላይ የደረሰውን በደል ሰምተው አዝነዋል!!!
ታህሳስ 1/2007
በነኡስታዝ አቡበክር አህመድ የክስ መ,ዝገብ በሀሰት ተወንጅለው ጉዳያቸውን CMC በሚገኝው በቦሌ ምድብ ችሎት እየተከታተሉ የሚገኙት የህዝብ ወኪሎቹ ኮሚቴዎቻችንና ወንድሞቻችን ቀጣይ የመከላከያ ምስክራቸውን እንዳስደመጡ ምንጮቻችን ዘገቡ።

ትላንት በተሰየመው ችሎት የመጀመሪያ ምስክር የነበሩት በነኡስታዝ አቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ የተካተቱት ኡንጂነር በድሩ ሁሴን ሲሆን ከኡስታዝ አቡበክር አህመድ ጋር አንደሚተዋወቁ በመግለፅ ያስረዱ ሲሆን በተለይም በጭብጡ ላይ ኡስታዝ አቡበክር ማዕከላዊ እስር ቤት በተለምዶ ሳይቤሪያ ተብሎ በሚጠራው ክፍል ውስጥ በነበሩ ጊዜ ድብደባ፣ እንግልት፣ ከፍተኛ ኢ-ሰብዓዊ ሰቆቃ ለተከታታይ ጊዜያት ይፈፀምበት እንደነበርና በተያያዥ ጉዳዮች ምስክርነቱን ሰጥቷል። በቀጣይም የዕለቱ ሁለተኛ ምስክር የነበረችውም የአሚራችን የኡስታዝ አቡበክር አህመድ ባለቤት የሆነችው ወ/ሮ ሮማና ሱልጣን ከቤት ፍተሻ ጀምሮ እስከ ማዕከላዊ እስር ቤት ድረስ በእርሷ እና በባለቤቷ ላይ የደረሰባትን ጥሰቶች ለፍርድ ቤት ያስረዳች ሲሆን ታዳሚያንን በእንባ ያራጨ እንደነበር ዘግበናል።
ዛሬ ታህሳስ 1/2007 ቀጥሎ በዋለው ችሎትም የህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎቻችንና ወንድሞቻችን ሁለት የመከላከያ ምስክሮችን አስደምጠው ውለዋል።
አ/ቶ አህመድ ሰዒድ ሙሃመድ የመጀመሪያ የዕለቱ ምስክር ሲሆኑ ሃምሌ 11/2004 የምስክር ባለቤት መውለዷን ገልፀው ሃምሌ 13/2004 ላይ ኡስተዝ አቡበክር አህመድንና ፐህግ አዋቂውን ኡስታዝ ካሚል ሸምሱን ዱዓ እንዲያደርጉ በመኪና እቤቱ ይዟቸው የሄደ ሲሆን በዚያው ቀን ከለሊቱ 9:00 አካባቢ የፌደራል እና የደህንነት አካላት ቤቱን በመደብደብ ካስከፈቱ ቡሁዋለ ከፊት ለፊት ያገኙት እንርሱን በመሆኑ እንደደበደቡትና ከ3-4 ደቂቃ ራሱን ስቶ እንደነበር፣ አቡበክር አህመድና ካሚል ሸምሱም ከመጀመሪያው አንስቶ ራሱን ስቶ እስከሚነሳ ድረስ ድብደባ ይፈፀምባቸው እንደነበር፣ ሁለቱም በድብደባው የተነሳ አይናቸው አካባቢ ምልክት እንደነበረው፣ ኡስታዝ አቡበክር ከንፈሩ መሰንጠቁን፣ከቤት እስከ ደጃፍ ድረስ እየደበደቡ በደረታቸው መሬት ላይ እየጎተቱ እንደወሰዷቸው፣ ምስክርን ጨምሮ ተከሳሾችን ማዕከላዊ በተለምዶ ሳይቤሪያ ተብሌ የሚጠራው ክፍል ካስገቧቸው ቡሃላ በንጋታው” መታሰርህን ለማንም እንዳትናገር!” ተብሎ መለቀቁን አስረድቷል።
ሁለተኛ ምስክር የነበሩት በብዙ ኢስላማዊ በተለይም ዶክተር ዛልኪ የሚያቀርባቸውን ፕሮግራሞች ወደ አማርኛ ተርጎሞ ለህዝበ ሙስሊሙ ቀላል የማይባል አስተዋፅዖ ያበረከተውና በማበርከት ላይ የሚገኝው ኡስታዝ ሃሰን ዓሊ ለታሪክ ሙሁሩ ለኡስታዝ አህመዲን ጀበል የመከላከያ ምስክርነቱን የሰጠ ሲሆን በተለይም በማዕከላዊ እስር ቤት የተፈፀመበትን የህግ ጥሰትና ኢ-ሰብዓዊ ድብደባ አስረድቷል።
በጭብጡም ላይ ምስክሩ ማዕከላዊ… በተለምዶ ሳይቤሪያ ተብሎ በሚጠራው ክፍል ውስጥ አብረው እንደነበሩ በመግለፅ በዕለቱ ኡስታዝ አህመዲን ጀበልን ያለፉትን ሁለት ቀናት ምን እንደተፈጠረ ሲጠይቁት ከደረሠበት እንግልትና ድብደባ አንፃር በአንደበቱ መግለፅ እንዳቃተውና በክፍሉ ውስጥ የነበሩ ሌሎች ታሳሪዎችን ሲጠይቅም ከፍተኛ ድብደባ እንዳደረሱበት እንደነገሩት፤ ለረጅም ሰዓት እንደሚያቆሙት፣ ውስጥ እግሩን እንደደበደቡት፣ ለምርመራ ተብሎ ማታ 1:30 ይወሰድና ከለሊቱ 9:00 እንደሚያመጡትና ሲመጣም ሰውነቱ ዝሎ አካላቶቹ ደክሞ እንዳየው በመግለፅ ቃሉንም የሰጠው ቤተሰብና ጠበቃ ሳየገኝ እንደሆነና በግዳጅም እንደሰጠ አስረድቷል።
የዕለቱ የመከላከያ ምስክር የነበሩት አ/ቶ አህመድ ሰዒድ ሙሃመድ እና ኡስታዝ ሃሰን ዓሊ በአቃቤ ህግ የቀረበላቸውን መስቀለኛ ጥያቄዎችም በአስደናቂ መልኩ መልስ ሰጥተዋል።
በዛሬው ችሎት ላይም ከወትሮው በተለየ ሁኔት ክርስቲያን እህቶቻችን ታድመው የነበሩ ሲሆን የቂሊንጦ ልሳን ምንጮቻችንም ከፍርድ ሂደቱ በሁዋላ አግኝተው አናግረዋቸዋል።
በዛሬው ችሎት የታደሙ ክርስትያን እህቶቻችንም “ከዚህ በፊት እየመጡ ችሎት እንደተከታተሉ አስረድተው- በፊት የነበራቸው አመለካከት መንግስት እንደሚለው አይነት እንደመበርና አሁን ግን አመለካከታቸው ሙሉ ለሙሉ እንደተቀየረ ገልፀዋል። አያይዘውም የህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎችና ወንድሞች ቃላቸውን የሰጡት ሰብዓዊ መብታቸው ተገፎና ቶርቸር ተፈፅሞባቸው እንደሆነ እንደተረዱ፣ በየሚዲያው የሚለፈፈው ውሸት መሆኑንም አክለው ለምንጮቻችን አስረድተዋል።
የፍርድ ሂደቱም ነገ ታህሳስ 2/2007 ዕለተ ሃሙስ ቀሪ የመከላከያ ምስክሮችን በማስደመጥ ይቀጥላል።

No comments:

Post a Comment