Friday, March 29, 2013

ለሥራ ታላቅ አክብሮት የነበራቸው ንጉሥ !!


ለሥራ ታላቅ አክብሮት የነበራቸው ንጉሥ
ነበራቸው፡፡ ንጉሳዊ ዘውድ ከማንም በላይ ነው የሚለውን አባባል አይቀበሉም፡፡ እንዲያውም ከማንኛውም ዘውድ በላይ የሆነው ገበሬ ነው የሚል ፅኑ ዕምነት እንደነበራቸው ታሪክ ይመሰክራል፡፡ አልፎ ተርፎም ሰውን በሚሠራው ሥራ የሚሳደብ ሰው እኔን እንደሰደበ ይቆጠራል ብለው አስጠንቅቀው ነበር፡፡ የሚሠራ ሰው የሚወዱና የሚያከብሩ ብቻ ሳይሆኑ ራሳቸውም ሥራ ወዳድ ነበሩ፡፡
ከዛሬ 104 ዓመታት በፊት የሚከተለው ማሳሰቢያ በጽሐፍ አስተላልፈው ነበር፡፡
‹‹... ከዚህ ቀደም ብረት ቢሠራ ጠይብ፣ ሸማ ቢሠራ ሸማኔ፣ ቢጽፍ ጠንቋይ፣ ቤተክርስቲያን ቢያገለግል ደብተራ እያላችሁ፤ አርሶ ነጩን ከጥቁር አምርቶ የሚያገባውን አራሽ ከዘውድ ይበልጣል የሚባለውን ገበሬ እያላችሁ፣ ነጋዴን ነግዶ ወርቁን ግምጃውን ይዞ ቢገባ አንተ ነጋዴ ገጣባ አጣቢ እያላችሁ በየሥራው ሁሉ ትሰድባላችሁ... ከእንግዲህ ግን እንዲህ ብሎ የተሳደበ እኔን የሰደበ ነው እንጂ ሌላውን መስደብ አይደለም፡፡ ዳግመኛ ግን ሲሳደብ የተገኘ ሰው መቀጫውን አንዳንድ ዓመት ይታሠራል፡፡ ሹማምንትም አስረህ ዓመት ለማስቀመጥ የሚቸግርህ የሆነ እንደሆነ አስረህ ወዲህ ስደድልኝ››

ጥር 17 ቀን 1900 ዓ.ም የዳግማዊ አጤ ምኒልክ ማስጠንቀቂያ አዘል ደብዳቤ
(አጤ ምኒልክ ከጳውሎስ ኞኞ)
‹‹መሃላ ተጣሰ በመላው አበሻ፣
ማን ይወልዳት ይሆን? ያችን ጥቁር ውሻ ››
ይህን ስንኝ የቋጠሩት አፈሩን ገለባ ያድርግላቸውና የማደንቃቸውና የማከብራቸው ዕውቁ ባላቅኔ ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ ነበሩ፡፡ ይህንን ስንኝ የቋጠሩበት ምክንያትም ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ የጤንነታቸው ሁኔታ አስጊ እየሆነ በመጣበት ወቅት የአልጋቸው (የመንበረ ሥልጣናቸው) ወራሽ ማን እንደሚሆን በአሳወቁበት (በተናዘዙበት) ወቅት ነው፡፡
ወቅቱም ግንቦት 10 ቀን 1901 ዓ.ም ነበር፡፡ ከኑዛዜያቸው ውስጥ፣ ‹‹...የእግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን የአልጋየ ወራሽ ከልጄ ከወ/ሮ ሸዋረጋና ከወሎው ገዥ ከራስ ሚካኤል የተወለደው ልጅ ኢያሱ እንዲሆን ሰጥቻለሁ፡፡ ይህንን የእኔን ቃል ያፈረሰ መሬት ይክዳው ጥቁር ውሻ ይውለድ፡፡ (ሠረዝ የተጨመረ)....›› የሚል ይገኝበታል፡፡
በኑዛዜው መሠረት ልጅ ኢያሱ ሥልጣን ላይ ቢወጡም በሸዌ ጥበብ ከመንበራቸው እንዲነሱ ተደርጐ የኋላ የኋላ ተፈሪ መኰንን (ስመ ምንግሥታቸው ዓፄ ኃይለሥላሴ ሆኖ) እንዲነግሱ ተደረገ፡፡ ይህን ጊዜ ነው ዕውቁ ባለቅኔ ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ ከላይ የተጠቀሰችውን ስንኝ ለመቋጠር የተነሳሱት፡፡
መቼም የሰው ልጅ ጥቁር ቀርቶ ነጭ ውሻም አይወልድም፡፡ ከሰው የተፈጠረ ሰው የሚወልደው ያው ሰውን ነው፡፡ የዓፄ ምኒልክ እርግማን ቃሌን ካላከበራችሁ ከጨካኝና ግፈኛ መንግስት ይጣላችሁ ማለታቸው ይመስለኛል፡፡

No comments:

Post a Comment