Friday, April 17, 2015

በአብራሃ ጅራና ከሱዳን ጋር በሚዋሰኑ የጎንደር አካባቢዎች በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ የሱዳን ጦር ሰራዊት ተኩስ በመክፈት ጉዳት አደረሰ፡፡

ሀሙስ እለት ሚያዚያ 1 2007 ዓ.ም እስከ አፍንጫቸው የታጠቁ የሱዳን ወታደሮች ድንበር ተሻግረው ከሱዳን ጋር ወደ ሚዋሰኑ የጎንደር መሬቶች በመግባት የአካባቢውን ህብረተሰብ በጦር መሳሪያ ወግተው ከገዛ አገሩ ለማፈናቀል በወሰዱት አርምጃ ሁለት ሰዎች ቆስለዋል፡፡ ቁስለኞቹ አንደኛው የአብደራፊ 01 ቀበሌና ሁለተኛው የሆሩመር ነዋሪዎች መሆናቸው ታውቋል፡፡
በተጨማሪም የሱዳን ወታደሮች በርካታ የግል ባለሃብት ካምፖችንና የቁም እንስሳትን በእሳት አቃጥለዋል፡፡
የሱዳን ጦር ሰራዊት የኢትዮጵያን ሉኣላዊነት በመግሰስ ድንበሯን አልፎ በመግባት በዜጎቿ ላይ የተኩስ ውርጅብኝና በንብረት ላይ ጉዳት ከማድረሱ በፊት በአካባቢው ሰፍሮ ከሚገኝ የህወሓት አገዛዝ መከላከያ ሰራዊት ጋር ውይይት አድርጓል፡፡ በመሆኑም የሱዳን ጦር ድንበር ሰብሮ ወደ ኢትዮጵያ በመግባት በአካባቢው ህዝብ ላይ ያሻውን ያደርግ ዘንድ ፈቃድ አግኝቷል፡፡

የህወሓት አገዛዝ መከላከያ ሰራዊት የጦር መኮንኖች በጋራ ባደረጉት ውይይት ላይ የሱዳንን ወታደሮች ቃል በቃል “ድንበራችሁ ትግራይ ድረስ ነው ግቡና ወሰናችሁን አስከብሩ፡፡” ማለታቸውን ውስጥ አዋቂዎች ለአርበኞች ግንቦት 7 ሬድዮ ዜና ምንጮች ተናግረዋል፡፡ እንዲሁም የሱዳን ጦር በህዝቡ ላይ ለሚወስደው ማንኛውም ወታደራዊ እርምጃ ምንም አይነት ምላሽ እንዳይሰጥ ጥብቅ መመሪያ በመሪዎቹ መተላለፉን ውስጥ አዋቂዎች ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የሱዳን ወታደሮች “መሬታችንን ልናስከብር ነው የመጣን፤ እኛ ከአማራ ጋር ድንበር የለንም፤ ወሰናችን ትግራይ ነው፤ ስለዚህ የራሳችን ምድር ላይ እስካለን ድረስ ያሻንን የማድረግ መብት አለን ማንም ከልካይ የለንም፡፡” በማለት ተኩስ ለከፈቱበት ህብረተሰብ የህወሓት የጦር መኮንኖች የነገሯቸውን መድገማቸውን ህብረተሰቡ አስረድቷል፡፡
የኢትዮጵያን ለምመሩቶች እየቆረሰ በፊርማ ለሱዳን መንግስት ሲያስረክብና ሲለማመጥ የኖረው የህወሓት አገዛዝ ልክ እንደ ከዚህ ቀደሙ የሱዳን ጦር ሰራዊት በድሃው ገበሬ ላይ እያደረሰ የሚገኘውን ጭፍጨፋና ከቀየ ማፈናቀል አሁንም በዝምታ እየተመለከተ በአህያ ባልነቱ የቀጠለ መሆኑን ወደፊትም እየደረሰባቸው የሚገኘውን ግፍና በደል እንዲባባስ ከማድረግ በስተቀር ምንም አይነት ጥሩ ነገር እንደማይጠብቁ የሱዳን ጦር ሰራዊት ወታደራዊ እርምጃ ሰለባ የሆኑት ኢትዮጵያዊያን አረጋግጠዋል፡፡
የህወሃት አገዛዝ ድሃ ኢትዮጵያዊያን በተለያዩ አገር መንግስታት ግፍና በደል ሲፈፀምባቸው ዝምብሎ ከማየት ባለፈም ችግራቸውን የሚያባብስ ድርጊት እንደሚፈፅም ዓለም ሁሉ የሚያውቀው አስነዋሪ ባህሪው ነው፡፡ የመን በሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ላይ የተፈፀመውን ግድያ በይፋ ሲደግፍም ታይቷል፡፡
የህወሓት አገዛዝ “አማራ ክልል” እያለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩ ገበሬ የህብረተሰብ ክፍሎችን በላባቸው ያፈሩትንና የንብረታቸው መጠበቂያ የጦር መሳሪያ በሙሉ ለመግፈፍ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ታወቀ፡፡
የህወሓት አገዛዝ ከዚህ በፊት በዚህ “አማራ ክልል” እያለ በሚጠራው አካባቢ ላይ “አስመዝግቡና ህጋዊ ፈቃድ ይሰጣችኋል” በማለት ገበሬውን ልክ እንደ ህፃን ልጅ በመቁጠር አሽበልብሎ ለማስመዝገብ በያካባቢያቸው ወደ ሚገኝ ሚሊሻ ፅፈት ቤት የሄዱትን ትጥቃቸውን ነጥቆ ባዶ እጃቸውን እንዲመለሱ አድርጓል፡፡ እንዲሁም የታጠቀ ጦር ልኮ የገበሬውን መንደሮች በመውረር በማናለብኝነት በህገ ወጥ መንገድ እያንዳንዱን የገበሬ ጎጆ በርብሮ እጁ ውስጥ የገባውን የጦር መሳሪያ ሁሉ በገፍ ዘርፏል፡፡
አሁንም በተመሳሳይ ሁኔታ ምስኪኑ ጥሮ ግሮ አዳሪው ህዝብ ሽጦ ለውጦ በህጋዊ መንገድ በራሱ የታጠቀውን እንደጥሪት መያዣ የሚጠቀምበትንና ለደህንነቱ ዋስትና የሆነውን ጠብመንጃ በጉልበት ለመግፈፍ እየሞከረ ይገኛል፡፡
የህወሓት አገዛዝ ይህን የሚያደርገው ህዝብ አንቅሮ ስለተፋው የታጠቀው የህብረተሰብ ክፍል ሳይወዱ በግድ ብረት አንስተው ወደ በረሃ የወረዱትን የነፃነት ኃይሎች ደግፎ ይወጋኛል ከሚል ስጋት በመነጨ እንደሆነ በደሉ እየደረሰባቸው የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ይገልፃሉ፡፡
የህወሓት አገዛዝ “ትጥቃችሁን ፈታችሁ ባስቸኳይ ካላስረከባችሁኝ ማዳበሪያ አታገኙም አሊያም መሬታችሁን እነጥቃችኋለሁ፣ ካስፈለገም ወደ ወህኒ ላወርዳችሁ እቸላለሁ፡፡” በሚሉና በሌሎችም ዛቻዎችና ማስፈራሪያዎች ለማንገራገር ቢሞክርም ገበሬው ህዝብ ደግሞ በበኩሉ “የከዚህ ቀደሙ ውርደት እየፀፀተን ከእንግዲህ በኋላ ሞተን ክንዳችን ሳንንተራስ ንብረታችንን በፈቃዳችን ለማንም አሳልፈን ፈፅሞ አንሰጥም፡፡” የሚል መረር ያለ ምላሽ በመስጠት ቆራጥና የማያወላውል አቋማቸውን አሳይተውታል፡፡ የህወሓት አገዛዝም ፍርሃቱ አይሎበት የፈሪ ዱላውን አንስቷል፡፡

የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ

No comments:

Post a Comment