Sunday, March 22, 2015

የሕወሓት ሰዎች በትግራይ ክልል ለፓርላማ ከመድረክ ዕጩዎች ጋር ይፎካከራሉ

አርከበ ዕቁባይ አይወዳደሩም
299d05d703691f17d2f061a06bf1f93c_Lዘንድሮ ለአምስተኛ ጊዜ በሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ የሕወሓት/ኢሕአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ከሆኑት መካከል አቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም፣ ዶ/ር አድኃነ ኃይለ አድኃናና አቶ ጌታቸው ረዳ በትግራይ ክልል በተለያዩ ዞኖች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከመድረክ ዕጩዎች ጋር እንደሚወዳደሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከድርጅቱና ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በዘንድሮ አምስተኛ ዙር ምርጫ አቶ ዓባይ ፀሐዬ በስለኽለኻ (ምዕራብ ዞን)፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም በብዘት (ምሥራቅ ዞን)፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልዩ አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ በአላማጣ (ደቡብ ዞን) ሕወሓት/ኢሕአዴግን ወክለው ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአረና ትግራይ (መድረክ) ተወካዮች ጋር ይፎካከራሉ፡፡

በሽሬ እንዳ ሥላሴ የአረና ትግራይ ለሉዓላዊነት ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተካልኝ ታደሰ አቶ ዓባይ ፀሐዬን፣ በአዲስ አበባ የአረና ፓርቲ ተጠሪ አቶ ኪዳነ አመነ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖምን፣ እንዲሁም የአረና የደቡብ ትግራይ አካባቢ ተጠሪ አቶ ንጉሥ አብርሃ ደግሞ አቶ ጌታቸው ረዳን መድረክን ወክለው እንደሚፎካከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የቀድሞው የትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር አድኃና ኃይለ አድኃና በማይጨው ከተማ ሕወሓት/ኢሕአዴግን ወክለው እንደሚወዳደሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአረና ትግራይ (መድረክ) ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የምሥራቅ ዞን አስተባባሪ የሆኑት መምህር ፍፁም ግርሙ በአዲግራት ከተማ የኢሕአዴግ ዕጩ የሆኑትን ዶ/ር መብራህቱ መለስን ይፎካከራሉ፡፡ እንዲሁም የአረና ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አምዶም ገብረ ሥላሴ በሀገረ ሰላም (ተምቤን አበዓዲ) የምርጫ ጣቢያ የሕወሓት/ኢሕአዴግ ተወካይ የሆኑትን አቶ ብርሃኑ ገብረ ማርያምን ይፎካከራሉ፡፡
በተያያዘ ዜና ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሕልፈት በኋላ የሕወሓት ሊቀመንበር የሆኑት የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ዓባይ ወልዱ፣ ያለምንም ተቀናቃኝ በአክሱም አካባቢ ለክልል ምክር ቤት ለምርጫ ይቀርባሉ፡፡
መድረክን ወክለው ባለፈው አራተኛ ዙር ምርጫ አቶ ዓባይን የተፎካከሩት ወንድማቸው አቶ አውዓሎም ወልዱ እንደማይወዳደሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ እንዲሁም ባለፈው ምርጫ መድረክን ወክለው በአደዋ ከአቶ መለስ ጋር ተፎካክረው የነበሩት የአረና ትግራይ ፓርቲ መሥራች ወ/ት አረጋሽ አዳነ በመቐለ ከተማ ለክልል ምክር ቤት የሚወዳደሩ ሲሆን፣ በእሳቸው ቦታ አቶ ተክላይ ታደለ ከሕወሓት ምክትል ሊቀመንበር ከዶ/ር ደብረ ጽዮን ጋር እንደሚፎካከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ቀደም ሲል ከሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴና ከሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የተሰናበቱት ዶ/ር አርከበ ዕቁባይ፣ በተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጾችና በተለያዩ ሕዝባዊ ስብሰባዎች ወደ ፓርቲው ከፍተኛ አመራር እንዲመለሱ ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር ቢባልም፣ በዘንድሮ ምርጫ እንደማይወዳደሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አረና ትግራይ ለሉዓላዊነት ፓርቲ በትግራይ ክልል ከሚገኙት ሕወሓት ሙሉ ለሙሉ ከሚወዳደርባቸው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 38 ወንበሮች መካከል በሃያ ዘጠኙ ይፎካከራል፡፡ እንዲሁም ለክልል ምክር ቤት 74 ተወዳዳሪዎች ማቅረቡ ታውቋል፡፡
ፓርቲው አባል የሆነበት መድረክን በመወከልም በአዲስ አበባ ከተማ ሦስት ተፎካካሪዎችን (አቶ ጎይተኦም ፀጋይ፣ አቶ ካህሳይ ዘገየና አቶ አብረሃ ካሳን) ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዕጩነት ማቅረቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡
Source:: Ethiopian Reporter

No comments:

Post a Comment