Friday, May 31, 2013

መኢአድ አንድነት ከሰማያዊ ጎን ቆሙ – ከግርማ ካሳ

Muziky68@yahoo.com
ግንቦት 22 ቀን 2005. .
ዜጎች ሃሳባቸዉን በነጻነት የመግለጽ፣ የመሰባሰብ፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ሙሉ መብት አላቸው። ይሄንን መብት በመጠቀም አገር ቤት የሚንቀሳቀሰው የሰማያዊ ፓርቲ፣ በአፍሪካ ሕብረት ፊት ለፊት ሰላማዊ ሰልፍ ይጠራል። ሕጉ በሚፈቅደው መሰረት፣ ለባለስልጣናት ሰልፍ እንደተጠራ ማሳወቅ ብቻ ስለሚያስፈልግ፣ የፓርቲዉ አመራር አባላት ማስታወቂያ ለማስገባት ወደ አዲስ አበባ አስተዳደር ይሄዳሉ። የአስተዳደሩ ሃላፊዎች ግን ሊያናግሯቸውም ሆነ ማስታወቂያዉን ሊቀበሏቸው ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀረ። ተደጋግሞ ሙከራ ቢደረግም፣ በሕጉ መሰረት የሰማያዊ ፓርቲን ማስታወቂያ ተቀብለው፣ አስፈላጊዉን ትብብር ማድረግ የነበረባቸው የኩማ ደመቅሳ ሰራተኞች ግን ዜጎችን ማንገላታት መረጡ።ዜጎች ሰልፍ በሚጠሩበት ጊዜ ለባለስልጣናት የሚያሳዉቁት፣ ፍቃድ ለመጠየቅ ሳይሆን፣ የትራፊክ መጨናነቅ፣ የኮንስትራክሽን ግንባታዎች የመሳሰሉ ችግሮች ካሉ፣ አስፈላጋዊዉን ዝግጅት ማድረግ፣ ያም ካልተቻለም ደግሞ ሰልፉ የሚደረገበትን ሌላ አማራጭ ቦታ ወይንም ጊዜ በመግለጽ፣ እንዲተላለፍ መጠይቅ ይችሉ ዘንድ ነዉ።

በአዲስ አበባ አስተዳደር እንግልት የደረሰባቸዉ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት፣ በፓስታ ቤት፣ በሬኮመንዴ ሰልፍ እንደሚያደርጉ የሚገለጸዉን ደብዳቤ ይልካሉ። ከአስተዳደሩ ግን ምንም አይነት ምላሽ አሁንም ሳይገኝ ይቀራል። የዚህን ጊዜ ሰልፍ ለማድረግ ማሳወቅ እንጂ ከማንም ፍቃድ መጠየቅ እንደሌለባቸው ጠንቅቀዉ ያወቁት ብሉዎች፣ ሰልፉ በተባለው ቀን (ግንቦት 17) እና ቦታ እንደሚደረግ ያሳውቃሉ። የዚህን ጊዜ፣ በሰማያዊ ፓርቲ ዉሳኔ ግራ የተጋቡትና የጨነቃቸው የአዲስ አበባ አስተዳደር ባለስልጣናት፣ በርካታ የዉጭ አገር መሪዎች በአዲስ አበባ በመኖራቸውና ከፍተኛ መጨናነቅ በመኖሩ፣ ሰልፉ ከአንድ ሳምንት በኋላ እንዲደረግ ይጠይቃሉ። ሕግን የሚያከብረው ሰላማዊዉ የሰማያዊ ፓርቲ፣ በቀኑ መለወጥ ተስማምቶ፣ ሰልፉ የፊታችን እሁድ ግንቦት 25 ቀን 2005 . እንደሚደረግ ይገልጻል።
እንግዲህ ይሄ ሁሉ የሚያሳየው ለመብት፣ ለእኩልነትና ለነጻነት የሚደረገዉ ትግል ስር እየሰደደ መምጣቱን ነዉ። በዚሁ በሰላማዊዉ ትግል እንቅስቃሴ ዙሪያ ከፍተኛ የሆነ የኢትዮጵያዉያን መሰባሰባና መተባበር እየታየ ነዉ። ይሄም በራሱ ትልቅ ድል ነዉ።
(የመኢአድ / ኢንጂነር ኃይሉ ሻውል)
የመኢአድ ተቀዳሚ /ሊቀመንበር የተከበሩ አቶ ወንድሙ ድርጅታቸው መኢኣድ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰልፍ ላይ አባላቱና ደጋፊዎች እንዲገኙ ጥሪ እንዳቀረበ፣ ከፍተኛ የማስተባበር ሥራ እንደሚሰራም አስረድተዋል። የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ፣ የተከበሩ አቶ ዳንኤል ተፈራ በበኩላቸው የአንድነት ፓርቲ የሰማያዊ ፓርቲን ጥሪ ከልብ እንደሚደግፍ፣ አባላቱም ከብሉ ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ጋር ሆነዉ ድምጻቸውን ለማሰማት እንደተዘጋጁ ገልጸዋል። ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር የአንድነት አመራር አባላት የቅርበት ግንኙነት እንዳላቸው የገለጹት ሌላው የአንድነት ከፍተኛ አመራር አባልና የዉጭ ጉዳይ ሃላፊ፣ የተከበሩ አቶ ተመስገን ዘዉዴ « የሰማያዊ ፓርቲ ያናሳቸው ጥያቄዎች የአንድነት ጥያቄዎቹ ናቸው። በአዲስ አበባ በሚገኙ 23 ወራዳዎች ባሉት ሴሎችና /ቤቶቹ አማክኝነት፣ የቅስቀሳ ሥራ ጀምሯል» ሲሉም የሰላማዊ እንቅስቃሴዉን ግለት ለማሳየት ሞክረዋል።
ከመኢአድና ከአንድነት ፓርቲ በተጨማሪ የባላራዩ የወጣቶች ማህበር የተስኘው የሲቪክ ማህበርም በሰልፉ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እንደሚያደርግ የገለጸ ሲሆን፣ የአመራር አባላቱ ከሰልፉ ጋር በተገናኘም ከወዲሁ ከፍተኛ እንግልት እየደረሰባቸው ነዉ። የባላራእዩ ወጣቶች ማህበር የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ፣ ወጣት ተክለ ያሬድ በአሁኑ ወቅት በአገዛዙ ፖሊሶች ተይዞ በእሥር ቤት ይገኛል። ይሄም የሚያሳየው ምን ያህል በአገር ቤት ያሉ ወገኖቻችን ከፍተኛ መስዋእትነት እየከፈሉ እንዳለ ነዉ።
ወደ ዉጭ አገር ስንመጣ ደግሞ ኢትዮጵያዉያን በሚሰባሰቡበት በርካታ የፓልቶክ ክፍሎች ከመቼዉም ጊዜ በላይ፣ ከቅንጅት ጊዜ ጀምሮ ታይቶ ያልታወቀ፣ አገር ቤት እየተደረገ ላለዉ ትግል ትልቅ ድጋፍ እየተሰጠ ነዉ። ትላንት የተለያየ መስመር ይዘው እርስ በርስ ሲላተሙ የነበሩ፣ የቃሌ ክፍል፣ ከረንት አፌር፣ ደብትራዉ፣ ሲቪሊቲ ….የመሳሰሉ ክፍሎች እየተግባቡ፣ እየተቀራረቡና ለአንድ አላማ በአንድ ላይ እየተሰባሰቡ ነዉ። ሁሉም ትኩረታቸውን አገር ቤት አድርገዉ፣ እየተደረገ ላለዉ ሰላማዊ ትግል ድጋፋቸውን እየለገሱ ነዉ። እንደ ኢሳት፣ ኢትዮጵያ ሪቪው፣ ዘሃበሻ፣ አቡጊዳ፣ ኢኤምኤፍ ያሉ ሜዲያዎችም፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፊ ዘገባ እያቀረቡበት ሲሆን፣ ተስፋ ቆርጠው በነበሩት መከፋፈሎች አዝነዉ ዝምታን መርጠው የነበሩ ሁሉ እየተነቃነቁ ነዉ።
በዉጭ አገር ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶችን ካየን ደግሞ፣ በባህር ዳር ከፍተኛ እንቅስቃሴ እንዳደረገ በኢሳት የተዘገበለት የሽግግር ምክር ቤት የተሰኘው ድርጅት፣ እንዲሁም ኢሕአፓ-ዴ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ለጠራዉ መኢአድና አንድነትን ለተቀላቀሉት የሰላማዊ ሰልፍ ያላቸዉን ድጋፍ ገልጸዋል። በስምንት የፓልቶክ ክፍሎች፣ በፌስቡክና ትዊተር በመተላለፍ ወደ 10 ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያዉያን ተከታትለውታል በተባለው፣ ግንቦት 17 እና 18 2005 . የሲቪሊቲ ክፍል ባዘጋጀው የአለም አቀፍ የኢትዮጵያዉያን ኮንፍራንስ ላይ፣ የተገኙት የሽግግር ምክት ቤቱ ዋና ጸሃፊ የተከበሩ ዶር ፍስሐ እሸቱ፣ ድርጅታቸው በአገር ቤት ለሚደረገዉ ሰላማዊ ትግል ሙሉ ድጋፍ እንዳለው አረጋግጠዋል። «ትግሉ ያለው አገር ቤት ነዉ። አገር ቤት የሚታገሉትን መርዳት አለብን» ሲሉ ነበር ዶር ፍስሐ ለአገር ቤቱ ትግል ያላቸዉን ጠንካራ ሶሊዳሪቲ የገለጹት።
ይሄ ሁሉ እንግዲህ የሚያሳያዉ ጸሎታችን እየተሰማ እንደሆነ፣ እንደ ሕዝብ ለመብታችን፣ ለአገራችን አንድነት መከበር፣ ለእኩልነት፣ ለፍትህ መስፈን ለሕግ የበላያነት ለመታገል በአንድ ላይ እየተሰባሰብን መሆኑን ነዉ።
ሁለት ነጥቦች ጣል አድርጌ ላቁም። በጣም መሰረታዊና ሊሰመርባቸው የሚገባ ነጥቦች !

አንደኛእሑድ ግንቦት 25 ቀን የሚደረገዉ ሰልፍ ጅማሬ እንጂ ፍጻሜ አይደለም። ቀጣይነት ያለው፣ የተደራጀ፣ የተጠና ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ይቀጥላሉ። በዘጠና ሰባት በግፍ የተገደሉትን እነ ሽብሬ ደሳለኝ፣ ለማስታወስ፣ የአንድነት ፓርቲ ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ለማድረግ ዝግጅት ላይ እንዳለ የፍኖት ጋዜጣ በቅርቡ መዘገቡ ይታወሳል።። ለአንድነት ቅርበት ያላቸው እንደገለጹልኝ፣ የሚደረጉትን ህዝባዊ እንቅስቃሴዎች፣ ሰላማዊ ሰልፎችን የሚያካትቱ ሲሆኑ፣ ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በማቀናጀት የሚሰራ እንደሆነም ለመረዳት ችያለሁ። መኢአድም እንደዚሁ የሚያደጋቸው ይኖራል። በአጭሩ ተከታታይ እንቅስቃሴዎች በሁሉም መስክ ይኖራሉ።
ሁለተኛ- የፊታችን ግንቦት 25 የሚደረገዉ ሰልፍ፣ ሰማያዊ ፓርቲ ቢጠራዉም፣ የመኢአድ፣ የአንድነት፣ የሽግግር ምክር ቤቱ፣ የኢሕአፓ_ዴ፣ የባላራዩ ወጣቶች ማሕበር፣ ሰልፉን የምንደግፍ ዜጎች ሁሉ ሰልፍ ነዉ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ሰልፍ ነዉ። ሰማያዊ ፓርቲ ለኮሰ። የተለኮሰውን ማቀጣጠል የእያንዳዳችን ነዉ። በድርጅቶች የሚጠሩት እንቅስቃሴዎች ዉጤት የሚያመጡት እያንዳንዳችን ስንተባበር ብቻ ነዉ። አገር ቤት ያለነዉ ወደ ሰልፉ መሄድ ይጠበቅብናል። ሰልፉ ሰላማዊና በሕግ የተፈቀደ ነዉ። «መብታችን ተረገጠ፣ ድህነት በዛ፣ ዘረኝነት በዛ፣ በአገራችን ባርያ ሆንን መኖር መረረን፣ ፍትህ ጎደለ፣ ቀንበርና ግፍ በዛ» የምንል ካለን እንግዲህ ጊዜው አሁን ነዉ። ሰላማዊ በሆነ መንገድ እንነሳ። እንጩህ። ድምጻችን እንደ ነጎድጓድ ያስተጋባ። አንፍራ።
በዉጭ አገር ያለነዉ ደግሞ፣ ስልክ እንደዉል፣ ኢሜል እንላክ። ዘመድ ወዳጆቻችንን እናበረታታ። ደብረጺዮን የስልክ መስመሩን እና ኢንተርኔቱን ሊዘጋው ይችላል። ግድ ይለም። መስመሮቹን እንዲዘጋ ማስደረጋችን በራሱ ትልቅ ድል ነዉ።
ያኔ ኢትዮጵያም በልጆቿ ትኩራለች !


No comments:

Post a Comment