Thursday, April 30, 2015

ብሔራዊ ባንክን በማጭበርበር 25 ዓመታት የተፈረደበት ግለሰብ ቅጣቱ ተሰርዞ ክሱ እንደገና እንዲጀመር ተወሰነ

ቁርጥራጭ ብረቶችን ወርቅ በማስመሰል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክን ከ95.5 ሚሊዮን ብር በላይ አጭበርብሮ ተሰውሯል ተብሎ በሌለበት 25 ዓመታት ጽኑ እስራትና 180 ሺሕ ብር የተፈረደበት አቶ አስማረ አያሌው፣ የቅጣት ውሳኔው ተሰርዞ ክሱ እንደ አዲስ እንዲጀምር ተወሰነ፡፡
የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 18ኛ ወንጀል ችሎት ሚያዝያ 19 ቀን 2007 ዓ.ም. ውሳኔውን ያሳለፈው፣ ግለሰቡ ‹‹በሌለሁበትና ባልተከራከርኩበት ይኼንን ያህል የእስራት ቅጣት ሊወስንብኝ አይችልም፤›› ብሎ በመከራከሩ ነው፡፡

ፍርድ ቤቱም ግለሰቡ ያቀረበው የመከራከሪያ ሐሳብ ትክክል መሆኑን በማመን፣ እንደገና በማረሚያ ቤት ሆኖ እንዲከራከር አዟል፡፡
አቶ አስማረ አያሌው ከታህሳስ 1998 ዓ.ም. እስከ መጋቢት 1999 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት ከንግድና ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሐሰተኛ የሆነ የላኪና የአስመጪ ፈቃድ በማዘጋጀት፣ ከማዕድንና ከኢነርጂ ሚኒስቴር ሐሰተኛ የሆነ የወርቅ ጥራት ማረጋገጫ በመያዝ፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በውስጣቸው ቁርጥራጭ ብረታ ብረት የያዙ 29 የታሸጉ ሳጥኖች በማቅረብ፣ ብሔራዊ ባንክን ከ95.5 ሚሊዮን ብር በላይ በማጭበርበሩ ተከሶ ነበር፡፡
አቶ አስማረ ድርጊቱን መፈጸሙ ሲታወቅባት በኬንያ በኩል ከአገር እንደወጣና ለሰባት ዓመታትም መኖሪያውን በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ አድርጎ እንደቆየ ታውቋል፡፡ አቶ አስማረ ፈጽሞታል በተባለው በማጭበርበር ድርጊት ክስ ተመሥርቶበት ባለመቅረቡ እርሱ በሌለበት ክሱ እንደተሰማና ፍርድ ቤቱም ጥፋተኛ ብሎት የ25 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ180 ሺሕ ብር ቅጣት አስተላልፎበት እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ግለሰቡ እ.ኤ.አ. መስከረም 30 ቀን 2014 በቁጥጥር ሥር ውሎ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽንና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ፖሊስ ኮሚሽን በብሔራዊ ኢንተርፖል ተቋማቶቻቸው አማካይነት በተደረገ ትብብር ተላልፎ መስጠቱን መዘገባችን አይዘነጋም፡፡
Source:: Ethiopian Reporter

No comments:

Post a Comment