Saturday, March 14, 2015

የአዲስ አበባ ነዋሪ ዜግነቱን እንዲያገኝ መፍትሄው “የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል” ብሎ 10ኛ ክልል መጨመር – ያሬድ ጥበቡ (ጌታቸው ጀቤሳ) f

What is Ato Yared Tibebu belching about?
ምን ይሻላል?
የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶች በብዙ ጉዳዮች የሚለያዩ ቢሆንም፣ ፊንፊኔ መናገሻችን ናት በሚለው ጉዳይ ግን ይስማማሉ ። ለዚህም ይመስ ላል በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጉዳይ፣ ኦሮሞ ፈርስትና ኦፒዲኦ እጅና ጓንት ሆነው ሃገሩን ያተራመሱት ። ለመሆኑ ፊንፊኔ የኦሮሞ መናገሻ ነበረች? ኦሮሞዎች ከየት መጡ? የኦሮሞን አፈታሪክና መዝሙሮች ፣ የታሪክ ተመራማሪዎችም ከፃፉዋቸው፣ ከሱማሌና ሐረሪ ህዝቦች አፈታሪክ በማጥናት፣ ታላቁ ኢትዮጵያዊ ይልማ ዴሬሳ “የኢትዮጵያ ታሪክ በአስራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን” የሚል መፅሀፍ በ1959 አም ፅፈዋል ። የታላቁ የኦሮሞ አፈታሪክ ቁንጮ፣ የብላታ ዴሬሳ ልጅ በመሆናቸው ልናዳምጣቸው የግድ ነው ። የመጨረሻው የሌቃ ነቀምቴ ንጉስ የሞቲ ሞረዳ በከሬ የቅርብ ዘመድም ስለሆኑ ( cousin) ታሪካቸውን ልቅም አድርገው ያውቃሉ ። እንዲህ ይሉናል ።

” ይህ ምዕራፍ የተፃፈው፣ የኦሮሞን ወይም አማሮች ጋላ የሚሉትን ነገድ ታሪክ በዝርዝር ለማስረዳት አይደለም ። ስለሆነ በ16ኛው መቶ ዘመን መጀመሪያ ይህ ነገድ ከደቡብ ኢትዮጵያ ወደ ሰሜንና ወደ ምስራቅ ጎርፎ የሚበዛውን ደጋ አገር ይዞ ስለሰፈረበት በዘመኑ ታሪክ ውስጥ የኦሮሞን ነገድ ፈንታ ሳናነሳው ያለፍን እንደሆነ የ16ኛው መቶ የኢትዮጵያ ታሪክ ሙሉ ሆኖ አይገኝም ።…
… ታሪክ ሲነጋጋ የኦሮሞ ህዝብ ከአደን ሰላጤና እስከ ቅርብ የእንግሊዝ ሱማሌ በሚባለው የሱማሌ ሪፐብሊክ አውራጃ መካከል ከሚገኘው የአፍሪካ ቀንድ በተባለው አገር ሲኖሩ ታዩ ። ኦሮሞዎች በየትኛው የታሪክ ዘመን በዚህ ምድር እንደሰፈሩ ግልፅ አይደለም ። … ይሁንና ከ10ኛው መቶ ዘመን በፊት ሱማሌ የተባለው ነገድ ከታጁራ ቤይ አቅጣጫ ተንቀሳቅሶ በኦሮሞዎች ላይ ጦርነት ባደረገ ጊዜ፣ መጀመሪያ የእንግሊዝ ሱማሌ የነበረውን አገር ለቀው ወደ ምስራቅ ደቡብ መጓዝ እንደጀመሩ ታውቋል ። ኋላም የአፍሪካ ቀንድ ከምትባለው ሶስት ማእዘን ወረዳ ተነስተው በዋቢ ሸበሌና በጁባ ወንዞች መካከል ቤናዲር በተባለው አውራጃ ሰፍረው በዚያ ብዙ ዘመን እንደኖሩ በጋሎች አፈታሪክ ሲነገር የኖረ ነው ። …
… ከሰሜን የሱማሌዎች ከደቡብ ባንቱዎች የሚያደርጉባቸው ጦርነት ምንም ጊዜም ሰላም የሰጣቸው አይመስልም ። ስለዚህ ከዚህም ከአዲሱ አገራቸው እንደገና መሰደድ ግዴታ ሆነባቸው ።
…ጋሎች ወላቡ፣ አበያ፣ ባሕርና ሕዲ ዳዲ ከሚባሉት አቅጣጫ የሰፈሩት በአስረኛው መቶ በዛጕዌዎች ዘመነ መንግስት መጀመሪያ ላይ ይመስላል ። … የኦሮሞ ህዝብ በሥጋና በወተት የሚመገብ ዘላን ስለነበር ድርቅ ከሆነው ከቤናዲር አውራጃ ተጉዞ ወላቡ ወይናደጋ በገባ ጊዜ ይህች ምድር ማርና ወተት ታፈሳለች እንደተባለችው እንደ ምድረ ከነአን የምትቆጠር ሁና አገኙዋት ። … በወላቡ ተራራና በአበያ ባህር አጥቢያ በኖሩበት ጊዜያት የሰላምና የጥጋብ የዕድገት ዘመን መሆኑን ሲወርድ ስዋረድ የመጣው የጋሎች አፈታሪክ አጋኖ ይገልፅልናል ። …
ኦሮሞዎች እላይ በተመለከተው አኳኋን በወላቡ ዙሪያ ብዙ ትውልድ ካሳለፉ በኋላ ከልክ ያለፈ ተራብተው ምድር ጠበባቸው ። … ከዚህም ሌላ በጥንት ዘመን ከቀድሞው መኖሪያቸው ከአፍሪካ ቀንድ ወግቶ ያስወጣቸው የሱማሌ ህዝብ፣ አስራ አምስተኛው መቶ ሲጋመስ ወይናደጋው ድረስ እየመጣ አዲሱን አገራቸውን መውረር ጀመረ ። በዚህ አኳኋን የኦሮሞ ህዝብ ለመከላከልና ለግጦሽ የሚፈልገውን መሬት አስፍቶ ለመያዝ ከሰላማዊ አኗኗር ወደ አርበኝነት ሃሳቡን መለሰ ። …ከወላቡ ሳይነሱ በገዳ ድርጅት ውስጥ የጦር ሠራዊትን ማከናወን ዋና ጉዳይ አድርገው ያዙት ። …በዚህ ዘመን ኦሮሞዎች ከረዩ፣ ቱለማ፣ ሜጫና፣ ወሎ በሚባል ባራት ትልልቅ ነገድ ተከፍለው ይገኙ ነበረ ። ስለዚህ ከረዩ የተባለው ነገድ፣ ባሌን ፈጠጋርንና ደዋሮን እንዲወር፣ ቱለማ ወደ ሰሜን ተጉዞ ዛሬ የሸዋ ጋላ ምድር የተባለውን እንዲይዝ፣ ሜጫ በስተ ምእራብና በስተደቡብ የሚገኘውን የእናሪያዎችን አገር እንዲወስድና፣ ወሎ የተባለው ነገድ በሸዋ በስተምስራቅ ተጉዞ ከወሎ አውራጃ እስከ ትግሬ የተዘረጋውን አንጎት የተባለውን አውራጃ እንዲይዝ የተቀየሰው ኦዳ ነቤ በነበሩ ጊዜ ነው ። …
ለጦርነት የተደረገው ድርጅት ከአለቀ በኋላ ኦሮሞዎች ዘመቻውን ፈጥነው አልጀመሩትም ። [ ዛሬ ኢሳያስ ወያኔን ለመበቀል የሚያሳየውን አይነት ትእግስት ይመስላል * የኔ] ይልቁንም በነዚህ ዘመናት ውስጥ ሱማሌዎች ክርስቲያናዊውን ኢትዮጵያ ለመውረር በትልቁ በመዘጋጀት ላይ ስለነበሩ፣ ምቹ ጊዜ ለማግኘት ኦሮሞዎች በትእግስት ጠበቁ ። በ1506 አም አነስተኛ ወረራ ወደሰሜን በሚገኘው ወረዳ ላይ ከአደረጉ በኋላ ጥቂት ገፍተው ቆሙ እንጂ ውጊያውን አልቀጠሉም ። … ስለዚህ በ1520ና በ1532 አም መካከል ግራኝ የኢትዮጵያን ደጋ ወሮ በአማራና በሱማሌዎች መካከል ሃይለኛ የሆነ ትግል ሲደረግ ጋሎች ያሰቡትን ለመፈፀም በፀጥታ ሲጠባበቁ ቆዩ ። …
እስከ 16ኛው መቶ ዘመን በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ድምፁን ሳያሰማ የቆየው የጋላ ነገድ በ1524 አም ከደቡባዊ መኖሪያው መንቀሳቀስ ጀመረ ። የዚህም እንቅስቃሴ አላማ ከዚህ በላይ እንደተመለከተው ሁሉ በደጋው የኢትዮጵያ አወራጃዎች ላይ ለመስፈር ነበር ። ”
እንግዲህ ከላይ በታላቁ ሰው ብእር ያነበብነው፣ ኦሮሞዎች ከየት ተነስተው ዛሬ የሚኖሩባቸውን ግዛቶች እንደያዙ ነው ። ገና 500 አመታት እንኳ ያላደረገ ታሪካዊ ክንዋኔ ነው ። ታዲያ የሶስት ሺህ አመት መንግስታዊ ታሪክ ባላት ሃገር ላይ፣ ታሪክ የሚጀምረው ከምንሊክ መስፋፋት ወዲህ ያለው ብቻ ነው የሚል ክርክር የት ያደርሳል? ፊንፊኔስ ብትሆን ከከብት አርቢዎች ሆራነት ወጥታ የአፍሪካ ዲፕሎማሲያዊ መናገሻ የሆነችው በመላ ኢትዮጵያውያን ትጋትና ድካም መሆኑ እየታወቀ፣ አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል ውስጥ ናት የሚል ወያኔአዊ ደባ ምን ይጠቅማል? የአምስት ሚሊዮን ነዋሪዎቿስ መብት ለምን ታገደ? ብዙ ጥያቄዎች አሉ ። መፍትሄዎችም እንዲሁ ።
አንዱ የሚታየኝ መፍትሄ ፣ አሁን ባለው ፌዴራላዊ አወቃቀር ውስጥ የአዲስ አበባ ነዋሪ ዜግነቱን የሚያገኝበት መንገድ ማፈላለግ ነው ። ለዚህም፣ ማዘጋጃ ቤቱን እንደ ማእከል ወይም መነሻ በመውሰድ፣ 150 ኪሎ ሜትር ሬዲየስ ያለውን ግዛት “የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል” ብሎ 10ኛ ክልል መጨመርና፣ ይህም ክልል በፌዴራል ምክርቤት ድምፅ እንዲኖረው ማድረግ ። ይህ ክልል የሁሉም ብሄረሰቦች የጋራ ክልል በመሆኑ፣ በምክርቤቱ ውስጥ ያለው ድምፅም ቢያንስ አንድ ሶስተኛውን የያዘ ቢሆን፣ ሃገሪቱን ማረጋገት ላይ ትልቅ አስተዋፅኦ ይኖረው ይመስለኛል ።
ይህ እቅድ ሶስት ችግሮች ይገጥሙታል ። አንዱ የሸዋን አማራ ከአማራ ክልል ያወጣዋል ። ሁለተኛው ችግር የኦሮሞን ክልል በምእራብና ምስራቅ ሁለት ቦታ ይከፍለዋል ። ሦስተኛው ችግር ደግሞ ጉራጌው የሚኖርበትን ከደቡብ ክልል ያስወጣዋል ። የአማራና ኦሮሞ ክልሎች ግን በወያኔ የፖለቲካ ፕሮዤ የተወጠኑ እንጂ፣ በታሪካዊ ወይም ውስጣዊ ፍላጎታቸው የተከለሉ አይደሉም ። ኦነግ ውስጥ የፖለቲካ ችግር በተነሳ ቁጥር፣ እስላምና ክርስቲያን፣ አርሲና ወለጋ እየተባባለ እንደሚቧደን ሁሌም የምንታዘበው ነው ። የአማራ ክልል ውስጥ የተካተቱም ህዝቦች፣ ከአማራነት ይልቅ ወሎዬነታቸው፣ ጎጃሜነታቸው፣ ጎንደሬነታቸውን ይበልጥ ያፈቅሩታል፣ ይወዱታልም። የወያኔ የዘር መድልኦ መባባስ ገና ወደፊት ይመስለኛል አማራ የሚባለውን ብሄር ቀጥቅጦ የሚፈጥረው ። ጉራጌው አዲስ አበባን ደክመው ከሰሯት ቀዳሚ በመሆኑ፣ ማእከላዊ ኢትዮጵያ ከልል ውስጥ ግባ ቢባል፣ ያን ቆንጆ ጭፈራውን ሲያቀልጠው በአይነ ህሊና ይታየኛል ። ሸዌው የኢትዮጵያ ማንነቱን አስቀዳሚ ሰለሆነ፣ ከኦሮሞና አማርነቱ በላይ ኢትዮጵያዊነቱን ያስቀድማል ብዬ መከራከር እወዳለሁ ። ስለሆነም ዜግነቱን የሚያሰከብርለት የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቢያገኝ የሚያሰማው እልልታና ሆታ፣ የፈረሱ ኮቴ በእዝነ ህሊናዬ እያደመጥኩት ነው ።
ስለሆነም የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መፈጠር፣ ኦሮሞውን ቢያንስ ወደ ሁለት ክልል፣ አማራውን ደግሞ ወደ ሶስት ሊከፍለው ይችላል ። ይህ ግን ለተሻለ አስተዳደርና ልማት ጥርጊያውን ሰለሚከፍት ጥሩ ሃሳብ መስሎ ይሰማኛል ። አሁን ያለውንም የአዲስ አበባ ማሰተር ፕላን ችግር ከስር መሰረቱ ይፈታዋል ብዬ አስባለሁ ። አዲስ አበባንም ለፖለቲካ ተንኮል ተብሎ ከተጣለባት የአንድ ብሄር ክልል ውስጥ የመወርወር አደጋ ይታደጋታል ። የኢትዮጵያ ብሄርተኝነትም ዙሪያውን በከበቡት የኦሮም፣ የጉራጌ፣ የአማራ ገበሬዎች እየታገዘ፣ ከሸገር በሚፈልቀው የመላ ኢትዮጵያውያን ባህላዊ መስተጋብርና ፍቅር እየተመራ፣ የኢትዮጵያን ቀጣይነት ያረጋግጣል ብዬ አስባለሁ ። ይህ ለብዙ ወራት ተጨንቄ ያቀረብኩት ሃሳብ በመሆኑ ለማውገዝ አትቻኮሉ ። እሰኪ እንደኔ ተጨነቁበት ።
በተለይ አዲስ በቀል የሆናችሁት የትግራይ ከበርቴዎች፣ የሃገር መረጋጋት የሚፈጥረው ጥቅም ተጠቃሚ ስለሆናችሁ ፣ ከመለስ የስልጣን ተንኮሎች ባሻገር፣ ለልጆቻችሁ የምታወርሱት ሃገርና ንብረት እንዲኖራችሁ፣ የሚቀርቧችሁን የወያኔ መሪዎች ከሃገር ማጥፋት እኩይ ተግባርና ከዘረኝነት እንዲርቁ ምከሩ ። ይህን ማድረግ አቅቷችሁ እስካሁን እንደተያዘው ተቃውሞን በጥይት ማጥፋት ይቻላል ብላችሁ ከገፋችሁበት፣ እንኳንስ ሃገር፣ መሰደጃ ስንኳ አታገኙም ። ከቀዬው የነቀላችሁት ስደተኛ “የኒዮ ሊበራሊዝም ጠበቆች” እያላችሁ በምታወግዟቸው አለምአቀፍ መያዶች እየታገዘ ያድናችኋል። ከዚህ ይሰውራችሁ ። ለሃገር የሚበጅ መላ ምቱ። ይህችን ቅድስት ድሃ ሃገር የሁላችን እናድርጋት ። ታላቁ ትግራዋይ ኢትዮጵያዊ ገብረሕይወት ባይከዳኝ ከመቶ አመታት በፊት እንደፃፈው “ጠንካራ መንግስት ከህዝብ ልብ ይቀዳል”

No comments:

Post a Comment