Wednesday, May 22, 2013

የአዲስ አበባው ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ለበተነው የሐሰት ምስክርነት የተሰጠ መልስ (ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ)


በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራው ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ የአዲስ አበባው ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ለበተነው የሐሰት ጽሑፍ የተሰጠ መልስ

መግቢያ
ቅዱስ ዳዊት እናንተ የሰው ልጆች እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ በማለት ለንስሐ ስፍራ ሳይኖራቸው ሐሰትን ፀንሰው አመፃን የወለዱትን ሰዎች የገሠጸበትን የቅዱስ መጽሐፍን ኃይለ ቃል መነሻችን ያደረግነው አለምክንያት አይደለም ። ሐሰትን እንደ ልብስ ለብሰው በልቡናቸው ሠራዒ መጋቢ ፈታሒ አምላክ የለም እንዳሉት የማኒ ልጆችና መሰሎቻቸው ፥ ፈራሽ በስባሽ የሆነውን የሰውን (የመንግሥትን) ኃይል ተገን አድርገው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሕገ ቀኖና ያፈረሱ ፣በአዲስ አበባ ያሉ ወንድሞቻችን ፥ ታሪክንና ሕዝብን ሳያፍሩ እናምነዋለን የሚሉትን እግዚአብሔርንም ሳይፈሩ ንስሐ በመግባት ፈንታ የሐሰት መጽሔት ጽፈው አውጥተዋል ። የሚገርመው መጽሔቱ የወጣው አባ ማትያስ ወያኔ ኢሕአዴግ መንበሩን በሰጣቸው ቀን መሆኑ ነው ። ያላስተዋሉት ነገር ግን ዛሬም እግዚአብሔር እነሱ በገፉአቸው በስደተኛውና በተሐራሚው የኢ.ኦ.ተ.ቤ/ክ ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ስደትና ሐዋርያዊ ተልእኮ መክበሩን አለማወቃቸው ነው ። ያን ለማስተዋል ቢታደሉ ኖሮ የቀደመውን ስሕተት በሌላ ስሕተት ለማረም ባልተነሡ ነበር።
The Ethiopian Orthodox Tewahedo Church,  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
መጽሔቱ ቤተ ክርስቲያናችን አንድ ትሁን ። ፓትርያርካችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ናቸው እያለ ለጮኸው ሕዝበ ክርስቲያን የማጽናናት ቃልን የሚናገር አይደለም።
መጽሔቱ በገዛ ሀገሩ ላይ እንደ ሁለተኛ ዜጋ እየታየና ዘሩ እየተጠየቀ ስለሚፈናቀለው ሕዝብ የሚያወራ አይደለም። መጽሔቱ «አማራንና የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን አከርካሪ ሰብረናል» እያለ የሚደነፋውን፣ ገና ከመነሻው በበረሃ የቀመመውን መርዝ የሚያመክን አይደለም።
መጽሔቱ እየፈረሱ ስላሉት ገዳማቶቻችን ፥ በአስተማሪ እጦት እየተበተኑ ስላሉት የአብነት ትምህርት ቤቶች ፥ ቀዳሽ በማጣትና የማስቀደሻ ዕጣንና ዘቢብ በማጣት ስለሚዘጉ አብያተ ክርስቲያናት የሚናገር አይደለም።
እነዚህ ልባቸውን እንደ ፈርዖን ያደነደኑ ወንድሞቻችን ያወጡት ሐሰተኛ መጽሔት በረኃብ ጽናት በየትምህርት ቤቱ ስለሚወድቁት ሕጻናት የሚናገር አይደለም ። ወይም ጊዜ አንሥቷቸው ዛሬ ከባዶ ባለሚሊዮን የሆኑት የገዢው ወርቅ ልጆች እንዴት ለደሃው ማሰብ እንዳቃታቸው የሚጠይቅ አይደለም። ይህ ሁሉ አይደለም።
ይልቁንም መጽሔቱ ላለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ካድሬዎች ሲደሰኩሩት የነበረውን የሐሰት ወሬዎች ከየትም ለቃቅሞ ያቀረበ ነው ። የስደተኛውና የተሐራሚው የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አባታዊ ፍቅር በሚሊዮን በሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ልጆች እንደ ገና መቀጣጠሉ እንቅልፍ የነሣቸው የገዢው ካድሬዎች ፥ የታላቁን አባታችንን ስም አጎደፍን ብለው የከተቡት ከንቱ ክታብ ነው።
ከአገሪቱ ፕሬዝደንት ጀምሮ እስከ ቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር ድረስ ፥ ከሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ እስከ ቤተ ክርስቲያኒቱ ምእመናን ድረስ እውነቱን እየገለጹ ባሉበት ጊዜ ፥ ሐሰቱን እውነት እውነቱን ደግሞ ሐሰት በማለት ያቀናበሩት ቅንብር ነው። የእግዚአብሔር ሰው ዳዊት «እናንተ የሰው ልጆች እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ ? ከንቱ ነገርን ለምን ትወዳላችሁ ? ሐሰትንስ ለምን ትሻላችሁ» ያለው በእርግጥ እንደነዚህ ያሉትን ነው።
የክርስቶስ ገዳዮች የሐሰት ወሬ በከተማው እንዲወራ በማድረግ የክርስቶስን ትንሣኤ እውነተኛነት ለማስተባበል ብዙ ደክመው ነበር ። መቃብር ጠባቂዎቹም ጌታችን መነሣቱን ለአይሁድ ሲነግሯቸው እነዚሁ የክርስቶስ ገዳዮች ጠባቂዎቹን በገንዘብ ገዝተው የሐሰት ሥራቸው ተባባሪ ለማድረግ ሞክረው ነበር ። ይህንንም ወንጌላዊ እንዲህ በማለት ጽፎታል።
«ለጭፍሮቹ ብዙ ገንዘብ ሰጡአቸው ፦ እኛ ተኝተን ሳለን ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት በሉ ። ይህም በገዡ ዘንድ የተሰማ እንደ ሆነ እኛ እናስረዳዋለን እናንተም ያለ ስጋት እንድትኖሩ እናደርጋለን አሏቸው ። እነሱም (ጭፍሮቹ) ገንዘቡን ተቀብለው እንዳስተማሩአቸው አደረጉ ። ይህም እስከ ዛሬ በአይሁድ ዘንድ ይወራል» ብሏል። ማቴ 28 ፥13-15። አሁንም በዘመናችን ቅዱስ ፓትርያርኩን ከመንበራቸው ለማውረድ የአመፅ አስተባባሪዎች የነበሩት ፥ «ጭቁን ካህናት ነን» የአዲስ አበባው ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ለበተነው የሐሰት ምስክርነት የተሰጠ መልስ በማለት ቤተ ክርስቲያንን ሰላም የነሡት እነዚህ ሰዎች ብኩርናውን ለመንግሥት አሳልፎ የሰጠውን የአዲስ አበባውን ኢሕጋዊ ሲኖዶስ ተጠቅመው የፈለጉትን ቢሉ አያስገርምም ። አሁን ሲኖዶሱን የሚያዙት ሰዎች የወያኔ ሰላዮች ሆነው ወያኔን መርተው አዲስ አበባ ሲያስገቡ በቅዱስ ፓትርያሪኩ ላይ ስም አጥፊ ጽሑፎችን ይበትኑ ነበር ። ዛሬም ያንኑ ነው እየሠሩ ያሉት ። ነገር ግን አይሁድ በገንዘብ የገዙት የወታደሮች የሐሰት ወሬ ቤተ ክርስቲያንን እንዳላሸነፋት ፥ የትንሣኤውንም
እውነተኛነት እንዳልጋረደ ፥ የዘመናችን አሳዳጆች የሐሰት መልእክትም በሕጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ ላይም ሆነ በሚመሩት ቅዱስ አባት ላይ የሚያመጣው ለውጥ የለም ።
ታዲያ ታላቅ የታሪክ አደራ ያለበት ፥ ይህ ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ለዚህ የሐሰት ክስ መልስ በመስጠት ጊዜውን በከንቱ ለምን ያጠፋል ? የሚል ጥያቄ መነሣቱ የማይቀር ነው ። ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ይህንን መልስ የሚሰጥባቸው ምክንያቶች የሚከተሉት ናቸው ።
1/ የሚመጣው ትውልድ አባቶቹና እናቶቹ ለቀኖና ቤተ ክርስቲያን መከበር ጊዜ ካነሣቸው ሐሳውያን ጋር ምን ያህል ተጋድሎ እንዳደረጉ እንዲገነዘብና ከየአቅጣጫው የሚመጡትን የሐሰተኞች ወንድሞችን የሐሰት ወሬ እንዳያደምጥ ለማስጠንቀቅ ።
2/ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎችም ይህ ዓይነቱ ስሕተት ወደ ፊትም እንዳይደገም የሚመጣውን ትውልድ ለማስተማር በእውነተኛዎቹ የታሪክ መዛግብት ላይ ተመሥርተው እንዲጽፉ የሚያስችል እውነተኛ መረጃ ለመስጠት ።
3/ ምንም እንኳ አብዛኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በአሁኑ ወቅት እውነቱን የተረዱ ቢሆንም ፥ በባለጊዜዎቹ ካድሬዎች የተበተነው የሐሰት መጽሐፍ አንዳንድ በቂ መረጃ ያላገኙ ወንድሞችንና እኅቶችን እንዳያሳስታቸው ለማድረግ ነው። በመሆኑም በሚቀጥሉት ገጾች በአዲስ አበባ ያለው ጊዜ ያነሣው የፖለቲካ ኃይል ሕገወጥ የፓትርያርክ ምርጫ አድርጎ በሐሰት መንበሩ ላይ ባስቀመጠበት ወቅት በመጽሔት አሳትሞ ለበተናቸው የሐሰት ጽሑፎች በዝርዝር መልስ እንሰጣለን። በመቀጠልም የአዲስ አበባው አካል የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ከዳር እስከ ዳር ያሰሙትን ጩኸት ወደ ጎን በማድረግና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን በመሻር ሐሰተኛ የፓትርያርክ ምርጫ አካሂዳለሁ ማለቱ እንደ ተሰማ በሕጋዊው ቅዱስ ፓትርያርክ የሚመራው ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ በሎስ አንጀለስ ከተማ ባደረገው አስቸኳይ ልዩ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ያወጣውን አጠቃላይ መግለጫ ሙሉ ቃል ፣ እንዲሁም በሐሰት ስለ ተሰየመው ሐሰተኛ ፓትርያርክ ከሕጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠውን መግለጫ እናቀርባለን ። እንዲሁም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን የሚመለከቱ ታሪካዊ ሰነዶች ለምስክርነት በዚህ ጽሑፍ ተካተዋል።ይቀጥላል… (ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)

No comments:

Post a Comment