Wednesday, August 26, 2015

የደኢህዴን አመራር የህዝብ ቁጣ ላይ እሳት እየጨመረ እንደሚገኝ ርዕሰ መስተዳደሩ ተናገሩ

‹‹በአመራሩ መካከል ትርምስና ጥርጣሬ ተፈጥሯል››
‹‹ሰማያዊና መድረክ ማሸነፍ ይችሉ ነበር›› አቶ ደሴ ዳልኬ
በቅርቡ ታደለ ቱፋ የተባለ ግለሰብ በጋሞ ብሄር ላይ የጻፈውን መፅሃፍ አስመልክቶ በደኢህአዴን አመራሮች መካከል የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ በተደረገ ሚስጥራዊ ስብሰባ ላይ የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ደሴ ዳልኬ የደኢህዴን አመራር የህዝብ ቁጣ ላይ እሳት እየጨመረ ነው ሲሉ መግለፃቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ የደረሰው የድምፅ ማስረጃ አረጋገጠ፡፡

የጋሞ ጎፋ ዞን በተለይም የአርባ ምንጭ የደኢህዴን አመራር በፌደራል ደረጃ በጥርጣሬ እንደሚታይ የገለፁት አቶ ደሴ ዳልኬ የጋሞ ጎፋ ዞን የደኢህዴን አመራሮች ከመጽሐፉ ፀሐፊ ጀርባ አሉ በሚል አመራሩ እርስ በእርስ ጥርጣሬ ውስጥ እንደሚገኝም ነገረ ኢትዮጵያ እጅ የገባው ድምፅ አረጋግጧል፡፡ በዚህም ምክንያት በክልሉ ርዕሰ መስተዳደርና በሌሎች አመራሮች መካከል ግልፅነት እንደሌለ ገልጸው ‹‹እናንተ ለእኔ ግልፅ ሁኑ!›› ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
የደኢህዴን በተለይም የጋሞ ጎፋ ዞን አመራሮች ከክልሉና ከዞኑ ያልወረዱ አጀንዳዎችን እንደሚያስፈፅሙና በጎን አመራሩ ያልተስማማባቸውንና የማያውቃቸውን ወረቀቶችም እንደሚያሰራጩ ተገልጾአል፡፡ በተለይም የአርባ ምንጭ አመራር መርህ እየተጣሰ ዝም ብሎ እንደሚያይ የገለፁት አቶ ደሴ ዳልኬ በዚህም ምክንያት ትርምስና አደጋ መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡
በስብሰባው ላይ የተገኙት የደኢህዴን አመራር በህዝቡ መካከል አንድነት እንዳይኖር ማድረጋቸውን፣ እንዲሁም ህዝብ ከአመራሩ እንደተነጠለ በመግለፅ ለችግሮቹ ድርጅቱን ተጠያቂ ሲያደርጉ ርዕሰ መስተዳደሩ በበኩላቸው ደኢህዴን ላይ ትችት ያቀረቡትን አመራሮች ሀሳብ በማጣጣል ችግሩን በጋሞ ጎፋ ዞን የሚገኙ ጥገኛ አመራሮች ችግር መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሆኖም በክልሉና በፓርቲው ላይ አደጋና ትርምስ እንዳለ፣ እንዲሁም የደኢህዴን አመራር ችግር በህዝቡ ቁጣ ላይ እሳት እየጨመረ እንደሚገኝ አቶ ደሴ ዳልኬ ገልጸዋል፡፡
የጋሞ ጎፋ ዞን የደኢህዴን አመራሮች ችግሩን ለማርገብ ስብሰባው ላይ የተገኙትን የደኢህዴንን ከፍተኛ አመራር ‹‹የት ነበራችሁ? ለምንድን ነው ዛሬ የመጣችሁ?›› የሚል ጥያቄ ያነሱ ሲሆን አቶ ደሴ ዳልኬም ‹‹እስካሁን እናንተ አላችሁ ብለን ነው፡፡ አሁን ግን የመጣነው የዞኑ አመራር ሲተራመስ ጊዜ ነው›› ብለዋል፡፡
የደኢህዴን አመራር ‹‹አባቴ፣ አያቴ፣ ሰፈሬ የት ነኝ›› የሚል ክፍፍል መፈጠሩን በመግለፅ ወቀሳ አቅርበዋል፡፡ የደኢህዴን አመራሮች ከመፅሐፉ በስተጀርባ እንዳሉበት ጥርጣሬ መፈጠሩንና የተፈረጁ አመራሮች መኖራቸውም በስብሰባው ወቅት ተገልጾአል፡፡ ፍረጃው መቆም እንዳለበት የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳደሩ ተጣርቶ እጁ እንዳለበት የታወቀ አመራር ላይ እርምጃ ይወሰዳል ብለዋል፡፡ ከመፅሐፉ ጋር ተያይዞ ህዝብ ሰላማዊ ሰልፍ የወጣ ሲሆን የህዝብን ጥያቄ ያነሱ ምሁራን እንዲፈቱ ጥያቄ አቅርቧል፡፡ ይሁንና ከታሰሩት መካከል አንድ ግለሰብ ተፈትቶ የነበር ቢሆንም በድርጅቱ ውሳኔ እስር ቤት እንዲቆይ ተደርጓል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል የደኢህዴን አመራሮች ‹‹ጥገኛ›› በሚል ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ግንኙነት እንዳላቸውና የተቃዋሚዎችን ሀሳብ እንደሚቀበሉ የተጠቆመ ሲሆን ይህን አስተሳሰብ ባይታገሉት መድረክና ሰማያዊ በጋሞ ጎፋ ዞን በተለይም አርባ ምንጭ ማሸነፍ ይችሉ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በስብሰባው ወቅት የዞኑ አመራሮች ጥያቄ እንዳላቸው በተጠየቁበት ወቅት ቅሬታቸውን ለመግለፅ ሲሞክሩ አቶ ደሴ መድረኩን ሳይሰጧቸው ቀርተዋል፡፡ ‹‹ጥገኛ›› ካሉት አስተሳሰብ ካልተላቀቁም እርምጃ እንደሚጠብቃቸው በመግለፅ አስጠንቅቀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment