Wednesday, July 24, 2013

እስቲ ቂማችንን ጥቂት እናቆየው

ይህንን ርዕስ የመረጥኩት ያለምክንያት አይደለም፤ ከጠላት ጎን ተሰልፈው ንፁሃን ዜጎችን በጠራራ ፀሐይ ሲያስጨፈጭፍ አገር ሲሸነሽኑና የአገር ሀብት ዘርፈው ሕዝብ ለሕዝብ ሆድና ጀርባ አድርገው ሲያበቁ ሌላ ማሊያና ሜዳሊያ አጥልቀው ሲመጡ ርችት ተኩሰን ስለምንቀበላቸው የጭቃ ውስጥ እሾሆች ጥቂት ለማለት ነው።
ጨካኙን የወያኔ አምባገነን አገዛዝ ከድተውና አውግዘው የሚመጡትን ግለሰቦች ከመቀበልም አልፎ የተቃዋሚው ጎራ ፓርቲ አመራር ያደርጋቸዋል። አንድ ሰሞን ከበሮአቸውን እንደልቅላቸዋለን ጥቂት ቆይተው ያፌዙብናል፣ ያላግጡብናል፣ ያላዝኑብናል ተመልሰው ጓዳ ጎድጓዳችን ፈትሸው፣ ሰልለው አሰልለው ወደ ጨካኝ ጓደኞቻቸው ቤት ከብዙ መረጃዎቻችን ጋር ይመለሳሉ።
ወያኔዎች በተመሳሳይ መልኩ የሕዝብን ትግል ለከርሣቸው ለውጠው ተቀበሉን ያሉዋቸውን የአንድ ሰሞን መበሸሸቂያ አድርገው እንደሸንኮራ መጥጠው ይተፏቸዋል፣ እንደሲጋራ ቁራጭ ሜዳ ላይ ይጥሏቸዋል፣ የውሃ ላይ ኩበት ያደርጓቸዋል። አቶ ልደቱ አያሌውና ሟቹ መለስ ዜናዊን ወገባቸው እስኪንቀጠቀጥ አጎንብሰው ይቅርታ የጠየቁትን የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ አዛውንት እንደምሳሌ ብጠቅሳቸው ብዙዎች በሀሳቤ ይስማማሉ።
እነዚህ ማፈሪያዎች ዛሬም አሉ በቴሌቪዥኑ መስታወት አይናቸውን በጨው አጥበው በተቃዋሚ ፓርቲ ስም ያላግጣሉ፣ እኛም ቂማችን ጥቂት አላቆየነውም፣ ጥቂቶቻችን ለይቅርታ ምክንያቶችን እንደረድርላቸዋለን። አዎ ዛሬም አይናችሁን ጨፍኑ እናሞኛችሁ እያሉን ነው።
ዛሬም የሕዝብ ወገን ነን የምንለው የተቃዋሚ ፓርቲ ድርጅቶችና አገር ወዳድ ግለሰቦች ከስህተታችን አልተማርንም ዛሬም እነሱ ቅጥፈታቸውን አልተዉም፣ ቀጥለዋል። እኛ ግን ካሸለብንበት ኛ አልነቃንም። እና ለዚህ ነው እየደጋገምኩ ቂማችንን ትንሽ እንኳን እናቆየው ያልኩት። የይሉኝታ ትግል ትግል ሳይሆን ልፊያ ነው። መላፋት ደግሞ የመከረኛውን ወኛችን የሥቃይ ዘመን ያራዝመዋል። ልቀጥል – -
አፍቃሪ ኢህአዴግ የሆነው ንብረትነቱ የታጋይ አማረ አረጋዊ ሪፖርተር ጋዜጣ አዲስ አበባ ከተማ ሆኖ ከኢህአዴግ ሕወሓት ጀምሮ የደጋፊ ተቃዋሚ ተግባሩን እያከናወነ ይኸው 21 ዓመት ዘልቋል። ከተፈቀደለት ቀይ መስመር አለፍ ሲል የአለቆቹን ቁንጥጫ እያጣጣመ ዛሬም አለ። በሌላ በኩል ደግሞ በተመሳሳይ፤ እዚህ ጉያችን ውስጥ ተሸጉጦ ስለሚገኘው እንደብዙዎቹ ስደተኛ አቻዎቹ በባሌ ሳይሆን በቦሌ ካለቆቹ በጥንቃቄ መመሪያ ተሰጥቶት ስለተላከው ያውራምባ ድረ-ገጽ ባለቤት ታጋይ ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ ነው። ይህ ያድዋ ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ግለሰብ እንደስደተኛ ጓደኞቹ የወያኔ ወከባና እንግልት በዛብኝ፣ ሕይወቴ ላይ አደጋ በማንዣበቡ የምወዳትን ሃገሬን ጥዬ መጣሁ ብሎ በሙያ ባልደረቦቹና በወያኔ ተጠቂ ወገኖች ትብብርና ድጋፍ በመጠየቁ ብዙዎቻችን ለቤት ኪራይና ለዕለት ጉርሱ ለተወሰኑ ወራት መደጎማችን አልቀረም። በተለያዩ ውጭ አገር በሚገኙ ሜዲያዎች እየቀረበ ከእንግዲህ ወዲያ እዚህ ሆኜ የወያኔን ፋሽስታዊ አምባገነን አገዛዝ እታገላለሁ አለን፣ የዳያስፖራው ማስ ሜዲያዎችም በተከታታይ ሰፊ የአየር ሽፋን ሰጥተውት ሰበከን፣ አደመጥነው፣ አዘንንለት።
የወያኔ ሰላይ ይሆናል የሚለው የብዙዎች አስተሳሰብ ላይ ብዥታን ፈጠረ። በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ አይንና ጆሮ የሆነውን ኢሳት – የኢትዮጵያ ሳተላይት ሬዲዮና ቴሌቪዥን ጠጋ አለ። ይህን ተቋም ፈተሸው፣ እሱና አለቆቹ እንዳሰቡት ዘው ብሎ ለመግባት ግን አልቻለም። አቅም አጣ፤ አንዳንድ እንቅስቃሴዎቹ ጥርጣሬን መጫራቸው አልቀረም። በዚህም በማኩረፍ የራሱን ድረ-ገጽ አቋቁሞ ኢሳትንና መሰል የተቃዋሚ እንቅስቃሴዎችን ለማፍረስ በግልጽ መንቀሳቀስ ጀመረ። በዚህ እኩይ ተልዕኮው ራሱን ማሳወቅ ናፈቀ፤ አዎ እርግጥ ነው ሊዋጋ የመጣው አምባገነኑን የሕወሓትን አገዛዝ ሳይሆን ተቃዋሚን ነበር። “ሰይጣን ሲያታልል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ይጠቅሳል” እንዲሉ እሱም እንዲህ ሆነ። ከአዲስ አበባው ሪፖርተር ጋዜጣ ባለቤት ጋር በመሆን በራሱ ድረ-ገጽ ላይ “ሪፖርተር ቲቪ” የሚባል የቴሌቪዥን ስርጭት ማስተላለፍ ጀመረ። ይህ አካሄዱ ኢሳትን የማጥፋት አንዱ ተልዕኮው ነበር።
ሌሎችም ተመሳሳይ ተልዕኮ ያላቸውን የወያኔ ሜዲያዎችን ተቀላቀለ። በቨርጂኒያ የሚገኘውን ሠላም ሬዲዮን፣ ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘውን ልዩ ሬዲዮንና ኢትዮጵያዊነት ሬዲዮዎች ጥቂቶቹ ናቸው። ወገኖቼ እንግዲህ እንዲህ ሆነላችሁ የዘንድሮ ጨዋታ። አውራምባ ታይምስ ድረ-ገጽና ከላይ የጠቀስኳቸው የወያኔ ሬዲዮዎች ከፍተኛ በጀት ተመድቦላቸው የዳያስፖራውን ችግር ለማኮላሸት የትግል አንድነቱን ለመስለብ መነሳታቸው እውነት ነው። ይህ አፍቃሪ ወያኔ ግለሰብ ዛሬ በገሃድ ያንድነት ኃይሎችን ለማጥፋት ከተነሱት ተቋማትና የዋህ ግለሰቦች ጋር ለመሥራት እንቅልፍ አጥቶ እያደረ ነው – ዛሬ።
ብዙዎች አካሄድህ አያምርም አስተካክል አሉት፤ ተልዕኮው ነውና አሻፈረኝ እምቢኝ አለ። ዳር ቆመው ተው አይሆንም “ከእባብ ዕንቁላል እርግብ እንዴት ትጠብቃላችሁ?” ያሉትን ብልህ ወገኖች ጆሮ የሚሰጣቸው ጠፋ። ዛሬ ግን ያሉት እውን ሆነ።
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ይህን ማስታወሻ ስከትብ ያንድ የትግል ጓዱ አመጣጥና አካሄድ ትዝ አለኝ። አዎ ተመሳሳይነት ያለው የሕወሓት መልዕክተኛ ታጋይ ጋዜጠኛ ፀሐዬ ደባልቄ። ይህ ግለሰብ ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ የነበረ (በደርግ አገዛዝ ዘመን ማለቴ ነው) በዚያን ዘመን ታታሪ ሠራተኛ በሚል ከማስታወቂያ ሚኒስቴሩ የጉርሻ ሽልማት እንደተበረከተለት ዛሬ በትዝብት የሚያስታውሱት የሙያ ባልደረቦቹ አጫወቱን። ዳሩ ምን ይሆናል ጥቂት እንኳን ሳይቆይ ባዲስ አበባ ከተማ ውስጥ አንድ አባላቸው ሲዘዋወር ጥሎት የሄደው የወያኔ ሕወሓት ሰርጎ ገቦች የስም ዝርዝር የያዘ ዶኩመንት በደርግ የደህንነት ሠራተኞች እጅ ወደቀ። እዚህ ዝርዝር ውስጥ ያሉት በአጠቃላይ የትግራይ ተወላጆች ነበሩ።
በዝርዝሩ ውስጥ የጋዜጠኛ ፀሐዬ ደባልቀው ስም በመገኘቱ ደርግ ከነጓደኞቹ ለቃቅሞ ከርቸሌ ወረወረው፤ ኢህአዴግ በገባ ማግስት ከከርቸሌ ወጣ፣ ላደረገው አስተዋጽዖ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዳይሬክተርነት ሥልጣን ድረስ የወያኔ አገዛዝ ሰጠው (ሾመው)። “የወያኔ ሥልጣን የዛፍ ላይ እንቅልፍ ነው” እንደሚባለው በወያኔ ክፍፍል ወቅት የዛሬ 12 ዓመት ገደማ ይህ ሰው ራሱን በዋሽንግተን ዲሲ አገኘው – የፖለቲካ ጥገኛም ሆነ። የመኖሪያ ወረቀቱ ተፈቀደለት የስደተኞች ማመልከቻ በማዘጋጀት ሥራ (Case worker) ላይ ተሠማራ። ጥቂት ቆየና በቀጥታ በዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው የወያኔ ኤምባሲ ውስጥ ትልቅ ባለሟል ሆነ። ከዚያም አልፎ በቨርጂኒያ በሚገኘው የሠላም ሬዲዮ ጣቢያ አዘጋጅና አቅራቢ ሆኖ እስከዛሬ ድረስ ወያኔያዊ አፍራሽ ተልዕኮውን ያካሂዳል። ዛሬ የዚህ ግለሰብ ወዳጅ በተመሳሳይ ወያኔን አውግዞና ጥገኝነት ጠይቆ የመኖሪያ ፈቃዱን አቀፈ፣ ታጋይ ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ። መተካካት ይሏችኋል ይሄ ነው።
አውራምባ ታይምስ የሚባለው ድረ-ገጽ ምን እየሠራ ነው? የባለቤቱስ ተልዕኮ ምንድነው? ከፊትና ከኋላው ያለውስ ማን ይሆን? እንደጋሪ ፈረስ የሚጎትታቸውስ የዋሆች እነማን ናቸው? የዚህን መሰሪ ተልዕኮ ፍርፋሪ የሚቀላውጡትስ እነማን ናቸው? እስቲ ትንሽ እንፈትሽ።
አውራምባ ታይምስ (ቁጥር 2 ሪፖርተር ጋዜጣ) በሚለው የሚያስማሙን ነጥቦችን ለግንዛቤ እንዲረዳ ልሞክር። ይህ የታጋይ ዳዊት ከበደ ከመግቢያዬ ላይ የጠቀስኳቸው በሰሜን አሜሪካ የሚገኙት የትግል አጋሮቹ ማለትም የሀገር ፍቅር ሬዲዮ፣ ልዩ ሬዲዮ፣ የኢትዮጵያዊነት ሬዲዮና ቨርጂኒያ የሚገኘው በታጋይ ፀሐዬ ደባልቄ የሚመራው ሰላም ሬዲዮ ከፍተኛ በጀት ተመድቦላቸው የዳያስፖራውን ትግል ለማኮላሸት መንቀሳቀሳቸውን እያየን ነው። በጣም የሚገርመው ደግሞ በዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘው በአቶ ምርጫው ስንሻው ባለቤትነት የሚተዳደረው የኢትዮጵያዊነት ሬዲዮ ሲሆን፤ ይህ ራስ ወዳድ ግለሰብ በደርግ አገዛዝ ዘመን የቀበሌ ካድሬ የነበረ በወቅቱ በፈፀማቸው ድርጊቶች ብዙዎች ያዝኑበታል። ዛሬም በግል ሬዲዮ ጣቢያው የእነዚህን አፍራሽ የወያኔ ተላላኪዎች የሚተርፋቸውን ፍርፋሪ ለመለቃቀም እነዚህን የጥፋት መልዕክተኞች በሬዲዮው ላይ ለማቅረብ የከፋፋይነት ተግባሩን በብቃት እየተወጣ ነው። ይህ ግለሰብ ሃገራችን ኢትዮጵያ በከፍተኛ ድርቅ በተጠቃችበት ወቅት ማለትም በ2002 አካባቢ ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው የቀድሞው ኮንቬንሽን ሴንተር አዳራሽ ውስጥ እሱና የሀገር ፍቅር ሬዲዮ ባለቤት በቅንጅት ባቋቋሙት የገንዘብ ማሰባሰቢያ “ደራሽ ግብረ ኃይል” በሚል መጠሪያ በመጠቀም ከሃገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ የተሰበሰበውን ከ200 መቶ ሺህ ዶላር በላይ ገንዘብ ሰብስበው ከዚያ ውስጥ በተወካያቸው አማካኝነት 200 መቶ ሺህ የኢትዮጵያ ብር በወቅቱ ለወያኔ ይርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ለነበሩት ለአቶ ስምዖን መቻሌ አስረክበው ቀሪውን ከመቶ ሺህ ዶላር በላይ የሚቆጠር የሕዝብ ገንዘብ ይዘው በመጥፋታቸው የዋሽንግተን ነዋሪ ገንዘባችን ተበላ ብሎ ቢጮህ ሰሚ ማጣቱ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። ይህም አልበቃው ብሎ በቅንጅት ፓርቲ እንቅስቃሴ ወቅት መሪዎቹ ከእስር በተፈቱ ማግስት የኢንጂነር ኃይሉ ሻውል ጋሻ ጃግሬ በመሆን ለልዩነታቸው ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያደረገ ግለሰብ መሆኑ በዚህ በዋሽንግተን ዲሲ በሚገባ ይታወቃል። ግለሰቡ የጥቅም ሱሰኝነቱን ለመወጣት ሲል ብቻ በተለያዩ ማኅበራዊ ጉዳዮች ውስጥ እየገባ የሚፈጽማቸውን የክህደት እንቅስቃሴዎች በዚህ ድረ-ገጽ ማስፈሩን ለጊዜው ማቆየት ይገባልና ትቼዋለሁ።
ዋናው ቁም ነገር በውጭ የምንገኝ ኢትዮጵያውያን አገር ወዳዶች እንደነዚህ ያሉ ሆድ አደር ግለሰቦችን በቃችሁ የምንላቸው መቼ ነው? ላለፉት 21 ዓመታት አታለውናል፣ ገንዘባችንን ዘርፈውናል፣ ጊዜያችንን አቃጥለዋል፣ አንድነታችንንና የትግል ስሜታችንን አኮላሽተውብናል፤ ዛሬ ደግሞ ወያኔ ከፍተኛ በጀት ተመድቦላቸው በቡድን ተደራጅተው እንደመዥገር በብብታችን ውስጥ ተሸጉጠው ደማችንን እየመጠጡት ነው። እና ምን እናድርግ፣ እንዴት ለዚህ ችግር መፍትሔ እንፈልግ?!
ሰሞኑን ዘ-ሐበሻ በተባለው ድረ-ገጽ ላይ ከኢየሩሳሌም አርአያ የቀረበው ጥቆማ ሁኔታውን ገሃድ አድርጎታል። በዚህ ድረ-ገጽ ላይ የሰፈረውን አጋላጭ ማስረጃ ቃል በቃል ላስቀምጥና ፅሑፌን ላብቃ።

በረከት ስምዖን በሰማያዊ ፓርቲ ዙሪያ እየዶለቱ ነው

(ከኢየሩሳሌም አርአያ)
በዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ሊቀመንበርነት ከሚመራው ግንቦት 7 ጋር በተያያዘ በሰማያዊ ፓርቲ ዙሪያ በረከት ስምዖን የሚመሩት የመንግሥት አካል በምሥጢር እየዶለተ መሆኑን ምንጮች ጠቆሙ። በቅርቡ ባንድ ድረ-ገፅ የወጣውን የዶ/ር ብርሃኑን ንግግር በማስረጃነት ይዘው እየተንቀሳቀሱ ያሉት አቶ በረከትና ተከታዮቻቸው ባገር ውስጥ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ሰማያዊ ፓርቲ ከግንቦት 7 ጋር ግንኙነት አለው፣ ከግንቦት 7 የኝዘብ ድጋፍ ይደረግለታል በሚል እነበረከት ድምዳሜ ላይ መድረሳቸውን የጠቆሙት ምንጮች የፓርቲውን አመራሮች “ከሽብርተኛ ቡድን ጋር በመገናኘት” ለመክሰስ ሴራ እያበጃጁ መሆኑን አስታውቀዋል። የፓርቲው አመራሮችን ከማሰር ባለፈ “ሰማያዊ ፓርቲ በሽብርተኛ ድርጅት የሚመራ ነው” በሚል በአገር ውስጥ የሚኖረውን የፓርቲው ቀጣይ ሕልውና ለማክሰም ጭምር እየዶለቱ መሆኑን ምንጮቹ ጠቁመዋል። ከበረከት በተጨማሪ ደብረጽዮን ይህንን ሴራ በበላይነት እየመከረበት እንደሆነ ምንጮቹ አያይዘው ገልፀዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አሜሪካ አገር ለሚገኝ አንድ ጋዜጠኛ የፓርቲው ባለሥልጣናት ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንደላኩለት ምንጮች አጋለጡ። በመጀመሪያ 250,000 (ሁለት መቶ ሃምሳ ሺህ)፣ በማስከተል 50,000 (ሃምሳ ሺህ) ዶላር ተመንዝሮ በእጁ እንደደረሰው ምንጮቹ ጠቁመዋል። ገንዘቡ ከነበረከት በኩል በምሥጢር የተላከ መሆኑን ያጋለጡት ምንጮቹ በዚሁ መሠረት ጋዜጠኛው ለሕወሓት/ኢህአዴግ ማገልገል መቀጠሉና በተለይ አሁን በሰማያዊ ፓርቲ ዙሪያ እየተሸረበ ያለው ሴራ መነሻው ይህ ሰው እንደሆነ አያይዘው ገልፀዋል።
“እስቲ ቂማችንን ጥቂት እናቆየው” ለምን?!!
  • አሰፋ ማሩና ወጣት ሽብሬ በጠራራ ፀሐይ በጥይት ተደብድበዋል፣
  • ከ200 በላይ ዜጎች በአደባባይ ባልሞ ተኳሽ አውሬዎች ተጨፍጭፈዋል፣
  • የአማራው ዜጋ እየተፈናቀለ ከነሕይወቱ ወደ ገደል ተጥሏል፣
  • የኦሮሞው ወገናችን ያገሪቱን እሥር ቤቶች አጣቧል፣
  • በዋልድባ ገዳም አባቶች እየተቀጠቀጡ እየተሰደዱ ነው፣
  • የሙስሊሙ ሕብረተሰብ እየተቀጠቀጠ በእሥር እየማቀቀ ነው፣
  • ከ80 ሺህ በላይ ዜጎች በኢትዮ ኤርትራ ትርጉም የለሽ ጦርነት ተማግደዋል፣
  • ዛሬም ዜጎች በየእስር ቤቱ አይናቸው፣ ብልታቸው እና ጡታቸው በጉጠት እየተቀረጠፈ ነው፣ ሌላም ሌላም ብዙ እጅግ ግፍ ላለፉት 22 ዓመታት . . .
አዎ እስቲ ቂማችንን ትንሽ እንኳ እናቆየው፤ በራችንንም ገርበብ እናድርግ። ምጥንቃቅ አሉ ገዢዎቻችን – ጠንቀቅ ነው ደጉ!
- – - ይቀጥላል – - -
ከናደው

No comments:

Post a Comment