Friday, March 29, 2013

ጉረኛው ጓደኛችን

ጓደኛችን
ልጆች በነበርንበት
ወቅት (12-17 ዓመት ዕድሜ)
ክልል ውስጥ የቀበና ልጆች
እንደመሆናችን የተለያዩ የስፖርት
አይነቶችን ለመጫወት አራት
ኪሎ በሚገኘው ወወክማ (ወጣቶች
ወንዶች ክርስቲያናዊ ማህበር) ዛሬ
መጠሪያው ተለውጦ የህፃናትና
ወጣቶች ማዕከል ሆኗል፡፡ በድሮ
ስሙ ልቀጥል ቢል ሙስሊሞችንና
ሌሎችንም የሃይማኖት ተከታዮችን
ቅር ማሰኘቱ አይቀርምና
መጠሪያውን መቀየሩ በበጎ ጎን
ማየት ይቻላል፡፡

እና የሚገርማችሁ
ከወወክማ ስንወጣ ከውጭ በሩ
ላይ ተደርድረን ወጪ ወራጁን
እያየን እርስ በርስ እንበሻሸቅ
ነበር፡፡ ከመካከላችን በጉረኝነቱና
በውሸታምነቱ የምናውቀው ጓደኛችን
መኪና እያሽከረከሩ የሚያልፉ ሰዎች
አንገታቸውን ጎንበስ ባደረጉ ቁጥር
ሁለት እጆቹን ወደ ላይ እያወናጨፈ
ሰላምታ ይሰጣቸዋል፡፡
እኛ፡- እኒህ ደግሞ ምንህ
ናቸው?
እሱ፡- አክስቴ ናት
እኛ፡- እኒህ አዛውንትስ?
እሱ፡- አጎቴ ናቸው
እኛ፡- እኒህ ማርሴዲስ
የያዙት ሰውዬስ?
እሱ፡- የእህቴ ባል
እኛ፡- ይህቺ ቢኤምደብልዩ
(BMW) እያሽከረከረች ያለፈችው
ቆንጆ ወጣትስ?
እሱ፡- የአክስቴ ልጅ ናት
እኛ፡- እነዚህ ሁሉ ዘመዶች
እያሉህ ለምን ወደ አሜሪካ ልከውህ
አትማርም?
እሱ፡- እኔ መሄድ
አልፈልግማ!
ይህን አይነቱን ጥያቄና
መልስ ወወክማ በሄድን ቁጥር
ለጓደኛችን ማንሳታችን አይቀርም፡፡
ምክንያቱም ልዩልዩ ተሽከርካሪዎችን
እየነዱ የሚያልፉ ሰዎች
(ከአዛውንት፣ ከሴት ወይዘሮ፣
ከጎልማሳና ከወጣቶች ጭምር)
ወደ እኛ ዞረው እጅ እየነሱ
ማለፋቸው አይቀርም፡፡ እናም እኛ
ደግሞ የጓደኛችን የቅርብ ቤተሰቦች
እንደሆኑ ነበር የምንረዳው፡፡ እሱም
ሁለት እጆቹን ወደ ላይ እያወናጨፈ
ሰላምታ ይሰጣቸዋል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን
እንደተለመደው ወወክማ በራፍ ላይ
ቆመን ሳለን፤ አንድ ብዙ ጊዜ ከእኛ
ጋር የማይውል ንቁ የሰፈራችን ልጅ
መካከላችን ነበር፡፡ እንደተለመደው
እጅ እየነሱ ለሚያልፉ አሽከርካሪዎች
ያኛው ጓደኛችን ሁለቱ እጆቹን አየር
ላይ እየቀዘፈ ሰላምታ እየሰጣቸው፣
‹‹እኒህ ደግሞ የአባቴ የቅርብ ጓደኛ
ናቸው›› ሲል የሰማው ንቁ ጓደኛችን፣
‹‹አንተ ጉረኛ ዝም አትልም! የአንተ
አባት ጓደኞች እኮ የቀን ሰራተኛ
አይደሉም እንዴ? ከመቼ ወዲህ ነው
ባለመኪና የሆኑት?›› በማለት ኩም
አደረገው፡፡
ይኸው ንቁ ጓደኛችን
ምን አለን መሰላችሁ? እነዚህ
ባለመኪኖች እጅ የሚነሱት ይህን
ጉረኛ ጓደኛችንን ሳይሆን የቅድስት
ሥላሴ ቤተ ክርስቲያንን እኮ ነው
ብሎ አሳቀን፡፡ የጉረኛው ጓደኛችን
ዘዴም ሳያስገርመን አልቀረም፡
፡ እኛም ወደ ኋላችን ዞር ብለን
የስላሴን ቤተክርስቲያን እጅ ነሳን፡፡
ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ጉረኛው ጓደኛችን
‹‹የውሸት ጎሬ›› እያልን እናበሽቀው
ጀመርን፡፡

No comments:

Post a Comment