Friday, March 27, 2015

ምርጫ በኢትዮጵያ – ሰማያዊ ፓርቲ ከምርጫ ክርክር ታገደ

ሰማያዊ ፓርቲ በኢብኮ ከሚደረገው የምርጫ ክርክር ታገደ

• ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በኢብኮ ስቲዲዮ ከሚደረግው ቀረጻ ተባረዋል
(ነገረ-ኢትዮጵያ) ሰማያዊ ፓርቲ ዛሬ መጋቢት 18/2007 ዓ.ም ምሽት ኢብኮ (EBC) ላይ ከሚቀርበው የ‹‹ግብርና እና ገጠር ልማት›› ላይ ሊያደርገው የነበረው የምርጫ ክርክር ላይ እንዳይቀርብ መታገዱን የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ለቀረጻ ወደ ኢብኮ ስቲድዮ ባቀኑበት ወቅት የድርጅቱ ምክትል ስራ አስካሄጅ አቶ ተሻለ ‹‹ባለፈው ያላሰባችሁትን የምርጫ ክርክር እድል ሰጥተናችኋል፡፡ በመሆኑም ዛሬ መከራከር አትችሉም›› ተብለው መባረራቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

በሰአብአዊ መብት ዙሪያ ኢብኮ ላይ በቀረው የምርጫ ክርክር ላይ አንድ ፓርቲ ለመቅረብ ፈቃደኛ አለመሆኑን በመገልጹ በክርክር 5 ፓርቲዎች እንዲቀርቡ የሚደረግ በመሆኑ ሰማያዊ ፓርቲ እንዲቀርብ የተደረገ ሲሆን ዛሬ ምሽት በግብርና እና ገጠር ልማት ላይ የሚደረገው ክርክር ላይ ሰማያዊ ፓርቲ ዕጣ የደረሰውና የፀደቀ ፕሮግራም ነው፡፡
በህገ ወጥ መንገድ ከቀረጻ ተባርሬያለሁ ያሉት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ‹‹ኢብኮ በፕሮግራም የተያዘ የምርጫ ክርክር ላይ እንዳንቀርብ ያደረገው እሁድ በ15 ከተሞች ሰልፎች እንዳለን ስለለሚያውቅና የዛሬው ክርክር በየአካባቢው ያለውን ህዝብ እንዳያነቃቃ ተፈልጎ ነው›› ብለዋል፡፡ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት አክለውም ‹‹እስካሁን እየተደረጉት ባሉት ክርክሮች ሰማያዊ የኢህአዴግን ተግባራት እያጋለጠና ጠንካራ አማራጮችን እያቀረበ በመሆኑ ነው፡፡ ስለሆነም ኢብኮ ኢህአዴግን አግዞ ሰማያዊ ወደ ህዝብ እንዳይደርስ እያደረገ ነው›› ሲሉ ወቅሰዋል፡፡

No comments:

Post a Comment