Friday, June 28, 2013

አዛዛኙ ክስተት !!! ከ 110 በላይ ኢትዮጵያዊ ባህር ላይ ቀሩ


xc

ስለ ስደተኛው የቁራሌው ጩኸት እስከ ጠ/ሚኒስትር ቢሮ….
በግሩም ተ/ሀይማኖት
…ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ተቃዋሚ ሀይሎች ከጅቡቲ ወስደው መጠቀሚያ ሊያደርጓቸው ነበር፡፡ ብዙ እናውቀለን…›› ይህን በስደት ዙሪያ የአዞ እንባ ያነባው ኢቲቪ ለውይይት ከጋበዛቸው ውስጥ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ያዳለጣቸው ነው፡፡ ያዳለጣቸው ያልኩት መንግስት ያን ሁሉ ማስመሰያ ያደረገበት ምክንያት ምን እንደሆነ አባሳደሩ በግልጽ ሳያውቁ ስላስቀመጡት ነው፡፡ የስደተኛው ህይወት አሳዝኗቸው አይደለም፡፡
ተቃዋሚዎች ይዘው ሊጠቀሙባቸው ስለሚፈልጉ ወይም ስለሞከሩ ነገ ስልጣናቸውን ላለማጣት ነው፡፡ ያ-ካልሆነማ ስንት አመት በሙሉ በስደት ወገን ረገፈ ሲባል…ሲጮህ ዝም በዝምታ ብለው በስደተኛው የጣር ድምጽ ባላላገጡ ነበር፡፡ ግን የፈሩት ተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች የትጥቅ ትግል ሊያደርጉ መሰናዶ ላይ ስለሆኑ ከሆነ አንድ ሰሞን አራግበው ዝም ማለት ጦሱ እንደሚብስ ለምን ልብ አላሉትም? የወጣውስ በአግባቡ ወደ ሀገሩ እንዲመለስ ካልተደረገ ወዴት እንደሚያቀና እንዴት አላገናዘቡም? ይገርማል፡፡ ሳዑዲ አረቢያ እየተሰቃየ ያለው ህዝብ ወዴት እያመራ ይመስላቸዋል? ለምንስ ያን አያስቡም? እንደ ዜግነቱ የሀገሩ ኤምባሲ ሊከራከርለት ሲገባ፣ ወደ ሀገሩ ሊመልሰው ሲገባ ኮሚኒቲ የሚባለው ውስጥ ተፋፍጎ ሶስት እና አራት አመት እንዲቀመጥ የአእምሮ መታወክ እንዲገጥመው ሲደረግ፣ በሽተኛውም ጤነኛውም በአንድ ቦታ እንዲቆይ ሲደረግ…ትኬት የሚቆርጥልህ ቤተሰብ ከሌለህ…ያመጣችሁ ሰው ትኬት ይቁረጥላችሁ..ተብሎ ከእሱ ዜግነት ይልቅ ለብር ክብር ሲሰጥ ሲያይ..ሀገሬ ባላት ኤምባሲ ሲበደል ለምንስ አይከፋው? ለምንስ አማራጭ አይወስድ? አንድ ሰሞን ሆይ ሆይ ብሎ ፖለቲካ ለማሳመሪያ ፕሮግራም ማድመቂያ ማራገብስ ውጤት ያመጣል? አያመጣም፡፡ መንግስት ህዝብን እያታለለ እስከመቼ የሚጓዝ ይመስለው ይሆን? ህዝቡ እኮ ያውቃል፡፡ ሳዑዲያ ፣ የመን.. እየተጨቆነ ያለው ወገኑ አይደለ እንዴ? ቤተሰቡ አይደለ እንዴ? ታዲያ የአንድ ሰሞን የሚሊኒየም አዳራሽ እና የኢቲቪ ለቅሶ የአዞ እንባ አልሆነም? ሆነ፡፡
አስተዳዳሪዬ ባይላቸውም አስተዳዳሪህ ነን ብለው ላዩ የተጎበሩበት ሰዎች እስከ ጠ/ሚኒስትሩ ድረስ በውሸት ሲደልሉት፣ አፋቸው ሌላ ስራቸው ሌላ ሲሆንበት ቢጠላቸው ምን ሊደንቅ? ምንም፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለትጥቅ ትግል ስደተኞችን ሊጠቀሙባቸው ብቻ ሳይሆን ስደተኛው ሀገሩ መመለስ ካልቻለ እሱ ራሱ ተቃዋሚዎችን ፍለጋ በዳዴ መሄዱ አይቀርም፡፡ በተቃዋሚዎች ተጠቅሞ መታገሉም አይቀርም፡፡ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ካሉት ላይ ልበደርና ‹‹…ከጅቡቲ ወስደው ተቃዋሚዎች ለትግል ሊጠቀሙባቸው…›› ቀርቶ ስለ ስደተኞቹ መኖርስ ተቃዋሚዎች ያውቃሉ ወይ? እንደሚያውቁ አቃለሁ ግን እነሱ ‹‹..አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም..›› እንዲሉ ሆነዋል፡፡ ስደተኛው ኢትዮጵያዊ የሆነ እስከማይመስል ድረስ ተቃዋሚዎችም ረስተውታል፡፡ የተሻለ ሀገር ቢሆን የሚሰደደው እና ዶላር መቁጠር ቢጀምር ግን እኛ ያላንተ ይባል ነበር፡፡ ዛሬ ምን ሊያደርግ? መከራ እንጂ ዶላር ስለማይቆጥር አላስታወሱትም፡፡ መንግስት ግን መከራውን መስማቱን አይፈልግም እንጂ ከዚህ ችግር ተርፈው ከተማ ከገቡ ከኤምባሲው ምንም አይነት ግልጋሎት ቢፈልግ ጌሙ ፍራንካ ነው፡፡ ዜጋ ነህ ቅብርጥሴ…ምንትሴ አይሰራም፡፡ ገንዘብ ከያዘ የአማራ ልማት..የትግሬ ልማት..የእንትን ልማት…በቆዳ እስኪቀሩ መጋጡን እንደ ጅብ ይችሉበታል፡፡ እሰይ የወያኔ ኤምባሲ…ብራቮ ይህን ምስኪን ስደተኛ ተገፍቶም ተደፍቶም ያመጣውን በሰበብ አስባቡ ንጠቁ፡፡
ደሀን የሚያስብ፣ ግፍ የሚፈጸምበት ስደተኛን የሚያይ የሚያስተውል መንግስትም ሆነ ተቃዋሚ አልገጠመንም፡፡ ያው ሁሌም ዞረሽ..ዞረሽ እንደሚሉት አይነት ነው የሚገጥመን፡፡ ትላንት ከሶማሊያ ጋር አብረው ሀገራቸውን የወጉ ተቃዋሚዎች አይነት አሁንም አሉን ከግብጽ ጋር ለመሰለፍ ያቆበቆቡ፡፡ ሀገራቸውን ከጠላት ጋር ወግተው ስልጣን ማግኘት እንጂ የህዝቡ ቁስል ያላቆሰላቸው ተቃዋሚዎች አሁንም አፍርተናል፡፡ ኢትዮጵያን እንወዳለን፣ ሀገሬ ክብሬ.. የ3000 ዘመን ታሪክ እያሉ ቀረርቶ የሚያሰሙ መንግስት እና ተቃወዋሚ አሁንም አሉን፡፡ ባይኖሩ በቀሩብን፡፡ ኢትዮጵያ ሀገሬ ጋራሽ ሸንተረሩ ሜዳማ…የሚል ቀረርቶ እያንቃረሩ መሬትና አፈሩን የሚወዱ ህዝቡን ያላማከሉ መንግስትና ተቃዋሚ አሉን፡፡ አሉ ከተባለ….
በሰቀቀን ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ተሳቆ መውጫ ቀዳዳ ጠፍቶት፣ ሀገሩን መርገጫ መላ አጥቶ ያለውን ዜጋ ማን አስታወሰው? ማንም፡፡ የመን ውስጥ ሀረጥ የሚባለው የአለም አወቀፉ ስደተኞች ድርጅት ካምፕ ውስጥ ያለውን ስደተኛ ቁጥር ማን ይቀንሰው? የኢትዮጵያ መንግስት ከስደተኛ ቢሮው ጋር በመተባበር ዜጎቼን እየሰበአሰብኩ ነው ሲል ይቃዣል፡፡ ከዚህ ቅዠት ግን መቼ እንደሚነቃ እና እንደሚሰራ ነው ግራ የገባን፡፡ ስደተኛው አሁንም ስቃይ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ስደተኛው አሁንም ባህር እየተሻገረ ነው ያለው፤ ስደተኛው አሁንም ባህር ላይ እየሰመጠ ነው የለው፡፡ ከሳምንት በፊት ከጅቡቲ ወደ የመን ድንበር እየገሰገሰ ያለ ጀልባ በመሳሪያ ተመቶ ሰጥሟል፡፡ የጫናቸው ዜጎቻችን በሙሉ ባህር በልቷቸዋል፡፡ ወደ 120 ሰው እንደሞተ ወዲያው ሰማሁ እና ለማጣራት አለም አቀፉ ስደተኞች ድርጅት ውስጥ እና ሜዲካል ሳን ፍሮንቴን (ድንበር የለሽ የህክምና ቡድን) ሰራተኞች ጋር ስልክ መታሁ፡፡ እነሱም ወሬውን አማቱት፡፡
በመሳሪያ ነው የተመታው ስለተባለ ማን ነው የመታው የሚለውን ጨምሮ እንዲመልሱልኝ በመጠየቄ የውሾን ነገር ያነሳ ውሾ እንድንል ነገሩን አድበስብሰው እንዲያውም መረጃ ካገኘህ ስጠን አሉ፡፡ በሰዓቱ አስከሬን በመልቀም ስራ ላይ ተሰማርቶ የነበረ ሰው ነው ደውሎ መረጃውን የመረጀኝ፡፡ ከሌሎች አካላት ለማጣራት እንደሞከርኩት ደግሞ በመሳሪያ ተመቶ ሳይሆን በአሁኑ ወቅት ሀይለኛ ንፋስ(ማዕበል) ያለበት ወቅት በመሆኑ ያሰጠማቸው ማዕበል ነው በመሳሪያ አልተመታም ብለውኛል፡፡ ጀልባው ተመታም አልተመታም ለእኛ ወገኖቻችንን አጥተናል፡፡ ባንዴ 120 አካባቢ አርግፈናል፡፡ ይሄ መንግስት ፍካሬውን ሳይጨርስ የሆነ ሁነት ነው፡፡ ያሳፍራል፡፡ መንግስት የስልጣን ዘመኑን ማራዘሚያ የወቅቱን ፖለቲካ ማስከኛ ለፈፈው የሳምንት ሆይ ሆታ ሳይፈዝ ይሄ መሆኑ ያወራል እንጂ መቼ ይሰራል፡፡ ማውራት እና መስራት ለየቅል ናቸው ያሰኛል፡፡
በግሩም ተ/ሀይማኖት

No comments:

Post a Comment