Thursday, April 30, 2015

የሳንቲም የመሰብሰቡ ተቃውሞ ስኬታማ በሆነ መልኩ እንደቀጠለ ነው

ረቡእ ሚያዝያ 21/2007 ህዝበ ሙስሊሙ ሀይማኖታዊና ህገ መንግስታዊ መብቶቹ እንዲከበሩለት ቢጠይቅም አሁንም ድረስ ከመንግስት ጠብ ያለ መልካም ምላሽ አላገኘም፡፡ እንዲያውም ከወትሮው በለየለት መልኩ መንግስት በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ እየፈፀመ ያለው ጭቆና ፍጥጥ ባለ ሁኔታ ተባብሶ የቀጠለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ከኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጋር የሚያገናኛቸው ሥውር መስመር እንኳ የሌላቸውን ዓለም አቅፍ ክስተቶች ሁሉ እየጎተተ ለዚሁ የጭቆናው ጉዞው ተጨማሪ መንደርደሪያ ማድረግን መርጧል፡፡ ይህም ሆነ በዚህ የበደል ደመና ባጠለለበት ድባብ ውስጥም ግን የመንግስትን መጠነ ሰፊ ጭቆና በመቋቋም ህዝባዊ ተሳትፎን በሚያረጋግጡ፣የመነቃቃትን ስሜት በሚፈጥሩ፣ ከአደጋ ነፃ በሆነ ክልል ውስጥ በተቀመሩና ለቀጣይ መጠነ ሰፊ ትግሎች መስፈንጠሪያ በሚሆኑ የትግል ስልቶች በአዲስ የትግል ምህዋር ላይ ትግላችንን አጠናክረን ቀጥለናል፤ አልሐምዱሊላህ! አሁን ላይ እየተገበርነው ያለነው የሳንቲም ማሰባሰብ መርሃ ግብርም የዚህ ተቃውሟችን አዲስ ምእራፍ አካል ነው፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲተገበር የታዘዘው የሳንቲም ማሰባሰብ መርሃ ግብር ይፋ ከሆነ ጀምሮ ህዝበ ሙስሊሙ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም የሀገራችን ከተሞች የሚገኙ ሙስሊሞች አኩሪ እና ስኬታማ በሆነ መልኩ ሳንቲሞችን በመሰብሰብ የዘመቻውን ውጤታማነት ወጋገን እያሳዩ ነው፡፡ ለአብነት ያህልም በሀገራችን የሚገኙ በርካታ የመንግስት እና የግል ተቋማት፣ እንዲሁም መሰል ድርጅቶች የሳንቲም እጥረት እየተከሰተ በመሆኑ መንግስት መፍትሄ እንዲሰጣቸው እየወተወቱ እንደሆነ ታውቋል፡፡ ሳንቲም የመሰብሰቡ መርሃ ግብር የተጀመረው ቅርብ ሊባል በሚችል ጊዜ ቢሆንም ህዝቡ መብቱን ለማስከበር ካለው ቁርጠኝነት በተወለደ ተነሳሽነት ሳንቲሞችን ከያሉበት በማደን እና በመቆጠብ ላይ ትጉህ ሆኖ በመገኘቱ ከላይ ለተገለፀው አመርቂ ውጤት መገኘት ምክንያት ሆኗል፡፡ በሳንቲም ትብብር መንፈጉ እንቅስቃሴ ከምናገኛቸው ጥቅሞች አንዱ ህዝቡ የትብብር መንፈግ ትግል ልምድ እንዲኖረው ማድረግ እንደመሆኑ መጠንም ርብርቦሹ በዚሁ ከቀጠለ ካቀድነው ጊዜ ቀድመን የዚህን ዘመቻ ውጤታማነት በማረጋገጥ ወደ ቀጣዩ የትግል ስልት እንንደረደራለን ተብሎ ይጠበቃል፡፡ አሁንም ቢሆን ግን ከከተማ እስከ ገጠር የምንገኝ ሙስሊሞች ሁሉ በእስከዛሬው ሳንቲም የመሰብሰብ ስኬታማ እንቅስቃሴያችን ሳንዘናጋ በአዲስ ወኔና ጉልበት በሳንቲም አሰባሰቡ ላይ ልንበረታ ይገባል፡፡ መቼም ቢሆን ህዝብ የተረባረበበት ስራ ከውጤታማነት የሚርቀው በጊዜ ብቻ ነውና የጀመርነውን መርሃ ግብር በአዲስ መንፈስ በማስቀጠል የድል ግስጋሴያችንን እናፍጥን፡፡ ትግሉ የሁላችንም እንደመሆኑ መጠን ቀልጣፋና የተሻለ የአሰባሰብ ጥበቦች ሲኖሩን ልምዱ ወደ ሌሎቻችንም እንዲደርስ በማድረግ ለተሻለ ውጤት እንትጋ፡፡ እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶች፣ ተማሪዎች፣ የመንግስት ሰራተኞች፣ ነጋዴዎችና ሌሎችም የሚመለከታቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ሁሉ ተሳትፏቸው ይጨምር ዘንድ በየቤታችን በመመካከርና ግንዛቤ በመስጠት ጥረታችንን እንድናጠናክር፣ እንዲሁም መርሃ ግብሩ ወሳኝ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ መንገዳችን ላይ ሊገጥሙን ከሚችሉ አዘናጊ ጉዳዮች በመጠንቀቅ ይህን የተቃውሞ መርሃ ግብር ባማረ ውጤት እንድናሳካ አደራ እንለላን! ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል! ድምጻችን ይሰማ! አላሁ አክበር! 

No comments:

Post a Comment